Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Sunday, February 18, 2018

ከዶ/ር አብይ አህመድ ጋር ስሰራ የማልወዳቸው 5 ነገሮች



1. ከዶ/ር አበይ ጋር ከሰራህ ከሌላ ከማንም የስራ ሀላፊ ጋር መስራት አትችልም፤
አብይ በባህሪው የስራ ባልደረባ አይደለም ፤ ወንድም ወይም ጓደኛ ነው ፡፡ አንተ ሃላፊም ሁን ተራ ባለሞያ፣ በተቋሙ ውስጥ ያለው ሰራተኛ 1 ሺም ይሁን 1 መቶ ከሱ ጋር እስከሰራህ ድረስ ያውቅሃል ፡፡ ማወቅ ማለት ደሞ ሰምህን ብቻ አይደለም፡፡ የት እንደምትኖር፣ እንዴት አንደምትኖር ማን እንደሆነክ ፣ ምን እንደሆንክ ያውቃል፡፡ ያስታወሳል ይጠይቅሃል ፡፡ ያስብልሀል ያግዝሃል ፡፡ የአለቃን ትረጉም ይቀይርብሀል፡፡ የመሪነት/leadership ደረጃን ከፍ ያደርግብሀል፡፡ በሆነ ምክንያት ከሌሎች ሰዎች ጋር ልትሰራ ከተገደድክ ሀሉንም ሰው ከሱ ጋር እያወዳደርክ ትሰቃያለህ ፡፡ ደ/ር አብይ ሲከፋህ፣ ሲደክምህ፣ ስትበሳጭ ፊትህ ላይ ያውቃል፡፡ “ዛሬ ደብሮሀል ሒድ ማሳጅ ግባ ቡክ አርጌልሃለው” ይልሀል፡፡ እቺን ትለምድና ከሌላ ሰው እንዴት ተደርጎ…
2. እሱን ለመሆንና ለመምሰል ስትታገል እራስህን ታጣለህ
አብይ በተፈጥሮው ተሰጦ ያለው ሰው ነው ብዬ አምናለው “Charismatic“ የሚባል አይነት ፡፡ ሰዎች አንዲያከብሩትና እንዲከተሉት ማድረግ ለሱ ቀላል ነው፡፡ ብዙ ግዜ እሱን ለመምሰል ሞክሬ ተሰቃይቻለው፡፡ እንደሱ ለመቆጣት ሞክሬ ሰውች ተቀይመውኛል፡፡ አንደሱ ዝቅ ለማለት ሞክሬ ሰዎች ታዝበውኛል፡፡ ሌላው የሚያበሳጨው ነገር ደግሞ ከሱ ጋር ስትሰራ (በተለይ ሀላፊ ቢጤ ከሆንክ) ሰዎች ከሱ ጋር ስለሚያወዳድሩህ አንተ ምንም ነህ፤ ወይ እራስህን አትሆን ወይ እሱን አትሆን በቃ ውዝግብ ብቻ
3. አብይ ስር ስትሰራ የኔ የምትለው ሰአት የለህም
ሌላው ከባድ ነገር ዶ/ር አብይ እረፍት የሚባል ነገር አይገባውም፡፡ እረ እንደውም ያስቀዋል፡፡ ምን ሰረትህ ነው የምታረፈው?? ‘’ስትሞት ታርፋለህ’’ ይልሀል፡፡ አስታውሳለው እሱ የሰራበት 4ቱም (እኔ በቅርበት የማቃቸው) ተቋማት ውስጥ የስራ መውጫ ሰአት ማታ 2 ሰአት ነው፡፡ በዚህም ገና ወደ ተቋማቸው ለመቀጠር ስትመጣ መጀመሪያ የሚነገርህ ነገር ይሄ ነው፡፡ አልፈልግም ካልክ የዛኑ ቀን ትወስናለህ ፡፡ 8 ሰአት ነው እኮ መስራት የሚጠበቅብኝ ካለክ እሱን ለአውሮፓዎቹ (ላደጉት ሀገራት) ንገራቸው ትባላለህ፡፡ እቺ ድሀ አገር 16 ሰአት እየተኛህ 8 ሰአት እየሰራህ አታድግም ይልሀል አለቀ፡፡
4. ከአብይ ጋር ስትሰራ ማናጀር እንጂ ሊደር አትሆንም
በጣም የሚያናድደኝ ነገር ደሞ ቀን በቀን፣ በየሰአቱና በየደቂቃው አዳዲስ ስራዎች ይመጣልህል፡፡ እሱ የሚሰጥህን ስራ በሚፈልገዉ ፍጥነትና ጥራት ማስረከብ እራስ ምታትህ ይሆንብሀል፡፡ የሚገርመው ደግሞ የሰጠህን ስራ ቢሞት አይረሳም፡፡ በ text፣ በስልክ፣ በemail ሲያጨናንቅህ ሳትተኛ ታድራለህ፡፡ እሱ የፈለገው ማንኛውም ባለሞያ ካለ ወንበሩ ድረስ ሄዶ ስራ ይስጠዋል፡፡ አስታውሳለው ከሱ ስር በሀላፊነት ደረጃ የነበርን እኔ እና መሰል ጓደኞቼ ይሄንን በሀሪውን እስክንለምደው ድረስ ተቸግረን ነበር፡፡ አረ እንደውም ለምን አንዲ ታደርጋለህ???……..ሰራተኞቹ እኮ አንተን ቀጥታ ማግኘት ከጀመሩ ለኛ አይታዘዙም ብለነው ነበር፡፡ የሱ መልስ ግን ሰዎችን እራሴ ወርጄ ማየት ስችል ነው ማን ምን አቅም እንዳለው ማየት የምችለው፤ እናንተንም (እኛ ከሱ ስር ያለነውን የስራ ሀላፊዎች ማለቱ ነው) ያወኳችሁ በዚህ መንገድ ነው ፤ ይሄ ቤሮክራሲያችሁን (bureaucracy) ተዉ ብሎ ኩምሽሽ አድርጎናል፡፡ ከሱ ጋር መስራትህ ትረጉሙ የሚገባህ ግን ከሱ አጠገብ የራክ ቀን ነው፡፡ ያኔ አንተ ማልት በብዙ እርቀት ከሌሎች የተሻልክ ሆነህ ትገኛለህ፡፡ ምክንያቱም የምትሰስትው ግዜ የለህም ፣ ያለስራ መቀመጥ ሀጥያት ይመስልሀል ፡፡ እንዴት መስራትም ሆነ ማሰራት እንዳለብህ ታውቃለህ፡፡ በከፍተኛ የስራ ጫና ውስጥ ማለፍ ትችላለህ፡፡ ለነገ የምትለው ስራ የለህም፡፡ በቃ አንተ የህዝብ አገልጋይ ነህ አለቀ፡፡
5. ከሱ ጋር ስትቆይ ገንዘብ የሚባል ነገር ትንቃለህ
እንደው በጋጣሚ ከሱ ጋር ስትሄድ ወይም አንድ ቦታ ተቀምጠህ ፊታችሁ የተቸገረ ሰው ከመጣ አለቀልህ፡፡ የሱም ያንተም ኪስ ባዶ መሆኑ ነው፡፡ እሱ ኪሱን ገልበጦ ያወጣና አንተም አዋጣ/አምጣ ትባላለህ፡፡ ታዲያ በየትኛው ልብህ ነው የምትሰስተው?????…..አንተም ኪስህን ትገለበጣለህ፡፡ በጣም የሚገርመውን ነገር ልንገራችሁ ሲም ካርድ አውጥቶ ስለኩን የሰጠበት ግዜ አለ ብላችሁ ምን ትላላችሁ; (ነገሩ እንዲ ነው፡- ባለፀጋ በሚባሉ ሰዎች መሀል ባጋጣሚ የአንድ ሰው ስልክ ይጠፋል ፡፡ ስልክ የጠፋባቸውም ሰዎች በቦታው ያለች አንድ ምሰኪን አስተናጋጅ ይይዙና አንቺ ነሽ የወሰድሺው ውለጂ ይሏታል፡፡ በቦታው ካሉ ብዙ ሰዎች ውስጥ እሷ ብቻ ተመርጣ ትፈተሻለች፤ ትበረበራለች፡፡ ስልኩ ከየት ይመጣ! በዚህን ግዜ ጉዳዩን ይከታተል የነበረው አብይ ብድግ ብሎ የራሱን ስልኩ አውጥቶ ሌባ ለተባለችው እንስት ስጥት……..ድራማ ይመስላል አይደል; ….እንግዲ እኔ የማውቀው አብይ ይሄ ነው፡፡
የቀድሞ የስራ ልጁ
Babyshow Yikrta

No comments:

Post a Comment

wanted officials