Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, December 26, 2013

ከ1924 - 2002 በኢትዮጵያ የተደረጉ ምርጫዎች ግምገማ በግርማ ሞገስ

ሰላማዊ ትግል እና ባህሪያቱ
ስልጠና ክፍል አምስት፥ ከ1924 - 2002 በኢትዮጵያ የተደረጉ ምርጫዎች ግምገማ ቅዳሜ ታህሳስ 12 ቀን 2006 ዓ.ም. [December 21, 2013] - ግርማ ሞገስ
የስልጠና ክፍል አምስት ግብ በዐፄ ኃይለስላሴ ዘመነ መንግስት (1924-1967)፣ በደርግ ዘመነ መንግስት (ከ1967 - 1983)፣
(3ኛ) በህውሃት/ኢህአዴግ ዘመነ መንግስት (1983 - 2002) የተደረጉትን ምርጫዎች በአጭር በአጭሩ መጎብኘት እና
መገምገም ነው። ምርጫ 97 ግን በርከት ያሉ ትምህርቶች በመለገሱ ሰፋ አድርገን እንጎበኘዋለን።

ምስጋና፥ ይኽን ግምገማ ሳዘጋጅ ከሌሎች መረጃ ምንጮች በተጨማሪ “ግንቦት 7” በሚል ርዕስ ክፍሉ ታደሰ ስለ ምርጫ 97
ዝግጅት፣ ሂደት እና አፈጻጸም የጻፈውን መጽሐፍ አና “ነፃነት እና ዳኝነት” በሚል ርዕስ ስየ አብርሃ ከጻፈው መጽሐፍ ውስጥ
ስለምርጫ 97 አንስቶ ምክሮች የሚለግስበትን ጠቃሚ ምዕራፍ ተጠቅሜያለሁ። እንዲሁም የታሪክ ባለሙያዎቹን የባህሩ
ዘውዴን እና የተክለ ፃድቅ መኩሪያን መጽሐፍቶች ተጠቅሜያለሁ። ለሁሉም ምስጋናዬ ገደብ የለውም።
(1) ምርጫ በዐፄ ኃይለስላሴ ዘመነ መንግስት (1924-1967)
ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ የዘመናዊ ኢትዮጵያ ታሪክ (A History of Modern Ethiopia, 1855-1991) በሚለው መጽሐፉ
በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ህገ መንግስት በዐፄ ኃይለስላሴ ዘመን በ1924 ዓመተ ምህረት መታወጁን እና በዚያው አመት
የኢትዮጵያ የመጀመሪያ ፓርላማ መሰብሰቡን ይገልፃል።

ኢትዮጵያ በህገ መንግስት መተዳደሯ የዘመናዊነት ምልክት ቢሆንም በዚያን በጉልተኛ ስርዓት ዘመን የተደነገገው ህገ
መንግስት ንጉሰ ነገስቱ በተወላጅነት ፍጹም የስልጣን ባለቤት መሆናቸውን የደነገገ ህገ መንግስት ነበር። ስለዚህ በ1924 ዓ.ም.
የታወጀው ህገ መንግስት የንጉሰ ነገስት ኃይለስላሴን ስልጣን ባለቤትነት ከእግዚአብሔር በስተቀር በማንም ሊጠየቅ
እንደማይችል እንደሚከተለው በሚደነግግ አንቀጽ እንደሚጀምር ተክለ ፃዲቅ መኩሪያ ይገልጻል፥

“ከንግስት ሳባና ከሰለሞን ዘር ከመጣው ከመጀመሪያው ንጉስ ከቀዳማዊ ምኒልክ የተወለደ በጳጳስ
ተቀብቶ ስርዓተ ንግስና ተደርጎለት ዘውዱን ከደፈና መንበረ ዳዊት ዙፋን ላይ ከተቀመጠ በኋላ ክብሩ
ሳይቀነስ ማዕረጉ ሳይገሰስ (ሳይሻር) ስልጣኑ ሳይደፈር እንደልቡ ያስተዳድራል።”
ስለዚህ እንደ አቤ ጎበኛ አይነቱ ተራማጅ አስተሳሰብ የነበራቸው ግለሰቦች በ50ዎቹ ግድም የፓርላማ አባል ከመሆናቸው
ቀደም ብሎ በነበረው ጊዜ በፓርላማው ውስጥ በይፋ የንጉሱን ስልጣን የሚተች የፓርላማ አባል ቢገኝ ብርቅ ነበር። አቤ
ጎበኛ “አልወለድም” የተሰኘው ልብ ወለድ መጽሐፍ ደራሲ ነው። ይኽ መጽሐፍ ለጥቂት ቀናት ገበያ ላይ ከዋለ በኋላ ፖለቲካ
ነው ተብሎ በኃይለስላሴ ዘመን እንዳይሸጥ ተደርጎ ነበር። በደርግ ዘመን ታትሞ ገበያ ላይ ውሏል።

የሆነው ሆኖ የፓርላማው አባሎች በአካባቢያቸው ተፎካክረው በምርጫ አሸንፈው የተመረጡ ሲሆኑ በፓርላማው ውስጥ
የተወሰኑ አመቶች ካገለገሉ በኋላ ሌላ ምርጫ ይደረግ ነበር። ይሁን እንጂ በኃይለስላሴ ዘመን የመደራጀት መብትም ሆነ
የፖለቲካ ፓርቲዎች አልነበሩም። ተፎካካሪዎቹም ቢሆኑ በግል የሚፎካከሩ የመሬት ወይንም የሌላ ንብረት ባለቤት መሆን
ነበረባቸው። ማንኛውም ዜጋ የመመረጥ መብት አልነበረውም። ስለሆነም ምርጫው ዴሞክራሲያዊ አልነበረም።

ከፍ ብለን ያነበብነው ህገ መንግስት እንደ እንግሊዝ አገር ህገ መንግስት የንጉሱን ወይንም የንግስቲቱን ስልጣን የሚገድብ
ሳይሆን ስልጣንን ጠቅልሎ በንጉሰ ነገስቱ እጅ የሚያስገባ ነበር። የሚመረጡትም ባላባቶች እና መሳፍንቶች ስለነበሩ የመሬት
ላራሹን ጥያቄ ሳይቀር በበጎ አይን የሚያይ ፓርላማ አልነበርም።
(2) ምርጫ በደርግ ዘመነ መንግስት (ከ1967 - 1983)
በደርግም ዘመን ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዲኖሩ አይፈቀድም ነበር። በኢትዮጵያ የነበረው ብቸኛው የፖለቲካ ድርጅት
በአምባገነኑ ኮለኔል መንግስት ኃይለማሪያም የሚመራው የኢትዮጵያ ሰራተኞች ፓርቲ (ኢሰፓ) ብቻ ነበር። ይሁን እንጂ
በደርግም ዘመን ምርጫ ተካሂዷል። በምርጫው የሚወዳደሩትም ሆነ የሚያሸንፉት የዚሁ ፓርቲ አባሎች ወይንም ፓርቲው
እንዲመረጡ የፈለጋቸው ግለሰቦች ብቻ ነበሩ። ስለሆነም ምርጫው ዴሞክራሲያዊ አልነበረም።
ወታደራዊው ደርግ ስልጣን የጨበጠው በመፈንቅለ መንግስት ነው። ምንም አይነት መፈንቅለ መንግስት ተቀባይነት ሊኖረው
እንደማይገባ ሳንዘነጋ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት እጅግ አደገኛ ሊሆን እንደሚችል የሚከተሉትን ነጥቦች ልብ ልንል
ይገባል፥ (1ኛ) ከምልመላ እስከ ምረቃ ድረስ የወታደር ትምህርት የአገር ድንበር መጠበቅ የሚያስችል የግድያ ሙያ ነው።
(2ኛ) ወታደር አገር እንዲያስተዳድር የሚሰጠው ትምህርት የለም። ወታደር ዋንኛ እውቀቱ እና ችሎታው መግደል ነው።
 1ተቃውሞን ለማስወገድ የሚቃወማቸውን መግደል ይቀናቸዋል ቢባል ስህተት አይደለም። ስለዚኽ ወታደር ስልጣን
ለመጨበጥ ሲሞክር ህዝብ ምንም አይነት ትብብር መለገስ የለበትም። መፈንቅለ መንግስትን እንዴት ህዝብ ሊከላከል
እንደሚችል በስልጠና ክፍል አራት አጥንተናል። አምባገነኑ መንግስቱ ኃይለማሪያም እና ተከታዮቹ፥ (1) የተቃወማቸውን
የተማረ ትውልድ መርጠው ማጥፋታቸው፣ እና (2) ኋላቀር እና ደሃ ኢትዮጵያን ይበልጥ ኋላቀር እና ይበልጥ ደሃ አድርገው
መሄዳቸው መርሳት የለበትም። በጠበንጃ ደርግን ፈንቅሎ ስልጣን የጨበጠው ህውሃት/ኢህአዴግ ደግሞ ዴሞክራሲ እየሰበከ
ጸረ-ዴሞክራሲ ስርዓት የገነባ አምባገነን ስለመሆኑ ለጥቀን በተለይ ምርጫ 97ን ስንገመግም በግልጽ እናስተውላለን።
(3) ምርጫ በህውሃት/ኢህአዴግ ዘመነ መንግስት (1983 - 2002)
በአልቤኒያ እና በሶቪየት ህብረት አምባገነኖች የፖለቲካ ንድፈ አሳብ ስልጥኖ ያደገው ሟቹ አምባገነን መለስ ዜናዊ እና
ድርጅቱ ህውሃት ስልጣን ሊጨብጡ ግድም ሶቪየት ህብረት ወድቃ አለም አቀፍ የፖለቲካ በላይነት በምዕራቡ አለም እጅ
ገብቶ ነበር። ዘመናዊ ለመምሰል እና የምዕራቡን ድጋፍ ለማግኘት ነፃ ገበያ፣ ነፃ ፉክክር፣ ነፃ ምርጫ፣ ዴሞክራሲ የሚሉትን
የካፒታሊዝም ጸባዮች ተቀብያለሁ ማለት የግድ ነበር። “ህጋዊነትን” በምርጫ ማግኘት ግዴታ ስለነበር አቶ መለስ ስለ ምርጫ
መስበክ ጀመረ። ስለዚህ በህውሃት/ኢህአዴግ መንግስት የሚጠራ ምርጫ “ህጋዊነትን” ከምዕራቡ ለማግኘት እንጂ ከራሱ
ህዝብ እና በኢትዮጵያ ውስጥ ከሚታገሉ ተቃዋሚዎች ለማግኘት እንዳልሆነ ግልጽ መሆን አለበት።
በምዕራቡ አለም መስፈርት ህዝቡ በምርጫ እስከተሳተፈ ድረስ የተቃዋሚ ፓርቲዎች በምርጫ አለመሳተፍ ብቻውን
ለህውሃት/ኢህአዴግ ፓርቲ ህጋዊነትን አያሳጣውም። ምርጫው ነፃ መሆኑ አለመሆኑም ከወቀሳ ባሻገር ህጋዊነትን
አያስነፍግም። አምባገነኖች የሚጠሩት ምርጫ ነፃ ምርጫ እንደማይሆን ለማወቅ ምዕራቡ መካሪ አይሻም። በምርጫ
የተሳተፈው ህዝብ በፈቃደኛነት ይሁን በፍራቻ ለምዕራቡ ምኑም አይደለም። ምርጫ መደረጉ እና ህዝብ መሳተፉ ብቻ በቂ
ነው በምዕራቡ ዘንድ። ምርጫ ቢሰረቀም ህዝብ ዝም ብሎ እንደቀድሞ መገዛቱን ከቀጠለ ምዕራቡ ደንታው አይደለም። ነገር
ግን ተቃዋሚው አፉን እና አቅሙን አንድ አድርጎ ነፃ ባልሆነ ምርጫ ተሳትፎ ገዢውን ፓርቲ በግልጽ ድምጽ ብልጫ ካሸነፈ
እና ድምጽ ለማስከበር የሚያስችለው ቀጣይነት ያለው ሰላማዊ ህዝባዊ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ እና ማህበራዊ ትብብር መንፈግ
እና ጣልቃ የመግባት እምቢተኛነት ካደረገ ምዕራቡ በፍጥነት ከተቃዋሚው እንደሚተባበር ግልጽ ነው። ይኽን መሰረታዊ
ሃቅ መዘንጋት የለብንም። አምባገነኖች ስለሚጠሩዋቸው ምርጫዎች ምንነት እና ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሊያደርጉት ስለሚገባው
ዝግጅት በስልጠና ክፍል አራት ሰፋ አድርገን አጥንተናል። ከቦታው ስንደርስ እንደምናነበው ምርጫ 97 ይህን ሃቅ ገሃድ
አድርጋለች። በቅድሚያ ግን ቀደም ብለው የተደረጉትን ምርጫዎች በአጭር በአጭሩ እናጠናለን።
ምርጫ 87፥ በ1987 ዓመተ ምህረት ምርጫው ነፃና ፍትሃዊ ስለማይሆን በምርጫ መሳተፍ የለብንም። ከተሳተፍን
ህውሃት/ኢህአዴግን ህጋዊ ከማድረግ ባሻገር ፋይዳ የለውም በሚል የተሳሳተ የፖለቲካ እምነት ተመርተው በርካታ በተለይ
ከኢትዮጵያ ውጭ በሰሜን አሜሪካ የሚኖሩ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአገር ውስጥ ያሉት ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በምርጫ 87
እንዳይሳተፉ አደረጉ። ስለዚህ ህጋዊነት እንነፍጋለን ብለው የወሰዱት እርምጃ ህውሃት/ኢህአዴግ ለምዕራቡ አለም ማሳየት
የሚፈልገውን ህጋዊነት ካለምንም ውጣ ውረድ እንዲያገኝ አደረጉ። በተደረገው አገራዊና ክልላዊ ምርጫ በ89 ከመቶ ድምጽ
ህውሃት/ኢህአዴግ አሸነፈ ተባለ። ከ546 አገራዊ ወንበሮች 491 ወንበሮችን ያዘ። አገሪቱን ለአምስት አመቶች በፈለገበት
አቅጣጫ ወሰደ።
ምርጫ 92፥ በግንቦት 1992 ዓመተ ምህረት ሁለተኛው አገራዊና ክልላዊ ምርጫ ተካሂዶ በአገራዊ ደረጃ ከ40 በላይ
ፓርቲዎች ተሳተፉ። እነዚህ 40 ተቃዋሚ ፓርቲዎች በመለስተኛ ፕሮግራም ዙሪያ ተሰባስበው እራሳቸውን ለህዝብ ሊያቀርቡ
ባለመቻላቸው 40 ደካሞች ሆነው ነበር ኢህአዴግን የገጠሙት። በዚህ ምክንያት ተቃዋሚዎች በምርጫ 92 ከምርጫ 87
የተሻለ ቁም ነገር መስራት አልቻሉም። ከ547 ወንበሮች ኢህአዴግ 481 ወንቦሮችን ማለትም 88% አሸነፈ። ለሌሎች አምስት
አመቶች ሌላ ህጋዊነት ተሰጠው ማለት ነው። ድምር 10 አመቶች።
ምርጫ 97፥ ምርጫ 97 የተለየ ስለነበር በአምስት ክፍሎች ከፍለን እንጎበኘዋለን። እነሱም፥ (1ኛ) በ1995 ዓ.ም ሐምሌ ወር
ተቃዋሚዎች ህብረት ከመሰረቱበት ጊዜ ጀምሮ እስከ 1997 ምርጫ ቀን (ግንቦት 7)፣ (2ኛ) ከ1997 ዓ.ም ምርጫ ማግስት
(ግንቦት 8) እስከ 1997 ሰኔ ወር ሁከት ፍጻሜ፣ (3) ከሰኔ ወር ሁከት ፍጻሜ እስከ በጳጉሜ ይፋ የተደረገው የምርጫ
ውጤት፣ (4) ከ1998 መስከረም ወር እስከ 1998 ጥቅምት እና ህዳር ወሮች ዳግማዊ ሁከት፣ እና (5) ምርጫ 97 ድምዳሜ።
የግምገማችን ግብ በዚያ ምርጫ የሆነውን፣ የተደረገውን እና የተፈጸመውን ታሪክ መለስ ብሎ ማስተዋል እና ለምርጫ 2007
ትምህርት መቅሰም ነው።
ክፍል (1)፥ ምርጫ 97 - ከ1995 ሐምሌ ወር የተቃዋሚዎች ህብረት ምስረታ እስከ 1997 ምርጫ ቀን (ግንቦት 7)
* በዚህ ክፍል ለምርጫ 97 ህውሃት/ኢህአዴግ እና ተቃዋሚዎች ያደረጉዋቸውን ዝግጅቶች እና በተቃዋሚዎች መንደር
የነበሩትን ችግሮች እንመረምራለን።
ከሶቪየት ህብረት መውደቅ እና ካፒታሊዝም በአለም አቀፍ ደረጃ የበላይነትን ካገኘበት ጊዜ ወዲህ ጀምሮ ስልጣን ላይ
የሚገኙ አምባገነን መንግስቶች እንደሚያደርጉት ሁሉ በምርጫ 97ም የአምባገነን ህውሃት/ኢህአዴግ ግብ ‘ህጋዊነት’ ማግኘት
 2 እንጂ በምዕራቡ አገሮች እንደሚደረገው ነፃ ምርጫ አድርጎ ለማሸነፍ እና ከተሸነፈም ሽንፈትን በፈቃደኛነት (ሳይገደድ)
ተቀብሎ ስልጣን ላሸነፈ ፓርቲ ማስረከብ አይደለም። በፈቃደኛነትም ሆነ በፍራቻ ህዝቡን በምርጫ ማሳተፍ እስከቻሉ ድረስ
ምርጫው ነፃ ሆነ አልሆነ፣ የምርጫ ዘመቻው ዴሞክራሲያዊ ሆነ አልሆነ፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በምርጫው ተሳተፉም
አልተሳተፉ፣ የምርጫው ውጤት ተወደደም ተጠላ ‘ህጋዊነት’ እንደሚያገኙ የዘመናችን አምባገነኖች ጠንቅቀው ያውቁታል።
ይኽን የአምባገነን አገሮች ምርጫ ሃቅ የዝንባቡዊው ሙጋቤ ያውቀዋል። እየተጠቀመበት ነው። ህውሃት/ኢህአዴግ
ያውቀዋል። እየተጠቀመበት ነው። በአጨቃጫቂው እና የአውሮፓ ህብረት ምርጫ ታዛቢዎች እነ አና ጎመዝ ሳይቀሩ
ምርጫው አለም አቀፍ መስፈርት አያሟላም ያሉት ምርጫ 97 ሳይቀር በወቅቱ የአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳይ ኃላፊ
የነበረችው ካትሪን አሽተን ህብረቱን ወክላ በምርጫ 97 ከተመረጠው የኢትዮጵያ መንግስት ጋር ለመስራት ዝግጁ መሆኗን
የሚገልጽ መግለጫ ስታወጣ ጊዜ አልፈጀባትም ነበር። በምርጫ 97 የአሜሪካው ፕሬዘዳንት የነበረው ጆርጅ ቡሽም በአቶ
መለስ ለሚመራው መንግስት እውቅና እና ድጋፍ ከመስጠት አልፎ ተቃዋሚውን ነበር በተንኳሽነት የወቀሰው በእስር ላይ
የነበሩትን የቅንጅት መሪዎች ነበር። ከምርጫ 97 ቀደም ብሎ ጀምሮ ምዕራቡ የአቶ መለስን መንግስት የምስራቅ አፍሪካ ጸረ-
ሽብር ጓደኛቸው እና በኢትዮጵያም የዴሞክራሲ ስርዓት በመገንባት ላይ የሚገኝ መንግስት አድርጎ እንደሚወስድ እና
ተቃዋሚውን አቶ መለስ የሚለውን ተቀብሎ ደካማ አድርጎ ይወስድ እንደነበር እናስታውሳለን።
በግልባጭ ደግሞ ተቃዋሚው አንድነቱን ጠብቆ ነፃ ባልሆነ ምርጫ (አምባገነኖች የሚጠሩት ምርጫ ፍጹም ነፃ አይሆንም)
ተሳትፎ ህዝብ በብዛት ወጥቶ ድምጽ እንዲሰጥ እና ድምጹን እንዲያስከብር ማድረግ ከቻለ እንዲሁም በስልጣን ላይ ያለው
አምባገነን ቢሸነፍ ተቃዋሚው ሰላማዊ አገር አቀፍ እዝባዊ እምቢተኛነት ጥርቶ ገዢው ፓርቲ ሽንፈቱን እንዲቀበል ማስገደድ
የሚችል ሰላማዊ ትግል መምራት ከቻለ ምዕራቡ ወዲያው ተገልብጦ ከተቃዋሚው ጎን ይሰለፋል። የምዕራቡ ጓደኛ ጥቅሙ
ብቻ ነው። ኢትዮጵያን ማንም ቢገዛት ደንታ የለወም።
ዝግጅት ቁልፍ ጉዳይ ነው። በአምባገነኖች ምርጫ የሚሳተፉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ቁምነገር ለመስራት ከፈለጉ ቢያንስ ከሶስት
እና አራት አመቶች ቀደም ብለው ጀምረው መዘጋጀት አለባቸው። ዝግጀታቸው ተቃዋሚ የምርጫ ፓርቲዎች አንድ ሆነው
በመቆም (1) ህዝብን በብዛት ወጥቶ እንዲመርጥ እና ድምጹን እንዲያስከብር መቻል እና (2) ከምርጫ በኋላ ገዢው ፓርቲ
የህዝብ ድምጽ አላከብርም ቢል ተቃዋሚ ፓርቲዎች የህዝብ ድምጽ ማስከበር የሚያስችል አገር አቀፍ ህዝባዊ እምቢተኛነት
መጥራትን እና መምራትን ያካትታል። ነፃ ምርጫ በሚካሄድባቸው አሜሪካ እና እንግሊዝ እንኳን የፓርቲዎች የምርጫ
ዝግጅት አንድት አመት ቀደም ብሎ እንደሚጀመር ማስታወስ አለብን።
ስለዚህ ገዢው እና ተቃዋሚ ፓርቲዎች ያደረጉዋቸውን ዝግጅቶች ስንገመግም ሁለቱ ዋንኛ ጥያቄዎቻችን በምርጫ 97
በአንድ ወገን (1) ህውሃት/ኢህአዴግ የሚፈልገውን ህጋዊነት ለማግኘት የሚያስችለው ዝግጅት አድርጎ ነበርን? የሚል ሲሆን
በሌላ ወገን ደግሞ (2) ተቃዋሚዎች ህዝቡ በነቂስ ወጥቶ ድምጽ እንዲሰጥ እና ድምጹን ከስርቆት እንዲያድን እንዲሁም
በአቶ መለስ የሚመራው ፓርቲ ሽንፈትን እንዲቀበል ማስገደድ የሚያስችላቸው ዝግጅት አድርገው ነበርን? የሚል መሆን
አለበት። ለእያንዳንዱ ጥያቄ ለጥቆ ከምንጎበኘው ዝግጅታቸው መልስ ለማግኘት እንሞክራለን።
(1) የኢህአዴግ የሁለት ባላዎች (የፕላን ሀ እና የፕላን ለ) ዝግጅት፥ በተለይ ከምርጫ 97 በፊት የህውሃት/ ኢህአዴግ መሪ
የነበረው አቶ መለስ ከልቡ የተጸጸተ በመምሰል ለለጋሽ አገሮች በኢትዮጵያ ጠንካራ ተፎካካሪ ተቃዋሚ ፓርቲ አለመኖሩ
የዴሞክራሲን ባህል እድገት ሂደት ጎድቷል እያለ ያደናግራቸው እንደነበር እናስታውሳለን። ስለዚኽ በ1997 ዓ.ም. ተቃዋሚው
በምርጫው ለመሳተፍ መወሰኑን ሲገነዘብ ህውሃት/ ኢህአዴግ ሁለት ዝግጅቶች (ፕላን ሀ እና ፕላን ለ) ማድረግ ጀመረ።
የፕላን ሀ ዝግጅት ግብ ቢቻል ታዛቢዎች ባሉባቸው ከተሞች ተፎካክሮ በማሸነፍ ህጋዊነት ማግኘት ሲሆን የፕላን ለ ዝግጅት
ግብ ደግሞ ምርጫውን በመስረቅ ህጋዊነትን ማግኘት ነበር።
ፕለን ሀን ተጠቅሞ የሚሻውን ህጋዊነት ለማግኘት ህውሃት/ኢህአዴግ ለምርጫ 97 ሁለት አመቶች ቀደም ብሎ ዝግጅት
በመጀመር ለምርጫ የሚያስፈልገውን ገንዘብ፣ የቅስቀሳ ነጥቦች እና የሚመረጡ ሰዎችን አዘጋጅቷል። በልማት መስክ
ህውሃት/ኢህአዴግ በአንድ ወገን በመስኖ፣ በግብርና፣ በፍራፍሬ ምርት እና በመሳሰሉት መስኮች ለኢትዮጵያ ያደረገውን
አስተዋጽኦ ሲያብራራ በሌላ በኩል ደግሞ በእርሻ ተሳክቶልናል የሚሉ ገበሬዎችን በቃለ-ምልልስ ሌት ተቀን በኢ.ቲ.ቪ.
እንዲናገሩ ያደርግ ነበር። እንዲሁም ህውሃት/ኢህአዴግ ኢትዮጵያን የገዛበትን ዘመን ከደርግ ዘመን ጋር በማነጻጸር፣ የምርት
እድገት ከፍ ማድረጉን፣ የዩንቨርስቲ ቁጠር ከ2 ወደ 8 ማድረሱን፣ ተጨሪ የአውሮፕላን ማረፊያዎች መስራቱን፣ 15216 ኪሎ
ሜትር መንገድ መዘርጋቱን፣ የጤና አገልግሎት ሽፋንን ከ35% ወደ 61% ማሳደጉን ሁሉ ሳይታክት በቁጥጥሩ ስር ባለው
ኢ.ቲ.ቪ. ደጋግሞ በማሰራጨት ህዝቡ ህውሃት/ኢህአዴግ የልማት እና የመልካም አስተዳደር መንግስት ነው ብሎ
እንዲመርጠው ለማድረግ ሰፊ የቅስቀሳ ዘመቻ አኪያሂዷል።
ህውሃት/ኢህአዴግ ተፎካክሮ በማሸነፍ የሚገኝን ህጋዊነት ተመራጭ ፕላን በማድረጉ “እንከን የለሽ ምርጫ” የሚለውን ቆቡን
አጥልቆ ወዲያ ወዲህ በማለቱ በርካታ ኢትዮጵያዊ ታዛቢዎችን፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን፣ ለጋሽ አገሮችን ሳይቀር ማደናገር ችሎ
ነበር። ህውሃት/ኢህአዴግ ከተሸነፈ ስልጣን በሰላም ይለቃል የሚል ብዥታ ፈጥሮ ነበር። እነ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ
ማሪያም ህውሃት/ኢህአዴግ ተሸንፎ አልወርድም ካለም ለጌቶቹ (አውሮፓ ህብረት፣ እንግሊዝ እና አሜሪካ) እንነግራለን
እስከማለት ደርሰው እንደነበር እናስታውሳለን። የምረጡኝ ዘመቻውን እና የተደረጉትን ክርክሮች ካስተዋሉ በኋላ የአውሮፓ
 3ህብረት ታዛቢዎች እና የካርተር ማዕከል ሳይቀሩ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሂደት ጥሩ ጅማሬ አስይቷል ሲሉ እንደነበርም
አንዘነጋም። ምርጫው ከመበላሸቱ በፊት በነበረው ሂደት በአቶ መለስ አጭበርባሪ ድራማ የተሳሳቱ ጥቂት አልነበሩም።
እንግዲህ የፕላን ሀ ተልዕኮ በምርጫ ጨዋታ ማሸነፍ ሲሆን የፕላን ለ ተልዕኮ ደግሞ የፕላን ሀ ድራማ ግቡን ካልመታ
ጉልበት በመጠቀም ተቃዋሚውን ጨዋታ አበቃ ማለት ነበር። የፕላን ለ ዝግጅት ስውር ቢሆንም አንዳንድ ኢትዮጵያውያን
ፕላን ለ ቀደም ብለው አስተውለው ነበር። ሰሚ አጡ እንጂ ህውሃት/ኢህአዴግ በጠመንጃ የያዘውን ስልጣን በነፃ ምርጫ
ይለቃል ብሎ ማመን የዋህነት ነው ይሉ ነበር። ስለዚህ በምርጫው ቢሸነፍ እና ስልጣን አልለቅም ቢላችሁ ምን ማድረግ
እንደሚገባችሁ ከወዲሁ ተዛጋጁ ይሉ ነበር። ይሁን እንጂ የምረጡኝ ክርክር እየጋለ እና ህውሃት/ኢህአዴግ በክርክሩ መሸነፍ
ሲጀምር የህውሃት/ኢህአዴግ ፕላን ለ ምልክቶች መታየት ጀምረው ነበር። ፉክክሩ እየጋለ ሲሄድ ተቃዋሚው ያለው የህዝብ
ድጋፍ ወለል ብሎ መታየት በጀመረበት ጊዜ ከህውሃት/ኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣኖች ውስጥ አንዳንዶቹ ከሽክሹክታ
አልፈው በአደባባይ አፍ አውጥተው “ተዋግተን ያገኘነውን በወረቀት አታገኙም” ማለት ጀምረው ነበር።
*እስከዚኽ ድረስ እንዳስተዋልነው ከሆነ በአቶ መለስ የሚመራው ህውሃት/ኢህአዴግ ‘ህጋዊነትን’ ሊያስገኝለት የሚችል
መሰረታዊ ዝግጅት አድርጓል። ተቃዋሚዎችስ? ለጥቀን የምናየው ነው።
የተቃዋሚ ፓርቲዎች እና የሲቪክ ድርጅቶች (ፕላን ሀ ብቻ) ዝግጅት፥
(1) ህብረት መፍጠርን በሚመለከት፥ ተቃዋሚው በመከፋፈሉ አንድ ጠንካራ ከመሆን ፈንታ ብዙ ደካሞች መሆኑን ህዝቡ
በማስተዋሉ በጋራ እንዲሰሩ ለማድረግ “ተባበሩ ወይንም ተሰባበሩ” የሚል ግፊት ማድረጉ ያታወሳል። የሆነው ሆኖ በሐምሌ
ወር 1995 ዓ.ም. በአገር ውስጥ እና ከአገር ውጭ የተደራጁ የፖለቲካ ድርጅቶች በአሜሪካ በዋሺንግተን ዲሲ ተገናኝተው
ለምርጫ 97 የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ህብረት (ህብረት) መሰረቱ። በህብረቱ ውስጥ የነበሩት ዋናዎቹ ድርጅቶች
ከአገር ቤት፥ (1) አማራጭ ኃይሎች፣ (2) የኦሮሞ ብሔራዊ ኮንግረስ (ኦብኮ)፣ (3) የመላ ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት
(መኢአድ)፣ (4) የኢትዮጵያ ዴሞክራሳዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ሲሆኑ ከአገር ውጭ ከነበሩት ፓርቲዎች ውስጥ አውራዎቹ ፥ (1)
የኢትዮጵያ ህዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢህአፓ)፣ (2) የመላ ኢትዮጵያ ሶሻሊስት ንቅናቄ (መኢሶን) እና (3) የትግራይ
ዴሞክራሲያዊ ትብብር (ትዴት/ታንድ) ነበሩ። ዶ/ር በየነ ጴጥሮስ የተመሰረተው ህብረት ሊቀመንበር ሲሆኑ የኢዴፓው ዶ/ር
አድማሱ ገበየሁ እና የኢህአፓው አቶ ፋሲካ በለጠ ም/ሊቀንበር ሆኑ። የተመሰረተው ህብረት በምርጫ ለመሳተፍ መሟላት
አለባቸው የሚላቸውን ቅድመ-ሁኔታዎች ከዘረዘረ በኋላ በአገር ቤት ያሉት የህብረቱ የአመራር አባላት ከመንግስት ጋር
ድርድር እንዲያኪያሂዱ ተስማምቶ ተበተነ። ቅደመ-ሁኔታዎቹ ከሞላ ጎደል የሚከተሉት እንደነበሩ የህብረቱ መግለጫ እና
ግንቦት 7 የተሰኘው የክፍሉ ታደሰ መጽሐፍ ያረጋግጣሉ፥ (1) ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በአዲስ መልክ ከፖለቲካ ድርጅቶች
ተውጣጥቶ እንዲቋቋም፣ (2) የምርጫ አስፈጻሚዎች ገለልተኛ እንዲሆኑ፣ (3) የምርጫ ታዛቢዎች ከአለም አቀፍና ከአገር
ከተውጣጡ ድርጅቶች እንዲመደቡ፣ (4) የመገናኛ ብዙሃን ያለአድልዎ መረጃዎችን እንዲያስተላልፍ እና (5) በውጭ አገሮች
የሚገኙ የህብረቱ አባላት አገር ውስጥ ገብተው በምርጫው የሚሳተፉበት ሁኔታ እንዲመቻች የሚሉና የመሳሰለት ነበሩ።
(2) ህብረቱ በተቋቋመ በአምስተኛ ወር ማለትም በ1996 ዓ.ም. በታህሳስ ወር ማለቂያ መኢአድ እና ኢዴፓ ከህብረቱ
እራሳቸውን በማግለላቸው በአገር ቤት የቀረው ህብረት ብቻውን ከመንግስት ጋር መነጋገር እንደሚፈልግ የሚገልጽ ደብዳቤ
ለጠቅላይ ምኒስትሩ አስገባ። በ1996 ዓ.ም. የካቲት ወር ከኢህአዴግ ጋር ድርድር ተጀመረ። የድርድር ነጥቦች ከፍ ብለው
የተዘረዘሩት አምስት ቅድመ-ሁኔታዎች ናቸው።
ድርድሩ በሂደት ላይ ሳለ ህውሃት/ኢህአዴግ ለህዝብ በሚሰጣቸው መግለጫዎቹ ህብረት ያነሳቸውን አንዳንድ ጥያቄዎች
ለመቀበል የወሰነ እየመሰለ ተደራዳሪዎቹ ሲገናኙ ግን ምክንያት እየፈጠረ በአንድ ወይንም በሁለት ነጥቦች ላይ ብቻ
እንዲወያዩ እንጂ በአምስቱም ቅድመ-ሁኔታዎች ላይ ተወያይተው ድርድሩ ፈጥኖ እንዲያልቅ አላደረግም። እንዲሁም
የድርድር ስብሰባዎችም የተራራቁ እንዲሆኑ በማድረግ በድርድሩ ላይ የሚሳተፈው ህብረት ለምርጫ መዘጋጃ ጊዜ
እንዳያጥርበት መስጋት እስኪጀምር ድረስ የድርድሩን ሂደት ተጓተተ። ህብረት ተበሳጭቶ ድርድሩን ጥሎ እንዲሄድ እና
ለድርድሩ መፍረስ ጥፋተኛዎቹ ተቃዋሚዎች ናቸው ለማለት ታስቦ የተደረገ ይመስላል። አቶ መለስ ይኽን ሲያደርግ ግን
ለህዝብ እና ለለጋሽ አገሮች ድርድር ማድረግን የተቀበለ በመምሰል ነበር።
(3) ከምርጫ 97 8 ወሮች ቀደም ብሎ በ1997 ዓ.ም. መጀመሪያ ግድም በዶክተር ብርሃኑ ነጋ የሚመራ ቀስተ ደመና የሚባል
የፖለቲካ ቡድን መቋቋሙ ተገለጸ። በዚያው ሰሞን ቀስተ ደመና፣ መኢአድ፣ ኢዴአፓ እና የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ሊግ
(ኢዴ.ሊ.) ሆነው አምስት አባል ድርጅቶች ያሉበትን ቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ (ቅንጅት) ፈጠሩ። ኢዴ.ሊ. መሰረቱ
በአብዛኛው ደቡብ ኢትዮጵያ ነው። ቅንጅት ሲቋቋም ለምርጫ ቦርድ ያስገባው ማመልከቻ እድሜው “ ከ1997 ጥቅምት 29
ቀን ጀምሮ እስከ 1997 ዓ.ም. የብሔራዊና ክልላዊ ምርጫ ፍፃሜ ድረስ የጸና ይሆናል” እንደሚል ክፍሉ ታደሰ ግንቦት 7
በሚለው መጽሐፉ ገጽ 196 ላይ ያመለክታል። ስለዚህ ከምርጫ በኋላ የቅንጅት እድሜ አጭር ነው። የቅንጅት እድሜ ማጠር
በስልጣን ላይ ያለው አምባገነን ቡድን ድምጽ ቢሰርቅስ? ሽንፈትን አልቀበልም ቢልስ? የሚሉትን ጉዳዮች ቀደም ብሎ አንስቶ
ሊፈጠር የሚችልን የተራዘመ ድምጽ የማስከበር ሰላማዊ ትግል በህብረት ለመታገል መዘጋጀቱን አያመለክትም።
 4 (4) የተጀመረው ድርድር ሞተ። በህብረት እና በአቶ መለስ መካከል የተጀመረው ድርድር ገና ሳይቋጭ ቅንጅት እንደተቋቋመ
በምርጫው ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ለመሳተፍ መወሰኑን አሳወቀ። አቶ መለስ ያላሰበውን ስጦታ ከማይገምተው አካባቢ
አገኘ። የተጀመረው ድርድር ዋጋ አጣ። አቶ መለስ ለለጋሽ አገሮች ድርድሩ የሞተው በተቃዋሚዎች ነው ሲል አብራራ።
(5) እጩዎች የማቅረብ ሽሚያ የቅንጅት ሌላው ችግር ነበር። ከቅንጅት በርካታ እጩዎች ያቀረቡት ኢዴአፓ እና መኢአድ
ቢሆኑም እነዚህ ሁለት ተፎካካሪ ድርጅቶች ተደራድረው በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍሎች ተመጣጣኝ ድርሻ ያገኙ ሲሆን
በመካከላችው ግን ከፍተኛ ጠብ ነበር። በአዲስ አበባ ውስጥ ባሉት 23 ወረዳዎችና በአማራው ክልል ባሉት የምርጫ
ወረዳዎችም በመካከላቸው ስምምነት አልነበረም። በመካከላቸው የነበረው ግጭትና ውጥረት የቅንጅትን ህልውና አደጋ ላይ
የጣለበት ጊዜ እንደነበር ይታወቃል።
(6) የተቃዋሚው የምርጫ ቅስቀሳ ነጥቦች፥ በክርክሩ ላይ ተቃዋሚው ህበረት እና ቅንጅት በተለይም ቅንጅት ስራ
እንደሚፈጥር፣ የተዛባውን የንግድ አኪያሄድ እንደሚያስተካክል፣ ኢትዮጵያ የባህር በር እንዲኖራት እንደሚታገል እና
የመሳሰሉት ጉዳዮችን አንስቷል። ስለዚህም ቅንጅት የስራ ፈላጊውን፣ የንግዱን እና ኢትዮጵያ ባህር-በር አልባ በመሆኗ
የተበሳጩትን የህብረተሰብ ክፍል ድጋፍ ያገኘ ይመስላል።
(7) የምርጫ 97 ምርጫ ቦርድ መዋቅር፥ በምርጫ 1997 የምርጫ ቦርዱ ሊቀመንበር አቶ ከማል በድሪ ሲሆኑ ቦርዱ 45
ሚሊዮን ብር አካባቢ ባጀት ተመድቦለት በቋሚነትና በጊዚያዊነት 350 ሺ ያህል ሰራተኞች የሚያስተዳድር አካል ነበር።
በ1ምርጫ 97 ምርጫ ቦርዱ አዲስ አበባንና ድሬ ደዋን ጨምሮ 11 አስተዳደራዊ ክልሎች፣ 68 ዞኖች፣ 547 የምርጫ ወረዳዎች
እና 38465 የምርጫ ጣቢያዎች ይመራ ነበር። በውስጥ ጠብ የተነሳ መስሪያ ቤቱን በበላይነት ይመሩ የነበሩት አቶ አሰፋ ብሩ
ከስራቸው በመገለላቸው አቶ ተስፋዬ መንገሻ ምርጫ 97ን በበላይነት መሩ።
(8) በምርጫ 97 ዝግጅት የሲቪክ ድርጅቶች ተሳትፎ፥ ኢሰመጉ፣ የንግድ ምክር ቤት፣ ራ’ዕይ 2020 እና ሌሎች ተሳትፈዋል።
(9) 1997 መስከረም ወር ግድም ለጋሽ አገሮች፥ የውጭ እርዳታ ሰጭ አገሮች ለምርጫው ዝግጅት የገንዘብ አስተዋጽኦ
አድርገዋል። የምርጫ ህግጋት እንዲሟሉ፣ የኤሌክትሮኒክ ሚዲያ እንዲፈቀድ፣ የውጭ ታዛቢዎች ምርጫውን እንዲከታተሉ
አሳብ አቀረቡ። የእርዳታ ሰጭ አገሮች የግል ሬዲዮ መፈቀድን እንደ አንድ የምርጫ መስፈርት ሲያቀርቡ በመስከረም ወር
1997 ዓመተ ምህረት የሬዲዮ ፈቃድ የጠየቁ በሙሉ ማመልከቻ ሞልተው እንዲያስገቡ ኢህአዴግ ማስታወቂያ ያወጣል።
እንደተለመደው አቶ መለስ ሂደቱን በማጓተት ምርጫ እንዲደርስ አደረገ። ጥያቄውም ሳይሟላ ቀረ።
(10) 1997 ግንቦት 7 ቀን (የምርጫው እለት)፥ (1) ህዝቡ በተመደበባቸው የምርጫ ጣቢያዎች በነቂስ ወጥቶ ምኞቱን ገለጸ።
ህዝቡ በመላ ኢትዮጵያ በምርጫው ላይ ያሳየው ጨዋነት፣ ደስተኛነት፣ ሰልፍ ረዘመብኝ፣ ታከተኝ ሳይል የሚጠበቅበትን በስነ
ስርዓት መፈጸሙ በምዕራቡ አለም ምርጫ ታዛቢዎች እና ጋዜጠኞች ሳይቀር ተወደሰ። (2) በምርጫው ቀን ምሽት አካባቢ
የአዲስ አበባ አብላጫ ህዝብ የፖለቲካ ትብብሩን ለተቃዋሚው በመለገስ አዲስ አበባ ከተማን በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ
ህዝብ በመረጣቸው መሪዎቹ እንድትተዳደር አደረግ። (3) ከአዲስ አበባ ውጭም ህዝብ የኢህአዴግን ከፍተኛ ባለስልጣኖች
የፖለቲካ ትብብሩን ለተቃዋሚው መለገሱ ተሰማ። ህዝብ ከስልጣን ካሰናበታቸው ባለስልጣኖች ውስጥ የሚከተሉት
አውራዎቹ ነበር፥ የማስታወቂያ ምኒስትር እና የምርጫው ዋና አዘጋጅ አቶ በረከት ስመዖን፣ የምክር ቤቱ አፈ ጉባኤ አቶ
ዳዊት ዮሐንስ፣ የትምህርት ምንስትሯ ወ/ሮ ገነት ዘውዴ፣ የፍትህ ምኒስትሩ አት ሀርቆ ሃሮያ፣ የመከላከያ ምኒስትሩ አቶ አባ
ዱላ ገመዳ፣ የኦህዴድ መሪው አቶ ጁንዲን።
* የተቃዋሚውን ዝግጅት እንዳስተዋልነው ከሆነ (1) ተቃዋሚው በአጭር ጊዜ ውስጥ ህዝብ በብዛት ህዝብ ወጥቶ
እንዲመርጥ በማድረግ ረገድ ጥሩ ሰርቷል። በተለይ በሚያዚያ 30/1997 ሰላማዊ ሰልፍ የወጣው ህዝብ መጠን ተቃዋሚው
በአጭር ጊዜ ውስጥ ጥሩ የለውጥ መነሳሳት መንፈስ ፈጥሮ እንደነበር ማስረጃ ነው። (2) ተቃዋምው ህዝቡ ድምጹን
ከስርቆት እንዲጠብ ስለማዘጋጀቱ ማስረጃ የለም። (2) ከምርጫ በኋላ አምባገነኑ መንግስት የህዝብ ድምጽ አላከብርም ብሎ
ሽንፈትን አልቀበልም ቢል የህዝብ ድምጽ ማስከበር የሚችል በሰላም ትግል ድስፕሊን የታነጸ በሚሊዮኖች የሚቆጠር የሰላም
ትግል ሰራዊት መገንባታቸው ከፍ ብለን ባየነው ዝግጅታቸው ውስጥ አይታይም። ይኽ የሰላማዊ ትግል ሀሁ ነው።
ተቃዋሚዎች ያን ሃቅ የጨበጡት አይመስልም። (4) በአምባገነን አገሮች በሚካሄዱ ነፃ ያልሆኑ ምርጫዎች ተሳትፈው
እራሳቸውን ከአምባገነን አገዛዝ ነፃ ለማውጣት የሚታገሉ ተቃዋሚ የምርጫ ፓርቲዎች የግድ ሊኖራቸው የሚገባው የአሳብ
እና የድርጅት ህብረት አይታይም። ለምሳሌ፥ ህብረቱን ብንመለከት በሰላማዊ ትግል የሚያምኑ በአገር ቤት ተመዝግበው
በሚታገሉ ህጋዊ ፓርቲዎች እና በትጥቅ ትግል በሚያምኑ በአገር ቤት ባልተመዘገቡ የፖለቲካ ድርጅቶች መካከል የተመሰረተ
መሆኑ በራሱ መሰረታዊ ችግር እንደሚኖረው መገንዘብ አያዳግትም። በትግል ስልቶች እና በህጋዊነት ጉዳዮች ላይ ሳይወያዩ
የተመሰረተ የነ ቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ አይነት ነበር ህብረቱ። ይኼን አይነት ቤት ማንንም አያድነም። ብዙም
ሳይቆይ ይፈርሳል። በመሆኑም ህብረቱ በተቋቋመ በአምስተኛ ወሩ ማለትም በ1996 ዓ.ም. በታህሳስ ወር ማለቂያ መኢአድ
እና ኢዴፓ ከህብረቱ እራሳቸውን አገለሉ። በተጨማሪ በቅንጅትም ውስጥ ጠንካራ የአሳብ እና የድርጅት አንድነት
አልነበረም። በቀረው ህብረት ውስጥም ተመሳሳይ ችግር ነበር። ስለዚህ ተቃዋሚው ከተወሰኑ አመቶች ቀደም ብሎ
 5ለዚጋጅባቸው ከሚገቡት አራት ጉዳዮች ውስጥ ህዝብን ለለውጥ በማነሳሳት በብዛት ወጥቶ እንዲመርጥ ማድረግ በሚለው
ጉዳይ ላይ ጥሩ ስራ የሰራ ሲሆን በቀሩት የሰላማዊ ትግል ግንባሮች ግን ምንም አልሰራም ነበር ማለት ይቻላል። የሚከተሉት
የምርምር እና ግምገማ ክፍሎችም ይኽን ያረጋግጣሉ።
ክፍል (2)፥ ምርጫ 97 - ከምርጫ ማግስት (ግንቦት 8) እስከ 1997 ሰኔ ወር ሁከት ፍጻሜ
*ይኽ ጊዜ በአንድ ወገን ህውሃት/ኢህአዴግ ስልጣን ከጁ የወጣ መስሎት የተደናገጠበት፣ አምባገነናዊ ባህሪውን ገሃድ
በማውጣት ከገባበት ማጥ ለመውጣት የታገለበት እና ደጋፊዎቹን ያረጋጋበት ሲሆን በሌላ ወገን ደግሞ ተቃዋሚው የአቶ
መለስን ምርጫ ስርቆት (ፕላን ለ) ለመከላከል የሚያስችለው ዝግጅት አለማድረጉ፣ ግራ መጋባቱ እና እስከ ግንቦት 7 ቀን
ድረስ ጨብጦት ከነበረው አጥቂነት ሚና ወደ ተከላካይነት መሸጋገር መጀመሩ የታየበት ነበር። ለጥቆ የምናያቸው መረጃዎች
በዚህ ጊዜ ከሆኑት፣ ከተደረጉት እና ከተፈጸሙት ውስጥ የሚከተሉት ዋናዎቹ ነበሩ።
(1) 1997 ግንቦት 8 ቀን (በምርጫው ማግስት) የህውሃት/ኢህአዴግ ፕላን ለ ተንቀሳቀሰ። አቶ መለስ ምርጫን የጸጥታ ጉዳይ
በማስመሰል የአስቸኳይ ጊዜ ወታደራዊ መተዳደሪያ ትዕዛዝ መሰል ህገ መንግስታዊ መብቶችን የሚገድብ ህገ ወጥ መግለጫ
ሰጠ። መግለጫው ካዘላቸው ትዕዛዞች እና መመሪያዎች ውስጥ የሚከተሉት ከፊሎቹ፥ (ሀ) በአዲስ አበባ መሰብሰብ እና
ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ እንደማይቻል፣ (ለ) ወታደራዊ ዕዙ በቀጥታ በእሱ ቁጥጥር ስር መሆኑን፣ (ሐ) የከተማው የሲቪል
አስተደዳር ፀጥታ ከወታደራዊው እዝ ጋር ተባብሮ እንዲሰራ መደረጉን፣ (መ) የምርጫውን ውጤት በሚመለከት በአዲስ
አበባ ደረጃ መሸነፉን እና በፌዴራል ደረጃ ማሸነፉን የሚገልጹ ነበሩ።
የአቶ መለስ መግለጫ በምርጫ ከተሸነፈ አምባገነን መንግስት የሚጠበቅ ነበር። ሽንፈትን ያለመቀበል መግለጫ ነበር።
በፍራቻ ለመግዛት ፍላጎቱን የገለጸበት መግለጫ ነበር። ለዚህ መድሃኒቱ የምርጫ ጉዳይ የጸጥታ ጉዳይ አለመሆኑን ገልጾ
የህዝብ ድምጽ ካላከበርክ ህዝብም ገዢነትህን አያከብርህም የሚል ምላሽ በመስጠት የህዝብ ድምጽ ማስከበር የሚችል
ህዝባዊ ሰላማዊ ትግል መጥራት ነበር። በዝግጅት ክፍል እንዳስተዋልነው ግን ተቃዋሚው ይኽን አይነት ሰላማዊ ትግል
ለመጥራት እና ለመምራት ዝግጅቱም ልምዱም አልነበረውም። ህውሃት/ኢህአዴግ ፕላን ለን አንቀሳቀሰ። ተቃዋሚው ግን
ቀደም ብሎ ያዘጋጀው የራሱ ፕላን ለ ስላልነበረው በዝምታ ተዋጠ።
(2) ከሳምንት በኋላ ግንቦት 16 ግድም ተቃዋሚው ምርጫው መጭበርበሩን እና ሰብዓዊ መብቶችም መረገጣቸውን
የሚገልጹ መግለጫዎች ማውጣት ጀመረ። በዚህ ረገድ፥ (ሀ) ቅንጅት - ግንቦት 16 ቀን 1997 ዓ.ም. በ139 የምርጫ
ጣቢያዎች ወከባ መፈጸሙን፣ የምርጫ ካርድ መሰረቁን፣ ታዛቢዎች መባረራቸውን አስታወቀ። (ለ) ህብረት - በምርጫው
ላይ እንዲገኙ የላካቸው ታዛቢዎች እንዳይገኙ ተደርገው በአብዛኛው ጣቢያዎች ምርጫው ያለታዛቢ መካሄዱን፣ ከፍተኛ
ቁጥር ያላቸው የድምጽ መስጫ ወረቀቶች አስቀድመው ምልክት ተደርጎባቸው መገኘታቸውን፣ ኮሮጆዎች ከድምጽ መስጫ
ጊዜ በፊት ሞልተው መገኘታቸውን፣ ድምጽ ተሰጥቶ ካበቃ በኋላ ኮሮጆዎች መዘረፋቸውን፣ ኮሮጆዎች በመጓጓዝ ላይ ሳሉ
በመንገድ ላይ ትክክለኛ የህዝብ ድምጽ የሆነውን ዘርግፎ ማቃጠልና በምትኩ የኢህአዴግ ምልክት በያዘ ድምጽ መተካቱን፣
ድምጽ የያዙ ኮሮጆዎች በግለሰቦችና በባለ ስልጣኖች ቤት እንዲያድሩና እንዲቀመጡ መደረጋቸውን ዘረዘረ። (ሐ) ኦፌን -
የኦሮሞ ፌዴራሊስት ንቅናቄም በየምርጫ ጣቢያዎች የተመደቡትን ታዛቢዎቻችንን የገዢው ፓርቲ ደጋፊዎች እና ታጣቂዎች
ስላባረሩዋቸው እነዚህ ተግባሮች በተፈጸሙባቸው ዞኖች መሳተፍ አልቻልንም ሲል ቅሬታውን አቀረበ። (መ) ኦብኮ - የኦሮሞ
ብሔራዊ ጉባኤ ደግሞ ከምርጫው በፊትና በኋላ 13 አባላቱ እንደተገደሉበት መግለጫ አወጣ። በርካታ አባላቱ በሐረር ቀይ
መስቀል መጠለላቸውን አሳወቀ። እንዲሁም በምእራብ ሸዋ፣ በባሌ ሮቢ ወረዳ፣ በአርሲ ዞን ኢተያ ወረዳ፣ እና በአዲስ አለም
ምርጫ ክልል በአባሎቹ ላይ አሰቃቂና ዘግኛኝ ድብደባ እንደደረሰባቸውና በርካታ አባሎቹ አካባቢያቸውን ለቀው እንዲሄዱ
መደረጋቸውን በማስረጃ እያስደገፈ በሰፊው ገለጸ። በተጨማሪ (ረ) የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች (ኢሰመጉ)፣ የውጭ አገር
ታዛቢዎችና የውጭ አገር ሰብአዊ መብት ድርጅቶች እጅግ የሚዘገንኑ ተመሳሳይና የከፉ ሁኔታዎችን ዘገቡ።
(3) ኢህአዴግ በተሸነፈባቸው አካባቢዎች ምርጫው መጭበርበሩን አስታወቀ።
(4) ቅንጅት የሰላም ትግል አማራጭ ነው አለ፥ ከምርጫው በኋላ ውጥረቱ እየተጋጋመ ሳለ “ገዢው ፓርቲ ህገ ወጥ
እንቅስቃሴውን በአስቸኳይ አቁሞ ለህዝብ ትክክለኛ የድምጽ ውሳኔ እራሱን ማዘጋጀት ካልቻለ፣ ህዝቡ ማንኛውንም
በሰላማዊ ትግል መዕቀፍ ውስጥ የሚገኝ የትግል ስልቶችን ተጠቅሞ መብትና ጥቅሙን ለማስጠበቅ ከዛሬ ጀምሮ ዝግጁ
መሆን አለበት” ሲል ቅንጅት መግለጫ አወጣ። ቅንጅት ሰላማዊ ትግል ቢጠራም ቀደም ብሎ ለደጋፊዎቹ በድስፕሊን የታነጸ
የሰላም ትግል ስልጠና እንዳልሰጠ እናውቃለን። ጥሪው ቀደም ብሎ በፕላን የተቀየሰ እና በዝግጅት የተደገፈ አልነበረም።
(5) 1997 ሰኔ ወር ድምጽ የማጣራት ስምምነት ተደረሰ፥ (ሀ)ተቃዋሚ እና ኢህአዴግ ተስማሙ። (ለ) ድምጽ የሚያጣራው
እና ውስኔ የሚሰጠው አካል ኢህአዴግን፣ ተቃዋሚውን እና የምርጫ ቦርድን ያካተተ እንዲሆን ተወሰነ። (ኢህአዴግ ህጋዊ
በሆነ መንገድ ድምጽ የሚሰርቅበት እድል ተሰጠው ማለት ነው።) (ለ) የውጭ ታዛቢዎች የማጣራቱን ሂደት በቅርብ
እንዲከታተሉ ተወሰነ። (መ)በዚህ አካል ውሳኔ ላይ ቅሬታ ያለው ለዳኝነት ዘርፍ ቅሬታውን ማቅረብ ይችላል ብለው
ተስማሙ። (የዳኝነት ዘርፉም በአቶ መለስ የሚታዘዝ መሆኑ ይታወቃል)። ስለዚህ በተቋቋመው ቦርድ ውስጥ ተቃዋሚው 2
 6 ለ 1 በሆነ ድምጽ እንደሚሸነፍ ግልጽ ነው። ተቃዋሚው በዚህ አይነት መንገድ ድምጽ እንዲጣራ ስምምነት ውስጥ መግባቱ
አምባገነኖች በምርጫ ጊዜ ብቻ ሳይሆን በማጣራት ጊዜም ድምጽ እንደሚሰርቁ ከመዘንጋት የመነጨ ነው።
(6) በቁጥር (4) የታዘብነው አልቀረም። ድምጽ የማጣርቱን ሂደት ተከትሎ ድጋሚ ምርጫ ተደረገና ግንቦት 7 ቀን የተሸነፉ
የኢህአዴግ ባለስልጣኖች እንደገና ተመረጡ። የማጣራቱን ሂደትና ውጤት አስመልክቶ የአውሮፓ ህብረት ከተቃዋሚዎች፣
ከኢህአዴግና ከምርጫ ቦርድ የተቋቋመው የቅሬታ ሰሚ ቦርድ፣ ተቃዋሚዎች ካቀረቧቸው ቅሬታዎች 80% ውድቅ ሲያደርግ
የኢህአዴግ ግን 87% ድምጽ ድጋፍ አገኙ። ስለዚህ ለኢህአዴግ የሚጠቅሙ ብዙ ቦታዎች ድጋሚ ምርጫ እንዲደረግ
ተወሰነ። በመሆኑም ተቃዋሚው ግንቦት 7 ቀን ካገኘው ድል ውስጥ የተወሰነውን ለኢህአዴግ ለገሰ ማለት ነው። ተቃዋሚው
ከማጣራቱ ምንም እንደማይገኝ ሲረዳ ከማጣራት ሂደት መውጣቱን ገለጸ። ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ አይነት ነው።
(7) የሰኔው ሁከት በድንጋይ እና በጥይት ንግግር ተጀመረ፥ ከሰላማዊ ትግል እውቀት እና ስልጠና ማጣት የተነሳ
የተቃዋሚው ደጋፊዎች የጀመሩት ድንጋይ ውርወራ ኢህአዴግበለጋሾች ዘንድ ቆስቋሽ ሳይመስል ነገር ግን ሰላማዊ ትግሉን
ለመምታት የሚመኘውን ቀዳዳ ከፈተለት። ተቃዋሚው በአዲስ አበባ ያልተደራጀ የሰላም ትግል ሰራዊቱን በፍጥነት ማጣት
ጀመረ። ተቃዋሚው ሰላማዊ ትግል ለመምራት ምንም ድርጅታዊ ዝግጅት እንዳልነበረው ወለል ብሎ መታየት ጀመረ።
በመንግስት ቁጥጥር ስር ያለውን የዜና አውታር ተቃዋሚው እንዳይጠቀም ታገደ። ስለዚህ ተቃዋሚው ትግሉን የሚመራበት
የግል ጋዜጣ ስላልነበረው ለህዝብ መመሪያ እና መግለጫ ይሰጥ የነበረው በአሜሪካ እና በጀርመን ሬዲዮ ጣቢያዎች እና
በኢትዮጵያ ይታተሙ በነበሩ የግል ጋዜጣዎች (ነፃ ፕሬስ) ነበር። ከነፃ ፕሬስ ውስጥ ደግሞ የተወሰኑት አስጩኸው በሚል
የተጋነነ እና አሳሳች ዜና በማሰራጨት ጎጂ ስራ ላይ ተሰማርተው ነበር። ይኽ ሁሉ ቀደም ብሎ ሊታሰብበት ይገባ ነበር።
ተቃዋሚው ቀደም ብሎ ፕላን የተደረገ ሰላማዊ ትግል ማድረግ ላይ አልነበረም። ትግሉ ግብታዊ ነበር። አደጋ ነው።
(8) በሰኔ ወር የተፈጠርውን የፖለቲካ ሁከት አስመልክቶ የአውሮፓ ህብረት እንዲህ ሲል ዘገበ፥ ”እናቶች ይጮሃሉ፣ ወደ ስራ
ለመሄድ ከቤቱ የወጣ ወደ ቤቱ ለመመለስ ይጣደፋል፣ አዲስ አበባ ከባድና ቀላል መሳሪያ በታጠቁ የፌዴራል ፖሊሶች
ተወራለች፣ በየአቅጣጫው የጥይት ድምጽ ይሰማል፣ ግርግሩን ተከትሎ የንግድ ሶቆች ተዘግተዋል፣ ወጣቶች በፌዴራል ፖሊስ
መኪና እየታፈሱ ይሄዳሉ፣ የግል መኪኖች በፍጥነት ወደ ግል መደበቂያቸው ይጣደፋሉ። ………።”
(9) በዚህን ወቅት (ሀ) የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ተማሪዎች “የህዝብ ድምጽ ይከበር” ማለት ጀምረዋል። ከግንቦት 29 ቀን
ጀምሮ የዩንቨርስቲ ተማሪዎች በጅምላ እየታፈሱ ወደ እስር ቤት ተወሰዱ። የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ተማርዎችን ጭነው
በኮተቤ ኮሌጅ በኩል የሚሄዱ መኪናዎች የሚጓዙባቸውን መንገዶች ህዝቡ ቀደም ብሎ በድንጋይ እና በግንዶች ዘጋ። የኮተቤ
ኮሌጅ ተማሪዎች ለአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ተማሪዎች የማበረታቻ ድምጻቸውን ይቸራሉ። ለፖሊሶቹ ህፍረት እንዲሰማቸው
የሚያደርጉ መልዕክቶችን ያሰማሉ። ፖሊሶች በህዝብና ተማሪዎች ላይ ተኩስ ከፍተው አንዲት ሴትና አንድ የኮሌጅ ተማሪ
ሲገደሉ ሌሎች ሰባት እንደቆሰሉ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ ሰኔ 28 ቀን 1997 ዓመተ ምህረት ባወጣው በ84ኛው
ዘገባ ገጽ 1 ላይ ዘገበ (ክፍሉ ታደሰ፣ ግንቦት 7 ገጽ 114)። .
(10) ሰኔ 1 ቀን 1997 ታክሲ ነጂዎች ስራ አቆሙ፥ የአዲስ አበባ ታክሲ ነጂ ሰራተኞች ለ5 ቀን ስራ አቆሙ። በዚህ ምክንያት
ብዙ ሰው ስራ መሄድ አልቻለም። በግል መኪናው የሚጓዘውም ለጸጥታ ሲል ከቤቱ ተከተተ። ብዙ ባንክ ቤቶች ግልጋሎት
አይሰጡም። የሚሰጡትም በዝቅጠኛ አቅም ነበር። ሁከቱን ተከትለው የንግድ ሱቆች ለሶስት ቀኖች ዘጉ።
(11) በዚህ ሁከት ውስጥ በፖሊሶች ላይ ድንጋይ መወርወር በምላሹ ደግሞ ተኩሶ መግደል በየቦታው ተፈጸመ። የከተማ
መመላለሻ አውቶቢሶችን በድንጋይ መቀጥቀጥ የከተማ መጓጓዣ እንዳይኖር አደረገ። በምላሹ የጅምላ አፈሳ ተፈጸመ።
* ወጣቱ ከታጠቀ ኃይል ጋር በድንጋይ መነጋገር መጀመሩ ሰላማዊው ትግላቸው ከቁጥጥራቸው መውጣት መጀመሩን
ያመለክታል። ድንጋይ ከመለስተኛ ቁስል እስከ ግድያ የሚያደርስ መሳሪያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። ንብረት ማውደሚያ
መሳሪያም ሊሆን ይቻላል። ግድያ እና ንብረት ማውደም ደግሞ ሰላማዊ ትግል አይደለም። ከዚያም ባሻገር ለአምባገነኖች
የሚመኙትን ቀዳዳ ይከፍትላቸዋል። ድምጽ ማስከበር የመብት ማስከበር ጉዳይ ሆኖ ሳለ በድንጋይ ድምጽ ለማስከበር
መሞከር ለአምባገነኖች የመብትን ጉዳይ ወደ ጸጥታ ጉዳይ እንዲለውጡት እና ሰላማዊ ትግሉን እንዲመቱት እድል
ይሰጣቸዋል። ሰላማዊ ትግሉ ከመቱት አምባገነኖች በፍርሃት መግዛት ይጀምራሉ። ሰላማዊ ትግል እንደገና አገግሞ እስኪነሳ
ድረስ አመቶች ሊወስድ ይችላል።
(12) ሆስፒታሎች፥ ሰኔ 1 ቀን ጳውሎስ ሆስፒታል እርዳታ ከተደረገላቸው 46 ሰዎች ውስጥ 10 ወዲያው ሞቱ። ሁኔታው
በሌሎች ሆስፒታሎችም ተመሳስይ ነበር። የሚዘገንን አቆሳሰልና ያሟሟት ሁኔታዎች ተዘግበዋል። የህውሃት/ኢህአዴግ
ሹማምንት እንደ ወራሪ ገዢዎች ያልታጠቀውን ወጣት ግንባር ግንባሩን ብላችሁ ግደሉ የሚል ትዕዛዝ የሰጡ ይመስል ነበር።
አቶ መለስ እና የሚመራው መንግስት ህዝብን አሸብረው እና አስፈራርተው ለመግዛት ወስነዋል።
 7(13) እስር ቤቶች፥ ሰኔ 1 ቀን ከአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ተማሪዎች መታፈስ ጋር በተያያዘ እስራቱ በስፋት መካሄድ ጀምሯል።
ከአዲስ አበባ ውጭ በተለይ በገጠሮች ከምርጫው ማግስት ጀምሮ እስራት አልተቋረጠም። በእስረኛ ማጎሪያነት
ከተመረጡት ቦታዎች የሚከተሉት ጥቂቶቹ ነበሩ፥ የአዲስ አበባ ከርቸሌ፣ ከአዲስ አበባ ወጣ ብሎ ደግሞ ዝዋይና ሸዋ ሮቢ፣
በወሎ ጨሪሳ ካምፕ፣ በሐረርጌ የሁርሶ ጦር ማሰልጠኛ ካምፕ፣ በወለጋ ደዴሳ፣ በጎጃም ብር ሸለቆ፣ በወሎና ሸዋ መካከል
እልም ያለ ደን ውስጥ የሚገኘው ደንቆሮ ሸዋ።
(14) የአውሮፓ አንድነት ህብረት፣ የእንግሊዝ እና የአሜሪካ መንግስቶች አቋሞች፥ (1) አለም አቀፍ የሰብአዊ መብት አስከባሪ
ድርጅቶች የአውሮፓ አንድነት ህብረት ለኢህአዴግ የሚለገሰውን የባጀት ድጎማ እንዲቆም ጠየቁ። ጫናቸው እየበረታ ሄደ።
(2) በጠቅላይ ምኒስትር ብሌር የሚመራው የእንግሊዝ መንግስት ለኢትዮጵያ የመደበውን 30 ሚሊዮን ፓውንድ ማገዱን
አስታውቆ እስረኞች እንዲፈቱ ጠየቀ። (3) በፕሬዘዳንት ጆርጅ ቡሽ አስተዳደር የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ቃል
አቀባይ በሰኔ ወር የተካሄደውን ግድያ አላውገዘም። መንግስት ህግንና አለም አቀፍ ድንጋጌዎችን እንዲያከብር፣ የታሰሩት
ፍትሃዊ በሆነ መንገድ እንዲዳኙ ሲል መግለጫ ሰጠ። ተቃዋሚውንም በጸብ ጫሪነትና ተንኳሽነት ወቀሰ ቡሽ። አምባገነን
መለስ ዜናዊ የፈለገውን አገኘ ከአሜሪካ መንግስት።
(15) በሰኔ ማለቂያና በሐምሌ ወር መጀመሪያ ላይ እስረኞች ተለቀቁ።
*እስከዚህ ድረስ እንዳስተዋልነው ተቃዋሚው ባጭር ጊዜ ውስጥ ብዙ ሰርቶ ትልቅ ውጤት አምጥቷል። የዴሞክራሲ ስርዓት
ግንባት ፈጥኖ ማደግ የተሳነው በምርጫ የሚፎካከረኝ ጠንካራ ተቃዋሚ አለመኖሩ ነው እያለ ምዕራቡን ሲያጭበረብር
የነበረውን አምባገነን መለስ ዜናዊ በአጭር ጊዜ አጋልጧል። ለዴሞክራሲ እንቅፋት እሱ እራሱ መለስ የሚመራው
ህውሃት/ኢህአዴግ እንጂ ተቃዋሚ አለመኖሩ እንዳልሆነ ባጭር ጊዜ ምዕራቡ እንዲገነዘብ አድርጓል ተቃዋሚው። ይሁን
እንጂ ከምርጫ ማግስት (ግንቦት 8 ቀን) ጀምሮ እስከ ሰኔው ሁከት ፍጻሜ ድረስ እንዳስተዋልነው ተቃዋሚው የበጀው ነገር
አልነበረም። ብርሃኑ ነጋ የሚመራው ቀስተ ደመናም መስከረም ወር 1997 ነው የተመሰረተው። ህዝቡ በምርጫ 97 እራሱን
አደራጅቶ ለተቃዋሚው ከማቅረቡ ባሻገር ተቃዋሚው በሰላም ትግል ድስፕሊን የሰለጠነ ምርጫን ከስርቆት መጠበቅ
የሚችል አገር አቀፍ የሰላም ትግል ሰራዊት አልገነባም። አገር አቀፍ እምቢተኛነት መጥራት የሚያስችል አቅም መገንባት ቀርቶ
በቅንጅት እና በህብረት እንዲሁም በቅንጅት ውስጥ የነበረው የአሳብ እና የተግባር አንድነት የጸና አልነበረም።
ከህውሃት/ኢህአዴግ የተሰነዘረበትን ፕላን ለ መከላከል አልቻለም። ተቃዋሚው ድምጽ እንዲጣራ ከጠየቀበት ወዲህ እስከ
ሰኔ ወር ድረስ ጉዞው የቁልቁል ነበር። ግራ መጋባት እና ግብታዊነትም ይታይበታል። ስለዚህ በአጭር ጊዜ ትልቅ ድል
ቢያስመዘግብም አቅሙን በትክክል ባለማወቅቁ ተቃዋሚው በተለይ ቅንጅት ያገኘውን ድርጅታዊ እና ፖለቲካዊ ድል ጠብቆ
ትግሉን ማሳደግ አልቻለም።
ምርጫውን ተከትሎ ድምጽ ቢሰረቅስ? መንግስት ሽንፈትን አልቀበልም ቢልስ? የሚሉ የተለያዩ ሁኔታዎች (Scenarios)
ቀደም ብሎ አንስቶ ይኽ ቢሆንስ? ባይሆንስ? . . . (What If … ?) የሚሉ ትንታኔዎች በማድረግ አቅሙን ከግንዛቤ አስገብቶ
ቀዳዳዎችን መድፈን የሚያስችሉ ዝግጅቶችን ማድረግ ነበረበት። ተቃዋሚው ግን ይኽን አይነት ዝግጅት አላደረገም ነበር።
ስየ አብርሃ እና ብርሃኑ ነጋ ሁለቱም ከእስር ከተፈቱ በኋላ ተገናኝተው ስለ ምርጫ 97 ያደረጉት ጭውውትም ይኽን ግምት
በብርሃኑ ነጋ አንደበት ያረጋግጥል። ወደ ሁለቱ ሰዎች ጭውውት እናምራ።
ስየ አብርሃ “ነፃነት እና ዳኝነት” በሚለው መጽሐፉ ገጽ 189 ላይ ከእስር ከተፈታ በኋላ የብርሃኑ ነጋን መጽሐፍ ስለማንበቡ፣
በብርሃኑ መጽሐፉ ውስጥ ”የቅድመ-ግምታዊ አማራጭ እቅዶች (Scenarios and Scenario plans) ጥናት የሚያኪያሂድ እና
አማራጮች የሚያቀርብ የጥናት ቡድን ቅንጅት አቋቁሞ እንደነበር በመጽሐፉ መጠቆሙን ያመለክታል። በአካል ሲገናኙ ስየ
አብርሃ ብርሃኑን ስለዚሁ ጉዳይ ጠይቆት ይኽ ጉዳይ በሂደት ቸል እየተባለ እንደሄደ እና ተቋቁሞ የነበረው ኮሚቴም ጠቃሚ
አስተዋጽኦ እንዲያበረክት አለመደረጉን ከጨዋታቸው እንደተረዳ ስየ አብርሃ ይገልጻል። ቅንጅት ምርጫ እንዳይሰረቅ
ለማድረግ ቀደም ብሎ ዝግጅት አላደረገም ነበር ማለት ነው። ከዚህ የበለጠ መረጃ ከየትም ማምጣት አይቻልም። ስለዚህ
ምርጫ 97ን ሁከት ውስጥ የከተተው እና ግንቦት 7 ቀን የተገኘውን ትልቅ ድል ያባከነው በምርጫ መሳተፍ እና ሰላማዊ
ትግል ማድረግ ሳይሆን የመሪዎቹ የሰላማዊ ትግል አቅም አለመገንባት እና የአመራር ልምድ ማነስ ነበር። ቀደም ብሎ
ተመክሮ ባላቸው ሰዎች ትክክለኛ ፕላን ከተነደፈ እና በቂ አቅም ከተገነባ ምርጫ እና ሰላማዊ ትግል ይሰራሉ።
ቀደም ብለህ ያደራጀኸው በቂ አቅም ከሌለህ ያገኘኸውን ፖለቲካዊ እና ድርጅታዊ ድል ይዘህ ከትግሉ ሜዳ ፈጥነኽ
መውጣት አለበህ። ይኽ የሰላማዊ ትግል ሀሁ ነው። በትግሉ ሜዳ መቆየት ያለብህ ያገኘኸውን ድል ሳታስነጥቅ ተጨማሪ
ድሎች ማግኘት የሚያስችል ተጨማሪ አቅም እንዳለህ እርግጠኛ ስትሆን ብቻ ነው። ስለዚህ በምርጫ 97 ተቃዋሚው
የነበረው የተሻለ አማራጭ በምርጫ ያገኘውን ፖለቲካዊ እና ድርጅታዊ ድል ከነ እንከኑ መቀበል ነበር። የአዲስ አበባን
አስተዳደር ተርክቦ በክብር ፓርላማ በመግባት ለምርጫ 2002 ወዲያውኑ ዝግጅት መጀመር ነበር። ያን ከማድረግ ፈንታ
ተቃዋሚው በሚቀጥለው ክፍል እንደምናነበው ቀደም ብሎ በጀመረው ግራ የተጋባ ጎዳና ወደ ውድቀት መጓዙን ይቀጥላል።
ክፍል (3)፥ ምርጫ 97 - ከሰኔ ወር ሁከት ፍጻሜ እስከ በጳጉሜ የተገለጸው የምርጫ ውጤት
 8 *ከሐምሌ ወር እስከ ጳጉሜ 3 ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ምርጫ 97 በሚከተሉት ውዝግቦች ውስጥ ተጓዘ። ህውሃት/ኢህአዴግ
በተቃዋሚ ላይ የመጨረሻውን ጥቃት ለመክፈት ዝግጅቱን እየጨረሰ ነው።
(1) ህብረትን ዶክተር በየነ ጴጥሮስ እንዲሁም ቅንጅትን ዶክተር ብርሃኑ ነጋ ወክለው ጠ/ም መልስ ዜናዊን ተገናኙ።
ግንኙነታቸው በተናጥል ቢሆንም ለሁለቱም የተሰጣቸው ትዕዛዝ ተመሳሳይ ነበር። “በህጋዊ መልክ የተቋቋመውን የምርጫ
ቦርድ አክብራችሁ ውሳኔውን ካለምንም ቅድመ ሁኔታ ካልተቀበላችሁ ከምርጫው ሂደቱ ውጪ ናችሁ” የሚል ነበር ትዕዛዙ
ባጭሩ። በዚህን ጊዜ ምርጫ ቦርድ በጠራቸው ዳግም ምርጫዎች ቅንጅት በርካታ ወንበሮች መነጠቁን እናስታውሳለን።
(2) ቀጥሎ መወሰድ ስላለበት እርምጃ ለመነጋገር ቅንጅት ሁለት ስብሰባዎች ይደረጋል። የሁለቱ ስብሰባዎች ውሳኔዎች ምን
እንደነበሩ ክፍሉ ታደሰ ላቀረበላቸው ጥያቄ ድርጅታቸውን ቀስተ ደመናን ወክለው የቅንጅት አባል በመሆን በሁለቱም
ስብሰባዎች ላይ የተሳተፉት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ውሳኒዎቹን እንደሚከተለው እንዳብራሩለት ግንቦት 7 በሚለው መጽሐፉ
ገጽ 143 ላይ ይገልጻል፥ (1) በመጀመሪያው ስብሰባ ላይ ምርጫው ውድቅ መሆኑን መወሰኑን እና ከእያንዳንዱ የቅንጅት
አራት አባል ድርጅቶች 10 ሰው ተገናኝተው ቀጥሎ ምን መደረግ እንዳለበት እንዲወስን መደረጉን እና (2) በሁለተኛው
ስብሰባ ላይ ደግሞ ወያኔ ባቋቋማቸው ተቋማት አማካኝነት የትም እንደማይደረስ፣ ምርጫው መጭበርበሩን፣ ለማጣራት
በሚደረግ ሂደት ውስጥ ምንም ነገር ለማምጣት እንደማይቻል ካየን በኋላ ወደ ፍርድ ቤት መሄድም ትርጉም የለውም ተብሎ
ተወስኗል። የቀረው አማራጭ ጉዳዩን ወደ ህዝቡ ወስዶ ህዝቡ የፈለገውን እርምጃ መውሰድ ነው ብሎ ይስማማል ቅንጅት።
(3) ይሁን እንጂ በቅንጅት ምክር ቤት ውስጥ ፓርላማ መግባት እና አዲስ አበባን ተረክቦ ማስተዳደር የሚለውን አቋም
የሚደግፉ እና የሚቃወሙ እንደነበሩ ይታወቃል። ቅንጅት በጠራው ህዝባዊ ስብሰባ ላይ ደግሞ ወጣቱ በትግል መቀጠልን
ሲደግፍ የተቀረው በእድሜ ገፋ ያለው ደግሞ አገሪቷን ትርምስ ውስጥ ከምናስገባ የተገኘውን ድል አሰባስበንና አጠናክረን
የአዲስ አበባን አስተዳደርም ተረክበን ፓርላማ በመግባት ትግላችንን መቀጠል ይኖርብናል የሚል አቋም ነበረው። ያም ሆን
ህዝባዊ ስብሰባ በተወሰኑ የአዲስ አበባ ክፍለ ከተሞች ከ1997 ሐምሌ 26 ማክሰኞ እስከ ነሐሴ 29 ድረስ ከተካሄደ በኋላ
መንግስት ቅንጅት ስብሰባ እንዳያደርግ በማገዱ ከድሬደዋ በስተቀር በቀረው አዲስ አበባ፣ በጎንደር፣ በባህር ዳር፣ በአዋሳ፣
በአርባ ምንጭ፣ በደሴ ውይይቶች አለመደረጋቸውን ክፍሉ ታደሰ ግንቦት 7 በሚለው መጽሐፍ ገጽ 143 ላይ ያመለክታል።
*የጎንደር፣ የባህር ዳር፣ የአዋሳ፣ የአርባ ምንጭ እና የደሴ ህዝብ አቋም ሳይታወቅ በአዲስ አበባ የተወሰኑ ክፍለ ከተሞች እና
በድሬደዋ የተደረጉትን ስብሰባዎች ብቻ በቂ አድርጎ መውሰድ የውክልና ፖለቲካን መርህ “Principle of Constituency
Politics” እንደሚቃረን እና የህዝብ ድምጽ መርገጥ መሆኑን አንባቢ ልብ ይላል። “በትግል መቀጠል” የሚለውም የወጣቱ
አቋም ከሰላማዊ ትግል እውቀት እና ልምድ ማነስ የመነጨ ነው።
(4) 1997 በሐምሌ ህብረት ከሁለት ተከፈለ። በውጭ ከሚኖሩት የህብረት መሪዎች አንዱ የነበሩት ዶ/ር ነገደ ጎበዜ
በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ በመገኘት ምርጫው ከተጭበረበረ እንደ ጆርጂያና ዩክሬን ይሆናል ማለታቸውን ሪፖርተር ጋዜጣ
በ1997 ሐምሌ 3 ቀን መዘገቡን ክፍሉ ታደሰ ግንቦት 7 በሚለው መጽሐፉ ገጽ 143 ላይ ይገልጻል። በመቀጠል በገጽ 143 እና
144 ላይ ደግሞ በዚሁ በሐምሌ ወር 1997 ዓ.ም. በአገር ውስጥ የሚገኙት የህብረት መሪ ዶ/ር በየነ ጴጥሮስ ደግሞ ”እኛ ወደ
ምርጫ ስንገባ (1ኛ) ሙሉ በሙሉ አሸንፈን ፓርላማ ውስጥ መግባት፣ (2ኛ) በጣምራ ስልጣን መያዝ፣ ካልሆነ ደግሞ (3ኛ)
በተቃዋሚነት ፓርላማ ውስጥ ገብተን የትግሉን ደረጃ ከፍ ማድረግ ነው። ፓርላማ አንገባም ብንል ከማንም በላይ
የሚደሰተው ኢህአደግ ነው ” ማለታቸውን ይተርካል።
*በውጭ በሚኖሩት እና በአገር ውስጥ በሚኖሩት የፖለቲካ መሪዎቻችን መካከል ያለውን የምኞት እና የዳኝነት ስክነት
መራራቅ አንባቢ ልብ ይበል። ትናትም ሆነ ዛሬ ተመሳሳይ ነው። ስለ ዩክሬን እና ጆርጂያ ከማውራትህ በፊት አቅምህን
መገመት አለብህ። ሊሆን የማይችል ነገር አደርጋለሁ ብሎ መናገር ወይንም ሊሳካ የማይችል ትግል መጥራት የሰላም ትግል
መሪዎችን ተአማኒነት ያሳጣል። ሰላማዊ ትግሉንም ይጎዳል።
(5) በ1997 ሐምሌ በአቶ ቡልቻ ደሜቅሳ የሚመራው የኦሮሞ ፌዴራል ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄም (ኦፌዴን) ከዶክተር በየነ
ጴጥሮስ ጋር የሚመሳሰል አቋም እንዳለው ለህዝብ አሳወቀ።
(6) በ1997 ነሐሴ ወር የቅንጅት ውይይት በእንጥልጥል ላይ እንዳለ ቅንጅትና ህብረት የአንድነት (ብሔራዊ) መንግስት ጥሪ
አቀረቡ። ይህ የአንድነት (ብሔራዊ) መንግስት ለአንድ አመት ስልጣን ላይ እንደሚቆይና ሌላ ምርጫ እንደሚጠራ አሳብ
አቀረቡ። አቶ መለስ ጥሪውን ወዲያውኑ ውድቅ አደረጉት። በዚህን ጊዜ ኢህአዴግ በአጥቂነት ላይ ስለነበር የአንድነት
(ብሔራዊ) መንግስት ጥሪው ውድቅ እንደሚደረግ መገመት አያዳግትም።
(7) 1997 ነሐሴ 18 ቀን የምርጫ ታዛቢዎች ዘገባዎች ይፋ ተደረጉ። (1) የአውሮፓ ህብረት የምርጫ ታዛቢዎች ዘገባ
በኢትዮጵያ የተካሄደው ምርጫ የአለም አቀፍ መስፈርትን እንደማያሟላ አሳወቀ። (2) የካርተር ማዕከል ደግሞ የማጣራቱ
ሂደቱ ፍትሃዊ እንዳልነበር ቢገልጽም ምርጫው አለም አቀፍ መስፈርትን አያሟላም እስከማለት አለደረሰም።
 9(8) ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ በአውሮፓ አንድነት የቀረበውን ዘገባ እንደማይቀበሉ ከመግለጽ አልፈው በመሄድ የአውሮፓ ህብረት
ምርጫ ታዛቢዎች ቡድን መሪ የሆኑትን አና ጎመዝን የተቃዋሚ ሸሪክ ናቸው የሚል እና ግለሰቢቱን የሚያንቋሽሽ መጣጥፍ
በኢትዮጵያ ሄራልድ ጋዜጣ ላይ አወጡ።
(9) 1997 ነሐሴ 1 እና ጳጉሜ 3 የምርጫ ውጤት ተገለጸ፥ የምርጫ ቦርድ ነሐሴ 1 ቀን ኢህአዴግ ማሸነፉን ገለጾ ጳጉሜ ሶስት
ቀን ደግሞ የምርጫውን ውጤት ይፋ አደረገ። የምርጫ ቦርድ ኢህአዴግ 296፣ ቅንጅት 109፣ ህብረት 52፣ ኦፌዴን 11
የፌዴራል ፓርላማ መቀመጫዎች አግኝተዋል ሲል ዘገበ።
*እርግጥ የድምጽ ማጣራቱን ሂደት ተከትሎ የአቶ መለስ ፍጡር የሆነው ምርጫ ቦርድ በጠራው ድጋሚ ምርጫ ተቃዋሚው
በተለይ ቅንጅት ግንቦት 7 ቀን የነበረው የፓርላማ መቀመጫ ከ109 በላይ እንደነበር እናስታውሳለን። ያም ሆኖ እንኳን ይኽ
ውጤት የሚያሳየን አምባገነኖች በጠሩት ምርጫ ተቃዋሚው መፎካከር እና ከፍተኛ ቁጥር የፓርላማ መቀመጫ ማሸነፍ
እንደሚችል ነው። ስለዚህ ምርጫ 97 ከሞላ ጎደል የሚከተሉትን አስተምራን ሄዳለች ማለት ይቻላል፥
ተቃዋሚው ከምርጫ በፊት፣ በምርጫ ቀን እና ከምርጫ በኋላ አምባገነኑ ተፎካካሪ ገዢ ፓርቲ ህጋዊነትን ለማግኘት
ሊያደርጋቸውን የሚችላቸውን ሁኔታዎች (Scenarios) መርምሮ በቅድሚያ ከተዘጋጀ እና (1) በህብረት በመቆም የአመራር
አንድነት ከሰጠ እና በእጩዎች ማቅረብ ጥያቄ አንድ መሆን ከቻለ፣ (2) በምርጫ ቀን ህዝብ (የመንግስት ሰራተኛው ጭምር)
በብዛት ወጥቶ ማጭበርበር በሚያስቸግር መጠን በ70 እና በ80 ከመቶ በሆነ ድምጽ ተቃዋሚው እንዲመርጥ እና ድምጹን
ከስርቆት እንዲያድን ህዝቡን ካስተማረው፣ (3) በድስፕሊን የታነፀ በሚሊዮኖች የሚቆጠር የሰላማዊ ትግል ሰራዊት ቀደም
ብሎ አደራጅቶ መምራት ከቻለ፣ (4) በሰላማዊ ትግል የታነጹ የአገር ታዛቢዎች በብዛት አስልጥኖ በየምርጫ ጣቢያው
ካሰማራ፣ (5) የምርጫው ግብ የገባቸው እና በሰላማዊ ትግል የታነጹ እጩዎች ካዘጋጀ፣ (6) ከተቻለ የውጭ አገር ታዛቢዎች
በብዛት እንዲገቡ ካደረገ፣ (7) ተቃዋሚው በምርጫ ቢያሸንፍም የመለዮ ለባሹ ተቋሞች ለህገመንግስት ተገዢ ሆነው
ስራቸውን እንደሚቀጥሉ በመጠኑም ቢሆን ማስተማር ከቻል።
ምርጫ 97 ተቃዋሚው የነበረው የተሻለ አማራጭ በምርጫ ያገኘውን ፖለቲካዊ እና ድርጅታዊ ድል ከነ እንከኑ መቀበል
ነበር። የአዲስ አበባን አስተዳደር ተርክቦ በክብር ፓርላማ በመግባት ለምርጫ 2002 ወዲያውኑ ዝግጅት መጀመር ነበር። ያን
ከማድረግ ፈንታ ተቃዋሚው የምርጫ 97ን ሂደት በማጓተት ለጥቀን ወደምናየው የ1998 ጥቅምት እና ህዳር ወሮች ዳግማዊ
ቀውስ ይገባል። ሰላማዊ ትግሉ በድጋሚ ይመታል። አመራሩም ከጨዋታ ውጭ ይደረጋል። የምርጫ 97 ድል ይባክናል።
ክፍል (4)፥ ምርጫ 97 - ከ1998 መስከረም ወር እስከ 1998 ጥቅምት እና ህዳር ወሮች ዳግማዊ ሁከት
* ይህ ጊዜ ህውሃት/ኢህአዴግ ተቃዋሚውን እና ሰላማዊ ትግሉን ይበልጥ በመምታት ከጨዋታ ሊያስወጣቸው በርትቶ
የሰራበት ነበር።
(1) 1998 በመስከረም ወር የአባይ ፀሃዬ ንግግር በዋሽንግተን ዲሲ፥ የህውሃት አባል የሆነው አባይ ፀሃዬ አንድ ቀን
ለደገፋፊዎቻቸው ኢንቨስተሮችን ጨምሮ ሌላ ቀን ደግሞ ለህውሃት አባሎች ስብሰባ አድርጎ የተለያየ መልዕክት አስተላልፎ
ሄደ። (ሀ) ለደጋፊዎቹ፣ ከተቃዋሚዎቹ ጋር ተስማምተን አገሪቱን ወደ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እናስገባለን አለ። (ለ) ለህውሃት
አባሎች ደግሞ፣ ቅንጅት የሚባለውን ከነጭራሹ ደምስሰን እኛ የምንፈልገውን ቅንጅት፣ ታማኝ ተቃዋሚ አድርገን
እናስቀምጣለን አለ። ይህ የአባይ ጸሐይ መልዕክት የተወሰደው ለንግግር ካዘጋጀው ጽሑፍ ገጽ 33 ላይ መሆኑን ክፍሉ ታደሰ
ግንቦት 7 ገጽ 164 ላይ ያመለክታል።
(2) የቅንጅት አመራር ውሳኔዎች መጠለፍ ጀመሩ። ይኽ ሁኔታ በቅንጅት አመራር ውስጥ እርስ በርስ መጠራጠር ፈጠረ።
በቅንጅት ውስጥ መረጃ ለህውሃት/ኢህአዴግ የሚያቀብል ማነው የሚል ጥርጣሬ ተበራከተ።
(3) 1998 መስከረም እስከ ህዳር ወር ውስጥ የቅንጅት ህጋዊ ህልውና ዘመን ማለቁን መንግስት እና ምርጫ ቦርድ አስታወቁ።
ቅንጅት በምርጫ ቦርድ እውቅና ሳያገኝ ቀረ። የቅንጅት ህጋዊነቱ ተሰረዘ። ኢዴአፓ ከቅንጅት ተገነጠለ።
(4) ለ1998 መስከረም 23 ቀን ህብረት ሰላማዊ ሰልፍ ጠራ፡፡ ቅንጅት አበረ። የሰላማዊ ሰልፉ ዓላማ ተሰረቀ የተባለውን
የህዝብ ድምጽ በማስገደድ ሌላ የማጣራት እርምጃ ወይንም ሌላ ምርጫ ለማድረግ ጥርጊያ መክፈት እንደሆነ እና ይህን ሂደት
ኢህአዴግ ካልተቀበለ ወይንም በእርቅ ላይ የተመሰረተ መፍትሄ ካላመጣ በጆርጂያና በዩክሬን እንደሆነው ሁሉ ትግሉ ቀጥሎ
ኢህአዴግ ተገዶ ስልጣኑን እንዲለቅ ይደረጋል የሚል ነው። ይኽ አቋም በውጭ የሚኖሩት የህብረት መሪዎች ነበር።
(5) የ1998 መስከረም 23ን ሰልፍ የጠራው ህብረት 1998 መስከረም 21 ቀን ምክር ቤት (ፓርላማ) መግባት አለመግባት
በሚለው ጉዳይ ላይ ተሰብስቦ 10 ለ 3 በሆነ ድምጽ አለመግባት ብሎ ወሰነ። የዚህ ውሳኔ አስቂኝ ክፍል መግባት የለብንም
ያሉት ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉት ድርጅቶች መሆናቸው ነው። ለመግባት የወሰኑት ዶክተር በየነና ዶክተር መራራ ነበሩ። በዚህ
 10 አይነት ለሁለት አመቶች ያህል አብሮ ሲሰራ የነበረው ህብረት ከሁለት ተከፈለ። በዚህ አይነት በአገር ቤት የሚገኘው ህብረት
ምክር ቤት ለመግባት ወሰነ።
(6) የመስከረም 23ቱን ሰልፍ ቅንጅት ወረሰ። እንደ አንድነት (ብሔራዊ) መንግስት ይህ ሰላማዊ ሰልፍም ቀደም ሲል
የቅንጅት አጀንዳ አልነበረም። የሆነው ሆኖ ቅንጅት ከአባሪነት ወደ ባለቤትነት ተሸጋግሮ የሰላማዊ ሰልፍ ጥሪ ማስተጋባት
ጀመረ። አቶ መለስ የሰልፉ አላማ ህገ-መንግስታዊ ባልሆነ መንገድ መንግስት ለመገልበጥ ነው በማለት ሰልፉ ተከለከለ።
በብዙ አቅጣጫ በችግር የተከበበው ቅንጅት ሰልፍ ቅንጅት ቀደም ብለው ታስቦባቸው ፕላን የተደረጉ ትግሎች በማድረግ
ላይ አልነበረም። ግብታዊ ትግሎች በማድረግ ላይ ነበር። ግብታዊ ትግል አደገኛ ነው።
(7) የመስከረም 23 ቀን ሰልፍ ሲከለከል ቅንጅት ከመስከረም 22 ቀን ጀምሮ በቤት ውስት የመቀመጥ ተቃውሞ ለማድረግ
ወሰነ። ይህ ውሳኔ በተላለፈ በ3 ሰዓት ጊዜ ውስጥ ኢህአዴግ ሊወያይ ፈቃደኛ እንደሆነ ተገለጸ። ውይይቱ እንዲጀመር ለጋሽ
አገሮች ግፊት አድርገዋል። በኢህአዴግና በተቃዋሚዎች መካከል ውይይት እንደሚጀመር እና የተጠራው በቤት ውስጥ
የመቀመጥ አድማው መሰረዙ ይፋ ተደረገ። 1998 መስከረም 22 እሁድ ቀን ተቃዋሚዎችና ኢህአዴግ ለድርድር ተቀመጡ።
ድርድሩ እንደተጀመረ ስለስብሰባው አካሄድ ውይይት ተደረገ። ሁሉም ወገኖች ጋዜጣዊ መግለጫ ከመስጠት ተቆጠቡ።
ኢህአዴግ ለመወያያ ያቀረባቸው 5ቱንም ነጥቦች ህብረቱና ቅንጅት ተቀበሉ። በአንጻሩ ተቃዋሚው ካቀረባቸው ውስጥ
ኢህአዴግ በተወሰኑት ላይ ብቻ ለመወያየት ፈቃደኛ ሆነ። በኢህአዴግ በኩል ቀረቡ የተባሉት አጀንዳዎች፥ (ሀ) ለአገሪቱ
ህገመንግስት፣ ህጎችና ተቋማት ተገዢ ስለመሆን፣ (ለ) ራስን የአመጽ ተልዕኮ አንግበው ከሚንቀሳቀሱ ሃይሎች ማግለል
ወይንም መለየት፣ (ሐ) ህጎችና ተቋማታን ህገ መንግስታዊ ባልሆኑ ስሌቶች ለማፍረስ ከመንቀሳቀስ መታቀብ፣ (መ) የህግን
የበላይነትና ህገ መንግስታዊ ድንጋጌዎችን ስለማክበርና (ረ) የግል ሚዲያ አጠቃቀም
ቅንጅትና ህብረት ለውይይት እንዲያዙ ከጠየቁት ውስጥ የተፈቀደላቸው፥ (ሀ) የመንግስት ሚዲያን አጠቃቀም፣ (ለ)
እስረኞችን ስለመፍታት፣ (ሐ) የፖለቲካ እስራትን ስለማቆም፣ የተዘጉ ጽፈት ቤቶችን በሚመለከትና (መ) በቅርቡ የወጡ
የፓርላማና የማዘጋጃ ቤት ህጎች ነበሩ። ዶ/ር በየነ ጴጥሮስ የተከለከሉ አጀንዳዎች ሲሉ በዕለቱ ያብራሩት፥ (ሀ) የብሔራዊ
አንድነት የሽግግር መንግስት ምስረታ፣ (ለ) የምርጫ ግድፈቶችን ዳግም ማጣራት፣ (ሐ) የምርጫ ቦርድን ብቃቱን ብቻ
ሳይሆን መዋቅሩንም ጭምር መነጋገር፣ (መ) በሰኔ 1 ቀን የተገደሉትን ኢትዮጵያውያንን በሚመለከት ገለልተኛ የሆነ አጣሪ
ቡድን እንዲቋቋም፣ (ረ) የፍትህ ስርዓቱን ነጻና ገለልተኛ እንዲሆን የሚሉና (ሠ) ስምንቱን አጀንዳዎች ለማስፈጸም የሚችል
አንድ ገለልተኛ ተቋም እንዲቋቋም የሚሉ ነበሩ። ድርድሩ እስከ መስከረም 27 ድረስ ከዘለቀ በኋላ ተቋረጠ።
(8) በ1998 ዓመተ ምህረት መስከረም 22 የጀመረው ድርድር መስከረም 27 ከተጨናገፈ በኋላ ቅንጅት ተንጠልጥሎ
የነበረውን ምክር ቤት (ፓርላማ) መግባት አለመግባት የሚለውን ጉዳይ አንስቶ ውይይት ተደረገ። ፓርላማ መግባትን
የሚደግፉም የሚቃወሙም አሳባቸውን አቅርበዋል። ድምጽ ገና አልተሰጠም።
በዚህን ጊዜ አሜራካ አገር በህክምና ላይ የነበሩት ኢንጅነር ሃይሉ ሻውል ቅንጅት ፓርላማ አይገባም በማለት በዋሽንግተን
ዲሲ አሜሪካ በተደረገ አንድ ስብሰባ ላይ መግለጻቸውንና በኢትዮጵያ ህዝብ ተቀባይነት ያጡት አቶ መለስ ዜናዊ
ከስልጣናቸው መልቀቅ አለባቸው ማለታቸውን 1998 መስከረም 10 ቀን የታተመውን ኢትዮጵያዊ ርቪው (Ethiopian
Review, September 18, 2005 ) ገለጸ (ክፍሉ ታደሰ፣ ግንቦት 7፣ ገጽ 211)። በቅንጅት ምክር ቤት የነበረው ውይይት
አልተቋጨም ነበርና ኢንጅነሩ በአሜሪካ ያደረጉት ንግግር በቅንጅት ውስጥ ውዥንብር ፈጠረ። ኢንጂነሩም ህክምናቸውን
አቋርጠው በውይይቱ ለመሳተፍ በመወሰናቸው የተጀመረው ውይይት ውሳኔ ሳይደርስ እንዲጠብቃቸው ደብዳቤ ላኩ።
(9) ቁጥሩ ብዙ የሆነ በውጭ የሚገኝ ኢትዮጵያዊ ኢንጂነር ኃይሉ የወሰዱትን እርምጃ ደገፈ። በውጭ ያለው ኃይል
ተቃዋሚውን በፖለቲካም ሆነ በገንዘብ ይደግፋል። ተደጋጋሚ ሰላሚዊ ሰልፎች በማድረግ ለኢህአዴግ መንግስት ያለውን
ተቃውሞ ግልጿል።
(10) ኢንጂነር ኃይሉ ሻውል አዲስ አበባ እንደ ደረሱ ውይይቱ ቀጠለ። ውሳኔው በቀላል ድምጽ ሳይሆን በ2/3 ድምጽ ማለፍ
አለበት ሲል ቅንጅት ተስማማ። አንድ ቀን ፓርላማ አለመግባት ለሚለው አቋም ሌላ ቀን ደግሞ መግባት ለሚለው አቋም
ተሰጥቶ በመጀመሪያው ቀን አነገባም የሚለው ወገን ለምን ፓርላማ መግባት ትክክል እንደማይሆን ሲያብራራና ሲከራከር
ዋለ። አንገባም የሚለው ወገን በተመደበለት ዕለት ክርክሩን ጨርሶ በምሽት በቅንጅት ምክር ቤት ስብሰባ ፓርላማ አንገባም
የሚለውን አቋም ያራምዱ የነበሩትን ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማሪያም፣ ዶ/ር በፈቃዱ ደገፌ፣ አቶ ግዛቸው ሽፈራውና ሌሎች ሁለት
ሰዎች የነበሩበትን መኪና የኢህአዴግ የስለላ ቡድን አስቁመው በመኪናው ውስጥ በነበሩት የቅንጅት ሰዎች ጭንቅላታቸው
ላይ መሳሪያ ደቅነው ምራቃቸውን እንደተፉባቸውና እንዳስፈራሩዋቸው ተገለጸ። ይህ ሁኔታ በመሰማቱ በሚቀጥለው ቀን
እንግባ የሚለውን አቋም ይደግፉ የነበሩት የቅንጅት ሰዎች ፓርላማ አንገባም የሚለውን አቋም እንደተቀላቀሉና ይህ ሁኔታ
ፓርላማ አንገባም የሚለውን ውሳኔ እንዳጠናከረው በስብሰባው ላይ የነበሩትን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን በምንጭነት
በመጥቀስ በመጽሐፉ አስፍሯል (ክፍሉ ታደሰ፣ ግንቦት 7፣ ገጽ 213-214)።
 11(11) መግባት አለመግባት በሚለው ጉዳይ ላይ ውይይት ከተደረገ በኋላ አስታራቂ አሳብ ቀረበ። ይህ አስታራቂ አሳብ ፓርላማ
ለመግባት የሚከተለው ባለስምንት ነጥቦች ቅድመ ሁኔታ እንዲሟላ ጠየቀ። ቅድመ ሁኔታዎቹ ከተሟሉ ቅንጅት ፓርላማ
እንደሚገባ ወሰነ። እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች በቅንጅት ውስጥ የአሳብ መቀራረብ ሊፈጥሩ እንደሚችልና ከህዝብ ሊመጣ
የሚችለውን ቁጣም ሊያስታግሱ ይችላሉ ተብሎ ተገመተ። ቅድመ ሁኔታዎቹ፥ (1) የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ነፃና ገለልተኛ
መሆኑን በሚያረጋግጥ መንገድ እንደገና ማዋቀር፣ (2) ፍትሃዊ የመንግስት ሚዲያ አጠቃቀምና የግል ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ
እንዲቋቋም፣ (3) የፍርድ ቤት ነፃነትን ማረጋገጥ፣ (4) 1997 ሰኔ 1 ቀን የተካሄደውን ግድያ የሚያጣራ ገለልተኛ አካል
በስቸኳይ እንዲቋቋም፣ (5) የፖሊስ፣ የመከላከያና የደህንነት ተቋማት ከፖለቲካ ገለልተኛ መሆናቸውን ማረጋግርጥ፣ (6)
የፓርላማና የአዲስ አበባ አስተዳደርን በተመለከተ የወጡ አዳዲስ ህጎች እንዲቀየሩ፣ (7) በፖለቲካ አመለካከታቸው የታሰሩ
የፓርቲ አባላትና ደጋፊዎቻቸው እንዲፈቱ፣ የተዘጉ ቢሮዎች እንዲከፈቱ፣ በተቃዋሚዎች ላይ የሚደረገው ወከባ እንዲቆም
እና (8) ከላይ የተጠቀሱትን የሚያስፈጽም ፍትሃዊ አካል እንዲቋቋም
ኢህአዴግ ቅድመ ሁኔታዎቹን ሳይቀበል ቀረ። ከምርጫው ማጣራት ጀምሮ ኢህአዴግ ማጥቃት ላይ ስለነበር ቅንጣትም
እንኳን ማፈግፈግ ወይንም ለተቃዋሚው ምላሽ መስጠት አልፈለገም (ክፍሉ ታደሰ፣ ግንቦት 7 ገጽ 214)። ከቀረቡት 8
ነጥቦች ውስጥ በተለይ 1ኛውን እና 2ኛውን ጉዳዮች ህብረት (ጉዲና እና በየነ) ሊሟሉ የሚገቡ የምርጫ ቅድመ ሁኔታዎች
በሚል ከአቶ መለስ ጋር በመደራደር ላይ ሳሉ ቅንጅት ካለምንም ቅድመ ሁኔታ በምርጫው እንሳተፋለን ማለቱን እና አቶ
መለስ የቅንጅትን አቋም በመጠቀም ህብረት የጀመረውን ድርድር ቸል እንዳሉት እናስታውሳለን።
(12) 1998 በህዳር ወር የኦሮሞ ብሔራዊ ኮንግረስ (ኦብኮ) ከሁለት እንዲከፈል ተደረገ። በህዳር ወር አጋማሽ በኦሮሞ
ብሔራዊ ኮንግረስ ስም 4 ሚሊዮን ህዝብ ለምክር ቤቱ ከመረጣቸው 39 ተወካዮች ውስጥ 37ቱ ከዶክተር መራራ ጉዲና ጎን
ቢቆሙም ምርጫ ቦርድ ከአቶ መለስ በመወገን በኦብኮ ውስጥ መፈንቅለ አመራር ለፈጸመው ቡድን እውቅና ሰጠ። በኦብኮ
ላይ ይኽን አይነት እርምጃ የተወሰደበት ምክንያት ዶክተር መራራ ጉዲና ከህብረቱ እንዲወጣ፣ ከቅንጅት እንዳያብር፣ ወይንም
ደግሞ ከህውሃት ጋር ጸረ-ነፍጠኛ ግንባር እንዲፈጥር በተደጋጋሚ የተሰጠውን ምክር ባለመስማቱ ነበር።
(13) ሁከት 1998 ጥቅምት 22 ቀን በአዲስ አበባ ከተማ ጀመረ።
(ሀ) 1998 ጥቅምት 22 - ጥሩንባ መንፋት፥ ለምሳሌ በአዲስ ከተማ ትምህርት ቤትና አቶቢስ ተራ አካባቢ የአንድ ታክሲ
ጥሩንባ መንፋትን ተከትሎ የተፈጠረውን እንመልከት። ታክሲ ነጂ ጥሩንባ ይነፋል። በአካባቢው የነበሩ መደበኛ ወይንም
የፌዴራል ፓሊስ ለምን ጥሩንባ ትነፋለህ ብሎ ታክሲ ነጂውን ይመታል። በአካባቢ ያሉ የታክስ ነጂ ጉዋደኞቹ ድንጋይ
ይወረወራሉ። ለሚወረወር ድንጋይ የተኩስ ምላሽ ፖሊሶች ይሰጣሉ። በአቅራቢያ ያለ ህዝብ ከፊሉ ከድንጋይና ጥይት መሸሽ
ይጀምራል። መንገዶች ይጣበባሉ። ሰዉ እርስ በርስ እየተደነቃቀፈ የወደቀም እየተረገጠ ይሸሻል። በአካባቢው ረብሻ ተነሳ
ማለት ነው። አካባባዊ ጥሩንባ በጥሩንባ ይሆናል። ፌዴራል ፖሊስ ያገኘውን ይገርፋል። ጥይት ይተኩሳል። በአቅራቢያ
ከነበረው ህዝብ ውስጥ መሸሽን ያለመረጠው የፖሊስን ግርፍ በድንጋይ መመከት ይጀምራል። እንደ አጋጣሚ ሆኖ ይህ
ውዝግብ የተፈጠርው አዲስ ከተማ ትምህርት ቤት አካባቢ በመሆኑ በዚህ ግርግር የአዲስ ከተማ ተማሪዎች ተሳታፊ በመሆን
ከህዝብ ይወግኑና ድንጋይ ውርወራውን ይቀላቀላሉ። ፖሊስ ትምህርት ቤት ቅጥር ግቢ ይገባል። ረብሻውን ሰምተው ወደ
ትምህርት ቤቱ የመጡ ወላጆች ከፖሊስ ጋር ግብ ግብ ይጀምራሉ። ይህ በአውቶቢስ ተራና በአዲስ ከተማ ትምህርት አካባቢ
የተጀመረ ሁከት ወደ ተክለ ሃይማኖት፣ አብነት፣ ጎጃም በረንዳ፣ ሰባተኛ፣ መርካቶ፣ እያለ ወደ ሌሎች አካባቢዎች ተዛመተ።
ፖሊሲ በየአካባቢው ያገኘውን ተበተኑ ማለት ቢጀምርም ሁሌ ትብብር ስለማያገኝ ግጭት ይፈጠራል።
(ለ) 1998 ጥቅምት 22 ቅንጅት- መግለጫ አወጣ፥ ሁከቱ በተነሳበት እለት ጥቅምት 22 ቀን 1998 ቅንጅት ያወጣው
መግለጫ የሚከተሉትን ነጥቦች ያመለክታል፥ (ሀ) መንግስት ህዝቡን ወደ አመጽ እየገፋ መሆኑን አስታወቀ፣ (ለ) መንግስት
ስፍር ቁጥር የሌለው ሰራዊት የፌዴራል ፖሊስ ልብስ አልብሶ ከመደበኛው ፖሊስ ጋር በመቀላቀል በከተማው ውስጥ
ማሰማራቱን ገለጸ፣ (ሐ) ሲቪል የለበሱ ተንኳሽ መልዕክተኞችን በህዝቡና በተማሪው ውስጥ በማሰማራት መንግስት ሴራ
እየጎነጎነ ነው አለ፣ (መ) በመላ አዲስ አበባ በመንግስት እየተገፋ በመስፋፋት ላይ ላለው አመጽ ተማሪዎችን ለጉዳት አጋልጦ
ጥፋቱን በቅንጅትና በህዝብ ላይ ለመላከክ ጥረት እያደረገ ነው ሲል ወንጀለ፣ (ረ) ትግሉ ከትጥቅ ትግል ፍጹም የራቀ ህጋዊና
ሰላማዊ ከመሆኑ ባሻገር ዘር፣ ቋንቋ፣ ሃይማኖት፣ ብሄር የሚለይ ሳይሆን በህዝብ ላይ መጥፎ አስተዳደርን ፣ ሰብዓዊ አፈናን
በሚያኪያሂዱ፣ ዴሞክራሲያዊ መብትና ፍትህ ርትዕን በሚነፍጉ ግለሰቦች ላይ ነው ሲል አብራራ፣ (ሠ) ህዝቡ ቤቱ ሆኖ
ተቃውሞውን እንዲቀጥል መመሪያ ሰጠ።
(ሐ) ኢህአዴግ የቅንጅት መሪዎችን “በአገር ክህደትና ዘር ማጥፋት” ወነጀለ፣ አሰረ፥ የቅንጅት መሪዎች የትግል ጥሪውን
ካደረጉ በኋላ ከቢሮዋቸ፣ ከቤታቸውና ከየመንገዱ እየተለቀሙ ለእስር ተደረጉ። በመጀመሪያ ከታሰሩት ውስጥ የድርጅቱ ዋና
መሪዎች የሆኑት ኢንጅነር ሃይሉ ሻውል፣ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ፣ ዶ/ር በፍቃዱ ደገፌ፣ ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማሪያም፣ ኢንጅነር ግዛቸው
ሽፈራው፣ ሻለቃ ጌታቸው መንግስቴ፣ አርቲስት ደበበ እሸቱ፣ ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማሪያም፣ ዶ/ር ኃይሉ አርአያ፣ ኮ/ል
ታምሩ ጉልላትና ሌሎች ይገኝቡታል። እስሩ በመቀጠል ወ/ት ብርቱካን መዴቅሳ፣ አቶ ሙሉነህ እዮኤል፣ አቶ አባይነህ
ብርሃኑና ሌሎች በርካታ መሪዎች እየታደኑ ለእስር ተደረጉ። 131 የሚሆኑ መሪዎችን፣ ጋዜጠኞችን፣ ነጋዴዎችን፣ የሰብዓዊ
መብት ተሟጋቾችን፣ ተራ ዜጎችን የኢህአዴግ መንግስት በአገር ክህደትና በዘር ማጥፋት ወነጀለ።
 12 (መ) በአዲስ አበባ ሁከት ተባባሰ - በ55 ቦታዎች የኮምሽነሩ ሪፖርት፥ የቅንጅት መሪዎች መታሰራቸው እንደታወቀ ሁከቱ
ይበልጥ ተቀጣጠለ። ታክሲዎች አገልግሎት መስጠት አቆሙ። አውቶብሶች በድንጋይ ተደበደቡ። አብዛኛዎቹ አቶብሶች
መንቀሳቀስ አቆሙ። ህዝቡም መንቀሳቀስ አልቻለም። ሃኪም ቤት የተኛን መጠየቅ፣ አልተቻለም። የሞተን መቅበር፣
አልተቻለም። የአዲስ አበባ ከተማ አገልግሎት ሰጪ ሆቴሎች፣ የመገበያያ ቦታዎች፣ ሱቆች ተዘጉ። ህዝቡ ተቸገረ።
በወታደርና በህዝቡ በተለይ በወጣቱ መካከል በድንጋይና በጠበንጃ መነጋገሩ ቀጠለ። በፒያሳ፣ በአራት ኪሎ፣ በኮከብ
አጽብሃ፣ መገናኛ፣ ካዛንችስና ሌሎች አካባቢዎች ሁከቱ ተቀጣጠለ። የአዲስ አበባ ኮምሺነር ለፓርላማ ባቀረቡት ሪፖርት
በአዲስ አበባ ብቻ በ55 ቦታዎች ሁከት እንደነበር ዘግበዋል። በተለያዩ ቦታዎች በተካሄደው ሁከት የተሳታፊው ብዛትና
የሁካታው ቆይታ ይለያይ እንጂ ባህሪው ተመሳሳይ ነበር። ያልተደራጀውና ያልተዘጋጀው ወጣት እስከ ጥርሱ ከታጠቀ
ወታደርና የፌዴራል ፖሊስ ጋር በድንጋይ ተጋጠመ።
አጋጣሚውን በመጠቀም ኢህአዴግ የግል ጋዜጦች አዘጋጆችን ማደን ስለጀመረ ጋዜጦች መውጣት አቆሙ። በዚያን ጊዜ
ይታተም የነበረው ሪፖርተር የ1998 ዓመተ ምህረት ጥቅምት 29 እትም አንድ አካባቢ የነበረውን ሁከት “ ወጣቶች
‘አትነሳም ወይ’ የሚለውን የትግል መዝሙር እያሰሙ ወደ ቀጨኔ በሚወስደው መንገድ ወደ ኢትዮጵያ ትቅደም ሁለተኛ
ደረጃ ትምህርት ቤት ሲሄዱ በርካታ የፌዴራል ፖሊስ በመሳሪያና በአድማ መበተኛ መሳሪያዎች ታግዘው ከቦታው
ይደርሳሉ።ወጣቶቹ የድንጋይ ውርወራ ትግላቸውን ይጀምራሉ። ሁኔታው ከፌዴራል ፖሊስ ቁጥጥር ውጭ ይሆናል።
የአግዓዚ ክፍለ ጦር በታንክ ታግዞ ወደ ቀጬኔ ይገባል። የገቡት ታንኮች 5 ባለ ጎማ ታንኮች እንደነበሩ፣ ይህ ግጭት እስከ
ሰሜን ሆቴል ከዚያም ከሰሜን ሆቴል ወደ ናይጄሪያ ኢምባሲና ከሰሜን ሆቴል ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን፣ ከቅዱስ
የሐንስ ቤተ ክርስቲያን ወደ አስኮ የሚሄደውን መንገድ ተከትሎ እስከ ፖሊስ ክበብ ድረስ ተቀጣጥሏል (ክፍሉ ታደሰ፣
ግንቦት 7፣ ገጽ 219-220)።”
 (ረ) ዘውዲቱ፣ ራስ ደስታ፣ ጥበቡና ሌሎች ሆስፒታሎች በሁከቱ ሰሞን፥ በወታደር ጥይት በአዲስ አበባ እጅግ በርካታ
ወጣቶች ቆሰሉ። ዘውዲቱ፣ ራስ ደስታ፣ ጥበቡና ሌሎች ሆስፒታሎች በቁስለኞች ተሞሉ። በየሆስፒታሉ በደም የተነከሩ
ልብሶች ተንጠልጥለዋል። ጫማዎች ወዳድቀውል። በየሆስፒታሎቹ ግቢዎች ኡኡታ ነግሷል። ደረት፣ እግር፣ ታፋ፣ ጎን፣
እጅ፣ ቁርጭምጭሚት፣ አናታቸውን የተመቱ በርካታ ነበሩ። ይህንና የፌዴራል ፖሊሶች ዘውዲቱ ሆስፒታል የነበረውን
ህዝብ እንዲወጣ አደረጉ (ክፍሉ ታደሰ፣ ግንቦት 7፣ ገጽ 220)።
(ሰ) ሁከቱ ጋብ ሲል ጅምላ አፈሳ ጀመረ፥ የፌዴራል ፖሊስ ሌሊት በአጥር እየዘለለ ቀን በበር እየገባ ወጣቶችን ያለምንም
ጥያቄና ፍርድ ቤት ትእዛዝ እየለቀመ መውሰድ ጀመረ። ወጣቶች በብዛት ታፈሱ። ወጣቶቹ ወዴት እንደ ደረሱ እንኳ
ለጊዜው ሊታወቅ አይቻልም ነበር። እናቶች ሌሊትም ቀንም እንደ ደርግ ዘመን ማልቀስ ጀመሩ። ልጄን አያችሁ የሚለው
የደርግ ዘመን የእናቶች ጥያቄ ዳግማዊ ትንሳኤ አደረገ።
(ሸ) የእስር ቤት ሁኔታ- ከርቸሌ፣ ዝዋይ፣ ደዴሳ፥ በዚህ ሁከት በርካታ ዜጎች ተገድለዋል፣ በብዙ ሺ የሚገመቱ ታፍሰው ወደ
ከርቸሌ ከዚያ ወደ ዝዋይና ደዴሳ እስር ቤቶች ተጋዙ። እስር ለአዛውንትም ተረፈ። ከነቀመት ደዴሳ 80 ኪሎ ሜትር ሲሆን
ከአዲስ አበባ ደዴሳ ስንት ኪሎ ሜትር እንደሚሆን ግምቱን ለአንባቢ እተዋለሁ። ምግብ የሌለበት ወይንም በቀን አንድ ዳቦ
ብቻ እስረኛው እንዲበላ የተደረገበት ጊዜ ትንሽ አልነበረም።
ክፍል (5)፥ ምርጫ 97 - መደምደሚያ
በአንድ ነፃ ባልሆነ ምርጫ ተሳትፎ አሸናፊ ሆኖ ለስልጣን መብቃት ከተቻለ ተመራጭ ነው። ካልተቻለ ደግሞ
ከምርጫው ለወደፊት ምርጫ የሚበጅ የተሻለ መቆናጠጫ ይዞ መውጣት የምርጫ ፓርቲዎች ሁሉ ግብ መሆን
አለበት። ያንን ማድረግ የምርጫ (የፉክክር) ሀሁ የግድ የሚለው መሰረታዊ ሃቅ ነው። ስለዚህ ከእያንዳንዱ ምርጫ
በፖለቲካ እና በድርጅት ተጠናክሮ መውጣት የምርጫ እና የሰላማዊ ትግል ተቃዋሚ ፓርቲዎች ግብ መሆን
አለበት። የምርጫ ዘመቻ የአንድ ሰሞን ስራ ሲሆን በምርጫ አሸንፎ ለስልጣን መብቃት ግን በምርጫዎች መካከል
ባለው የአራት እና የአምስት አመቶች ረጅም ጊዜ የሚሰሩ ትናንሽ እና ትላልቅ ስራዎች ድምር ውጤት መሆኑ
ለአንድ አፍታም ቢሆን መዘንጋት የለበትም።
በምርጫ 97 ግንቦት 7 ቀን የነፃነት ተስፋ ብልጭ ብሎ ነበር። የዴሞክራሲ ተስፋ ብቅ ብሎ ነበር። በተስፋ ላይ
ተስፋ ይገነባል እንጂ ብልጭ ብሎ የታየ ተስፋ የግድ መጥፋት የለበትም። ተቃዋሚው ድምጽ ለማስከበር
የሚያስችል አንድነት እና የሰላማዊ ትግል አቅም ሳይኖረው የምርጫ ውዝግብ እንዲራዘም ማድረግ አልነበረበትም።
ድምጽ ይከበር ብሎ ባዶ እጁን አደባባይ የወጣው ወጣት በድንጋይ ከጥይት ጋር መነጋገር የጀመረው ስለ ሰላማዊ
ትግል ስልጠና ስላልተሰጠው ነው ቢባል ስህተት አይመስለኝም። በዚህ አይነት የሰላም ትግል ሰራዊት የግድ በ97
ሰኔ ወር እና በ1998 ጥቅምት/ህዳር ወሮች ሁለት ጊዜ መመታት አልነበረበትም።
 13የምርጫ እና የሰላም ትግል መሪዎች የግድ ሙልጭ ብለው ተለቅመው እስር ቤት እስኪገቡ እና ትግሉ ድርግም
ብሎ እስኪጠፋ ድረስ የምርጫ ውዝግብ መራዘም አልነበረበትም። በሚሊዮኖች የሚቆጠር በሰላማዊ ትግል
ድስፕሊን የታነጸ የምርጫ ድምጽ አስከባሪ ሰራዊት ቀደም ብሎ ተደራጅቶ ቢሆን ኖሮ የመሪዎች መታሰር ትግሉን
ከመቅጽበት እንዲጠፋ አይዳርገውም ነበር። ያን አይነት ሰራዊት አልነበረም።
ድምጽ የማስከበር ዘመቻ የሰላማዊ ትግል ዘመቻ ነው። አንድ ዘመቻ መቼ መቆም እንዳለበት የሰላም ትግል
መሪዎች ቀደም ብለው ማወቅ አለባቸው። ማፈግፈግ ሲያስፈልግም መቼ ማፈግፈግ እንደሚያስፈልግ ማወቅ
ያስፈልጋል። ማፈግፈግ አስፈላጊ ሲሆን አለማፈግፈግ ጀግንነት ሳይሆን ስህተት ነው። ወይንም ጀብዱ ነው።
አሊያም ውድቀት እንደ ግብ ተወስዷል ማለት ነው። በምርጫ 97 ቀስተ ደመና የተባለው ድርጅት በተቋቋመ
በ7ኛው ወር ነበር የቅንጅት አባል ሆኖ በምርጫ 97 የተሳተፈው። አልፎም በቅንጅት ውስጥ በነበሩት አባል
ድርጅቶች መካከል የነበረው ስምምነት በጸብ የተበከለ ነበር። በቅንጅት እና በህብረት መካከል የነበረውም
ግንኙነት ጥንካሬ አልነበረውም ነበር። እንዲሁም ህዝቡ እራሱ በራሱ ተነስቶ የለገሰው ትብብር እንጂ ተቃዋሚው
አንድነቱን አጠናክሮ ቀደም ብሎ የገነባው በሚሊዮኖች የሚቆጠር ቀጣይነት ያለው ድምጽ የማስከበር ሰላማዊ
ትግል ማድረግ የሚችል የሰላም ትግል ሰራዊት እንዳልነበረው የሚታወቅ ሃቅ ነው። ይኽ ሁሉ እየታወቀ ድምጽ
የማስከበር ዘመቻው እንዲጓተት መደረጉ ብልህ አኪያሄድ አልነበረም። የሰላማዊ ትግል ዘመቻዎች መጓተት
እንደሌለባቸው የጂን ሻርፕ ባልደረባ ሮበረት ሃርቬይ እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በ1989 ዓመተ ምህረት
በታይናሜን አደባባይ የተፈጸመውን በማስታወስ እንደሚከተለው ይመክረናል፥ “በአደባባይ የወጡት ቻይናውያን
ተማሪዎች የጀመሩት ዘመቻ ከመንግስት በኩል ያስገኘላቸውን መለስተኛ እሺታ እንደ ድል በመቁጠር የመንግስት
ጦር ኃይል በታንክ እና በእግረኛ ወታደር ጥቃት መፈጸም ከመጀመሩ ቀደም ብሎ ዘመቻውን አቁመው መበተን
ነበረባቸው። ያን ሁሉ ታንክ እና ጦር ኃይል ገጥመው ከማለቅ ቀደም ባሉት ሳምንቶች ያገኙትን ድሎች ይዘው
ማፈግፈግ ነበረባቸው” ይለናል። ማፈግፈግ ፍራቻ አይደለም። ጀግኖች ያፈገፍጋሉ። አላንዳች ጥቅም ሰራዊትህን
ማስጨረስ የለብህም። አልፎም ሰላማዊ ትግሉን አታስገድልም። ይኸው ከ1989 ወዲህ እስከ አሁን ድረስ ለ23
አመቶች በቻይና ያን አይነት ሰላማዊ ትግል ገና አልተጀመረም።
ምርጫ 2002፥ የምርጫ 2002 ሽንፈት ምክንያቱ “ህውሃት/ኢህአዴግ የዴሞክራሲ አድማስን ከማጥበቡ እና
እንደተለመደው ድምጽ ከመስረቁ ይልቅ በምርጫ 97 የተገኘው ፖለቲካዊ እና ድርጅታዊ ድል በመባከኑ፣
በምርጫ 97 ድምጽ የማስከበር ዘመቻ ሰላማዊው ትግል ሁለት ጊዜ በመታቱ፣ የተወሰነው ተቃዋሚ አገር ለቆ
በመውጣት ጫካ ግቡ (ትጥቅ ትግል) ብሎ መስበክ በመጀመሩ፣ ህዝብ በተቃዋሚዎች ላይ እምነት በማጣቱ እና
የተወሰነው የህዝብ ክፍል ተቃዋሚዎችን ለመቅጣት ሆን ብሎ ለህውሃት/ኢህአዴግ ድምጽ በመስጠቱም ጭምር
ነው” የሚል ተገቢ ክርክር ማንሳት ይቻላል። ስልጠና ክፍል አምስት አበቃ።

ምርጫ 2007፥ እስከዚህ ድረስ ያገኘችውን ተመክሮዎች ተጠቅማ ኢትዮጵያ በምርጫ 2007 የተሻለ ታሪክ
እንደምታስመዘግብ ጥርጥር የለኝም። ...........

Source:https://www.zehabesha.com/amharic/archives/11243

No comments:

Post a Comment

wanted officials