Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Saturday, February 22, 2014

ሰበር ዜና!! አንድነት ለትግል በወጣበት የመድረክ አባል ፓርቲዎች አገዱት


“አንድነትን በመግፋት መድረክን ወደ አክራሪ ብሔረተኛ ስብስብነት ለመግፋት የተደረገ ስልታዊ ውሳኔ ነው” የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ም/ፕሬዝደንት አቶ ተክሌ በቀለ
መድረክ በከፍተኛ ደረጃ የፖለቲካ ውጤት ያመጣ ስራ እየሰራ የሚገኘውን አንድነት ፓርቲን ማገዱ ትዝብት ላይ የሚጥል ውሳኔ ነው፡፡” የአንድነት ፓርቲ ፕሬዝዳንት ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው
የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፌደራላዊ አንድነት መድረክ አባል ፓርቲዎች አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲን ማገዳቸውን ዛሬ የካቲት 15 ቀን 2006 ዓ.ም በተደረገው የመድረኩ 9ኛ ጠቅላላ ጉባኤው ላይ አሳውቀዋል፡፡ በጉባኤው አንድነትን ወክለው የተሳተፉት መካከል የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ም/ፕሬዝደንት እንዲሁም የመድረክ ም/ሊቀመንበርና የውጪ ግንኙነት ኃላፊ ሆኑት አቶ ተክሌ በቀለ ለፍኖተ ነጻነት እንዳስታወቁት የመድረክ አባል ፓርቲ የሆኑት የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስና በፕ/ር በየነ የሚመራው የኢትዮጵያ ማህበረ ዲሞክራሲ ደቡብ ህዝቦች አንድነት ፓርቲ አንድነት ከመድረክ እንዲባረር ቢጠይቁም አረና ትግራይ ለሉአላዊነትና ለዴሞክራሲ አንድነት ላልተወሰነ እንዲታገድ የሚል ሞሽን አቅርቦ በጉባኤው ተቀባይነት አግኝቷል፡፡
አቶ ተክሌ በቀለ የመድረክ አባል ፓርቲዎች አንድነትን ለማገድ የወሰኑባቸው ምክንያዎች አስገራሚ መሆናቸውን ጠቅሰው “የመድረክ አባል ፓርቲዎች አንድነትን ለማገድ የወሰኑት በቅርቡ በተደረገው ጠቅላላ ጉባኤ አንድነት መድረክ ውስጥ ካሉ ፓርቲዎች ጋር ውህደት እንዲፈፀም መወሰኑን፣ አንዳንድ ከፍተኛ አመራሮችም ውህደት እንደሚያስፈልግ በተለያዩ ሚዲያዎች መናገራቸውን፣ የአንድነት ፓርቲ የሀገር ውስጥና የውጪ ሀገር ድጋፍ ሰጪዎች በመድረክ ስም የፋይናንስ ድጋፍ እንዲደረግ ትብብር አያደርጉም በሚልና ከመድረክ ዕውቅና ውጪ መስከረም 19(ሰላማዊ ሰልፉ የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት ህዝባዊ ንቅናቄ የማጠቃለያ መርሀ ግብር ነው፡፡) በአዲስ አበባ ሰላማዊ ሰልፍ አካሂዷል፡፡” የሚሉ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡ አክለውም አንድነትን በመግፋት መድረክን ወደ አክራሪ ብሔረተኛ ስብስብነት ለመግፋት የተደረገ ስልታዊ ውሳኔ ነው ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል፡፡ አቶ ተክሌ መድረክ የራሱን ዕቅድ አውጥቶ በቁርጠኝነት የማይሰራ በመሆኑ አንድነት በተናጠልና ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር የተለያዩ ስራዎችን መስራቱን ጠቅሰው “በተደጋጋሚ ለመድረክ በዕቅድ የተደገፉ እንቅስቃሴዎችን በማቅረብ በጋራ እንዲሰራ ቢጠይቅም ቀና ምላሽ አግኝቶ አያውቅም፡፡ ይልቁኑም የራሱን ጥፋት በአንድነት ላይ ለማላከክ ይሞክራል ” ብለዋል፡፡
ነገ አንድነትና መኢአድ በባህር ዳር የሚያደርጉትን ሰላማዊ ሰልፍ በማስተባበር ላይ የሚገኙት የአንድነት ፓርቲ ፕሬዝዳንት ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው የመድረክን ውሳኔ አስመልክተው ለፍኖተ ነፃነት እንደገለፁት “ መድረክ በከፍተኛ ደረጃ የፖለቲካ ውጤት ያመጣ ስራ እየሰራ የሚገኘውን አንድነት ፓርቲን ማገዱ ትዝብት ላይ የሚጥል ውሳኔ ነው፡፡” ካሉ በኋላ “አንድነት የታገደው ውጤታማ ስራ ስለሰራና በሚሊዮኖች ድምፅ ንቅናቄ እና በተመሳሳይ ስራዎች የተቀዛቀዘውን የሰላማዊ ትግል በማነቃቃት ትግሉን ወደ ህዝብ ስላወረደ ነው፡፡” ብለዋል፡፡ አክለውም “መድረክ ውስጥ ካሉት ፓርቲዎች የተሻለ የፖለቲካ እንቅስቃሴ የሚያደርገው አረና ብቻ ነው፤ የዛሬው ውሳኔ አረናም በቅርቡ የአንድነት እጣ እንደሚገጥመው አመልካች ነው፡፡” የሚል አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ “መድረክ እንደዚህ ያለ እገዳ ከመወሰን ይልቅ አንድነትና አረና የጠየቁትን ውህደት ተቀብሎ ፖለቲካውን በአንድ ላይ ማንቀሳቀሱ ለኢትዮጵያ ህዝብ ከፍተኛ ውጤት እንደሚያስገኝ አንድነት ያምናል፡፡ ስለዚህ መድረክ የወሰነውን ውሳኔ እንደገና አጢኖ የሀገራችንን ፖሊቲካ በውህደት አብረን እንድንመራ እንዲያደርግ በአክብሮት እጠይቃለሁ፡፡” የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል፡
ፍኖተ ነጻነት

No comments:

Post a Comment

wanted officials