Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Friday, August 11, 2017

የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ የዋስትና ጥያቄያቸው ውድቅ ተደረገ

) የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ የዋስትና ጥያቄያቸው ውድቅ ተደረገ።
በካቴና ታስረው ፍርድ ቤት የቀረቡትና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር የነበሩት የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ ዋስትና የተከለከሉት ለ5 ጊዜያት ያህል በጉዳዩ ላይ ፍርድ ቤት ከተመላለሱ በኋላ ነው።
በኦሮሚያ ክልል ከተቀጣጠለው ሕዝባዊ አመጽ ጋር በተያያዘ የታሰሩትና በአሸባሪነት የተከሰሱት አቶ በቀለ ገርባ ከወር በፊት ክሳቸው ከአሸባሪነት ወደ ወንጀል ክስ ተደርጎ በፍርድ ቤት መበየኑ ይታወሳል።
የፍርድ ቤቱን ብይን ተከትሎ በጠበቆቻቸው አማካኝነት የዋስትና ጥያቄ ያቀረቡት አቶ በቀለ ገርባ የተለያዩ ምክንያቶች እየተሰጡ የዋስትና ጥያቄያቸው ውሳኔ ሳያገኝ 5 ቀጠሮዎችን አሳልፏል።
አንዴ ዳኞች አልተሟሉም በሌላ ጊዜ አንዱ ዳኛ ታሟል በሚል ሲገፋ የቆየው የዋስትና ጥያቄ ነሀሴ 4/2009 ውሳኔ አግኝቷል።
በዚህም ፍርድ ቤቱ አቶ በቀለ ቢፈቱ አመጽ ያነሳሳሉ በሚል ዋስትና ከልክሏቸው ወደ ወህኒ ቤት እንዲመለሱ ወስኗል።
አቶ በቀለ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ ለመከታተል ከወህኒ ወደ እስር ቤት ሲወሰዱ እንዲሁም ከፍርድ ቤት ወደ ወህኒ ሲመለሱ ሁለት እጃቸውን በካቴና ታስረው ታይተዋል።
ከሳምንት በፊት የኦፌኮ ሊቀመንበር ዶክተር መረራ ጉዲና በተመሳሳይ ሁለት እጃቸውን በካቴና ታስረው ፍርድ ቤት መቅረባቸው ይታወሳል።
አቶ በቀለ ሁለት እጃቸውን ወደፊት አድርገው በካቴና ሲታሰሩ ዶክተር መረራ ደግሞ ሁለት እጃቸውን ወደ ወደ ኋላ መታሰራቸው ይታወሳል።
በሌብነት፣ በነፍስ ማጥፋት፣ በዘረፋ ወዘተ የሚታሰሩ ግለሰቦች ማጅራት መቺዎች ጭምር በካቴና በማይታሰሩበት ሁኔታ ውስጥ እነዚህ ሁለት የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች በካቴና ታስረው መታየታቸው ኢትዮጵያውያንን ማስቆጣቱን በማህበራዊ ሚዲያዎች ከሚሰጡ አስተያየቶች መረዳት ተችሏል።
የዶክተር መረራ በካቴና ታስሮ መታየት በአምቦ፣ወሊሶ በኋላም በጊንጪና ጉደር ተቃውሞ መቀስቀሱ በግልጽ በታየበት አቶ በቀለ ገርባን በተመሳሳይ ሁኔታ ወደ ፍርድ ቤት መውሰድ አነጋጋሪ ሆኗል።

No comments:

Post a Comment

wanted officials