Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Saturday, December 1, 2018

ጋናዊው የእግር ኳስ ተጨዋች በኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ እየተፈለገ ነው

ኪንግ ፋይሳል የተሰኘው የጋና ክለብ አጥቂ የነበረው ሞሪሰን ኦሲይ በተቃጠለ ቪዛ አገር ውስጥ በመቆየቱና በሆቴል እዳ በኢትዮጵያ ፖሊስ እየተፈለገ ነው፡፡ ራሱ ተጨዋቹ ለጋና ጋዜጦች እንዳስታወቀው ከኢትዮጵያ ቡና ክለብ ጋር የነበረው ኮንትራት ከተቋረጠ በኋላ ላለፉት ጥቂት ወራት ኢትዮጵያ ውስጥ ይገኛል፡፡ ሲናገርም ‹‹እኔ ወደ ኢትዮጵያ የመጣሁት ኢትዮጵያ ቡና ክለብን ለመቀላቀል ነበር፡፡

ነገር ግን እኔን ያስፈረሙኝ ሰርቢያዊው አሰልጣኝ ወደአገራቸው መመለሳቸውን ተከትሎ ክለቡ ተገቢ ባልሆነ ሁኔታ ክፍያ ሳይፈፅምልኝ ኮንትራቴን ሊያቋርጠው ችሏል›› ብሏል፡፡ ጨምሮም ‹‹በዚህ የተነሳ ሌላ ክለብ እያፈላለኩ እያለ ቪዛዬ ለወራት ያህል ተቃጥሎብኛል፡፡ እንዲሁም የሆቴል ወጪዬንም ክለቡ ሊከፍልልኝ ፈቃደኛ አልሆነም›› ሲል ለጋና ጋዜጦች ዛሬ በፃፈው ደብዳቤ ገልጿል፡፡ በመሆኑም ያረፈበት ሆቴል አስተዳደር እዳውን መክፈል ስላልቻለ ስለሁኔታው ለፖሊስ በማመልከቱ መታሰርን ፈርቶ ከአዲስ አበባ ውጭ ሌላ ከተማ መደበቁን ተጨዋቹ አስረድቷል፡፡
ደብዳቤውን በመቀጠል ‹‹አሁን የኢትዮጵያ ፖሊስ እያሳደደኝ ነው፡፡ አንዳንዴ የምደበቅበት ቦታ እያጣሁ መኪና ስር የማድርበት ጊዜም አለ፡፡ አሁን ከኢትዮጵያ ለመውጣት 3ሺህ 500 ዶላር ለኢምግሬሽን አገልግሎት መክፈል ይጠበቅብኛል፣ ግን ምንም የለኝም›› በማለት አትቷል፡፡
ሞሪሰን ኦሲይ በእስያ ፕሮፌሽናል ሆኖ የተጫወተ ሲሆን ከዚያ ቀደም ሲልም በኸርት ኦፍ ላየንስ ክለብ ተሰልፎ በጋና ፕሪምየር ሊግ ተጫውቶ ነበር፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials