Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, June 13, 2019

የኢሳት ቦርድ በድርጅቱ ላይ የሰራውን ጥፋት የሚዘረዝር መረጃ



የኢሳት ቦርድ በድርጅቱ ላይ የሰራውን ጥፋት የሚዘረዝር መረጃ እጃን ገብቷል
በአስራ ሁለት የኢሳት ጋዜጠኞች የተፈረመና ቦርዱ የድርጅቱን ህልውና አደጋ ላይ መጣሉንና ወደ ጥፋት አቅጣጨ መምራቱን በዝርዝር የሚያትትና የእርምት እርምጃ እንዲወሰድ የሚጠይቅ ደብዳቤ እጃን ገብቷል።
አበበ ገላው፣ ሲሳይ አጌና፣ መሳይ መኮንን፣ መታሰቢያ ቀጸላ፣ አፈውርቅ አግደው፣ እንግዱ ወልዴ፣ ወንድም አገኝ ጋሹን ጨምሮ በ12 ጋዜጠኞች የተፈረመው ደብዳቤ የተጻፈው ከሶስት ወራት በፊት ወደ አገር ቤት በተላከው የኢሳት የልዑካን ቡድን አባላት ሲሆን የኢሳት ማኔጅመንት፣ ሰራተኞችና ባለድርሻዎች ባልተሳተፉበትና ባላወቁበት ሁኔታ ያለምንም ጥናትና በቂ ዝግጅት ከተጣለበት ህዝባዊ አደራ ጋር በሚጻረር መልኩ ኢሳት ወደ ኢትዮጵያ እንዲገባ መደረጉ አግባብ አለመሆኑን ገልጿል።
“ይህም እርምጃ ያሳዘነንና የኛ በምንለው ድርጅት ውስጥ የባይተዋርነት ስሜት መፍጠሩን መካድ አይቻልም። ከዛም አልፎ ያለምንም ጥናትና ዝግጅት ፕሮግራሞችን የማጠፍ እና ስቱድዮችን የመዝጋት እቅድ ለብዙዎቻችን ሞራልን የሚነካ ክስተት ነበር፣” በማለት ሰራተኛ የመቀነስና ስቱዲዮችን የመዝጋት እቅድ በቦርዱ አስቀድሞ ታቅዶ እንደነበር ደብዳቤው አመላክቷል::
“ኢሳት ከሚጠበቅበት ደረጃ እጅግ ባነሰ መልኩ የግለሰብ መኖሪያ ቤት በደባልነት እንዲገባ ከመደረጉም በላይ ማንነታቸውን እስካሁን በማናውቃቸው ግለሰቦች የግል አክስዮን ማህበር ሆኖ ተመዝግቧል” ያለው ይሄው ደብዳቤ ምንም አይነት የሚዲያ ልምድ የሌላት ግለሰብ ዋና ስራ አስኪያጅ ሆና እንድትመደብ መደረጉ ኢሳት የገጠሙትን ችግሮች የበለጠ ማወሳሰቡን ጠቁሟል።
“በቦርድ ስም የተወሰደው አግባብነት የጎደለው እርምጃ ኢሳትን ወደሁዋላ ከመመለስ ባሻገር ወሳኝ የሆነው የአዲስ አበባ ስቱድዮ ተጠያቂነት የጎደለው ከደረጃ በታች የወረደ አሰራርም መንገድ መክፈቱን ተረድተናል። የኢሳት አላማ ወደ ጎን ተገፍቶ ለግል ጥቅምና እራስን የመሸጥ እሩጫ በጋራ የቆምንለትን አላማችንን ለማሳካት እንቅፋት ደቅኗል።” በማለት ጋዜጠኞቹ በቦርዱ ላይ ምሬታቸውን ገልጸዋል።
በቅርቡ ከኢሳት የለቀቁ ጋዜጠኞች ኢሳት ለገጠሙት ችግሮች ቦርዱን መወንጀላቸው ይታወሳል። የቦርዱ አባላት የሆኑት እራሴን አጥፍቻለሁ ያለው የግንቦት 7 ከፍተኛ አመራር አዲሱ መንገሻ፣ ዘላለም ተሰማ፣ ሙሉ አለም አዳም፣ አዚዝ አህመድና ነአምን ዘለቀ መሆናቸው ታውቋል። አንዳንዶቹ የኢሳት ጋዜጠኞች የቦርዱን አፍራሽ እንቅስቃሴ ሲቃወሙ እንደ ነበርና ድርጅቱ ነጻ ህዝባዊ ሚድያ መሆን እንደሚገባው ሲሞግቱ እንደ ነበር ለማወቅ ተችሏል።

የደብዳቤውን ሙሉ ይዘት ለማንበብ ከታች ያለውን ተስንፈንጣሪ በመጫን ያንብቡ። እዚህ በመጫን ሙሉውን ያንብቡ

No comments:

Post a Comment

wanted officials