Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Tuesday, August 8, 2017

የመብራትና ውሃ እጥረት በመላ ሃገሪቱ ህዝቡን ለከፍተኛ ችግር እየዳረገ መሆኑን ለኢሳት የደረሱ መረጃዎች አመለከቱ።

የመብራትና ውሃ እጥረት በመላ ሃገሪቱ ህዝቡን ለከፍተኛ ችግር እየዳረገ መሆኑ ተገለጸ

(ኢሳት ዜና –ሐምሌ 27/2009) 
የመብራትና ውሃ እጥረት በመላ ሃገሪቱ ህዝቡን ለከፍተኛ ችግር እየዳረገ መሆኑን ለኢሳት የደረሱ መረጃዎች አመለከቱ።
በመዲናይቱ አዲስ አበባ የኤሌክትሪክና የውሃ እጥረት እየተባባሰ መሆኑን ነዋሪዎች ይናገራሉ።
ንጽህና የጎደለው ውሃ ከመጠቀም ባለፈ ዝናብ እየጠበቁ ውሃ ማጠራቀምና ለእለታዊ ፍጆታ ማዋል እየተለመደ መጥቷል።
በአማራ ክልልም የውሃና የኤሌክትሪክ እጥረቱ በህዝቡ ላይ የፈጠረው አደጋ እየከፋ መምጣቱ ተገልጿል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክፍልም በተለያዩ አካባቢዎች መብራትና ውሃ ከአንድ ወር በላይ እንደሚጠፋባቸው ወኪላችን ያነጋገራቸው ነዋሪዎች ገልጸዋል።የነዳጅ እጥረትም ተከስቷል።
በስልጣን ላይ ያለው መንግስት የሃይል መቆራረጥ እንጂ እጥረት የለም ይላል።
የኤሌክትሪክ ሽያጭ ከጎረቤት ሀገራት ባሻገር እስከ አውሮፓ ድረስ ሊቀርብ የሚያስችል አቅም እየፈጠርን ነው ይላል በሕዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ የሚመራው መንግስት።
ጅቡቲ ሱዳንና ኬንያ መስመር ተዘርግቶላቸው ከኢትዮጵያ መብራት እያገኙ እንደሆነም በመንግስት በኩል በየጊዜው በስኬት ተመዝግቦ እየተገለጸ ይገኛል።
አዲስ አበባ በመብራት እጥረት የተነሳ ነዋሪው ከፍተኛ ችግር ላይ በመውደቁ ደግሞ ጉዳዩን ግራ የሚያጋባ አድርጎታል።
ሰሞኑን የታየው የመብራት እጥረት ከምንግዜውም በላይ የከፋ ሆኖ ህዝቡን ለተለያዩ ችግሮች እየዳረገው ነው ሲሉ የኢሳት ወኪል ያነጋገራቸው ነዋሪዎች ገልጸዋል።
በመደበኛነት በሳምንት ሁለትና ሶስት ቀናት ለ24 ሰአት መብራት ሙሉ በሙሉ የሚጠፋ በመሆኑ ከኤሌክትሪክ ጋር በተያያዘ የንግድ ቤቶች ለከፍተኛ ችግር እየተዳረጉ ናቸው።
መብራት በሚመጣባቸው የተቀሩት ቀናት ለሰአታት የሚዘልቅ የሃይል መቆራረጥ የሚከሰት በመሆኑ በአዲስ አበባ ነዋሪው የገጠመው ችግር የመኖር ህልውናውን እየተፈታተነው እንደሚገኝ ወኪላችን ገልጿል።
የኤሌክትሪክ እጥረቱ ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በዋና ዋና የሀገሪቱ ከተሞች የተከሰተ መሆኑን ለኢሳት የደረሱት መረጃዎች ያሳያሉ።
ሀዋሳ፣ዲላ፣አዳማ፣ባህርዳር፣ጎንደር፣ደሴ፣ነቀምት፣ድሬደዋና ሀረር ተመሳሳይ በሆነ የኤሌክትሪክ እጥረት ነዋሪው ለከፋ ችግር ተጋልጦ ከሚገኝባቸው አካባቢዎች የሚጠቀሱ ናቸው።
በአዲስ አበባ በጸጉር ቤት ስራ ፣በአነስተኛ ማሽኖች የሚንቀሳቀሱ የንግድ ተቋማት፣ሆቴል ቤቶች በአጠቃላይ ኑሮአቸው በኤሌክትሪክ ሃይል ላይ የተመሰረተባቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ሰርተው መብላት እስከሚያቅታቸው እንደደረሱ ለማወቅ ተችሏል።
ችግሩ በአማራ ክልልም ጎልቶ የሚታይ ሲሆን ከአንድ ሳምንት በላይ መብራት የሚያጡ አካባቢዎች ጥቂት የሚባሉ አይደሉም።በባህርዳር ያለው ሁኔታም ተመሳሳይ ነው።
በደቡብ ኢትዮጵያ በከፋ ዞን ቦንጋ ነጋዴዎች የቀን ገቢ ግብር አንከፍልም የሚል ተቃውሞ ሲያስነሱ በምክንያትነት ያስቀመጡት የመብራት እጥረትን ነው።
በአመት ከአንድ መቶ ቀናት በላይ መብራት እየጠፋ ሲመጣም እየተቆራረጠ መሆኑ በንግድ ስራቸው ላይ ከፍተኛ ኪሳራ እያስከተለ በመሆኑ የተጣለባቸውን የቀን ገቢ ግብር መክፈል እንደማይችሉ ነው ለሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ያስታወቁት።
የውሃ እጥረትም በተመሳሳይ የኢትዮጵያውያንን ኑሮ አደጋ ውስጥ ከቶታል።ከውሃ እጥረቱም በተጨማሪ ለጤና ጠንቅ የሆነ ድፍርስ ውሃ በቧንቧ እየመጣ ለከፍተኛ ችግር የተጋለጡ አካባቢዎች እንዳሉ ተጠቁሟል።
ውሃ ለመቅዳት የሚያዙ ሰልፎች እየተለመዱ የመጡ ሲሆን አንድ ጀሪካን ውሃ ከ20 ብር በላይ እየተሸጠ እንደሆነም ተገልጿል።
በሀዋሳ መብራትና ውሃ የነዋሪው ብርቱ ችግር እየሆነ እንደመጣም ነዋሪዎች ይናገራሉ።
ከሃይል መቆራረጥ ሌላ ለቀናት የኤሌክትሪክ አገልግሎት የማይኖር በመሆኑ ችግሩ አሳሳቢ ከሚባል ደረጃ ላይ ይገኛል።
በሀዋሳ እስከ 15 ቀናት ድረስ ውሃ የሚጠፋ እንደሆነ የሚናገሩት ነዋሪዎች የታሸገ ውሃ በመግዛት ለመጠቀም እንደተገደዱም ይገልጻሉ።
በመላ ሀገሪቱ የተከሰተውን የመብራትና የውሃ እጥረት በተመለከተ በመንግስት በኩል መፍትሄ እየቀረበ እንዳልሆነ ይነገራል።
ከዚያ ይልቅ ለጎረቤት ሀገራት የኤሌክትሪክ ሃይል በሽያጭ ለማቅረብ ትኩረት ሰጥቶ እየተንቀሳቀሰ እንደሆነ መረጃዎች ያሳያሉ።
የሀገር ውስጥ ፍላጎት ሳይሟላ ለውጭ ምንዛሪ በሚል የሃይል ሽያጭ መከናወኑ ህዝቡን እያስቆጣ እንደሆነም ለኢሳት የደረሱት ምረጃዎች አመልክተዋል።

No comments:

Post a Comment

wanted officials