Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Tuesday, March 20, 2018

አረመኔያዊ የጅምላ ጭፍጨፋ ማውገዝ በብጹዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ከሚመራው ከሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ፤



”የወንድምህ የደሙ ድምጽ ከምድር ወደኔ ይጮኻል”ዘፍ 4፤10 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ዱ አምላክ አሜን።
Date: 15-03-2018
Ref. No: 07-0-/2018
የዘር ማጥፋት ዘመቻውን ለማፋጠን በከፍተኛ ፍጥነት በሩጫ ላይ የሚገኘው ራሱን ወያኔ እያለ የሚጠራው የትግራይ ነጻ አውጭ በሀገራችን በኢትዮጵያና በሕዝባችን ላይ ያወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የዘር ማጥፍያ መሠሪያ በማድረግ በደቡብ ኦሮምያ ክልል በቦረና ዞን በሞያሌ ከተማና በአካባቢው በሚገኙ ሰላማውያንና ንጽሀን ዜጎቻችን ላይ የፈጸመውን አረመኔያዊ የጅምላ ጭፍጨፋ ማውገዝ በብጹዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ከሚመራው ከሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ፤
የሰው ልጅ በእግዚአብሔር በጎ ፈቃድና መለኮታዊ ጥበብ በሥላሴ አርአያና ምሳሌ የተፈጠረ ስለሆነ በፈጣሪው ዘንድ የተወደደ ክቡርና ልዩ ፍጥረት ነው በመሆኑም ይህ በሥላሴ አረዓያና አምሳል የተፈጠረ ክቡርና ልዩ የሆነ የሰው ልጅ በግፍ ሲገደል ደሙ ወደ እግዚአብሔር ይጮሃል ገዳዩንም ይከሳል። ”የሰውን ደም የሚያፈሥስ ሁሉ ደሙ ይፈሥሳል ሰውን በእግዚአብሔር መልክ ፈጥሮታልና”ዘፍ9:6።በዚህ አምላካዊ ቃል መሠረት ዛሬ በሐጋራችን በኢትዮጵያ በግፍ የሚገደሉ ወገኖቻችን ሁሉ ደማቸው በከንቱ ፈሥሶ የሚቀር አይደለም እንደ አቤል ደም ወደ እግዚአብሔር ይጣራል። ገዳዮችንም ያሳድዳል። ይህ ክፉ ቀን የማያልፍ እየመሰለው የሐገሪቱን ንጹሀን ዜጎች የሚገድል ዘር አጥፊው ወያኔ ለፍርድ የሚቀርብበት ቀን ሩቅ አይደለም። ከሁሉም በላይ ደግሞ “የተረገምክ ነህ፤ በምድር ላይ ኮብላይና ተቅበዝባዥ ትሆናለህ”ዘፍ 4:12 የሚለው አምላካዊ ቃል ዘር አጥፊውን ወያኔን የሚመለከት በመሆኑ የንጹሀንን ደም በግፍ እያፈሰሰ መቸም ቢሆን ከፍርድ ሊያመልጥ አይችልም።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያንም ከእግዚአብሔር በተሰጣት አምላካዊ አደራ መሠረት መንጋውን ሕዝቧን የመጠበቅና ከሕዝቧም ጎን የመቆም ሀላፊነትና አደራ እንዳለባት ቅዱስ ሲኖዶስ ያምናል ስለሆነም በወገኖቻችን ላይ ግፍ ሲፈጸም ድምጹን ከፍ አድርጎ የጮኻል ጮቋኙን ክፍል ይመክራል ይገስጻል። በመሆኑም በየጊዜው ሳይበድሉ በግፍ የተገደሉትንና እንዲሁም በዚህ ሰሞን በሞያሌ ከተማና በአካባቢው በሚኖሩ በሰላማዊ ንጹሀን ወገኖቻችን ላይ ዘር አጥፊው ወያኔ የፈጸመው አረመኔያዊ የጅምላ ጭፍጨፋና ከቤት ንብረታቸው አፈናቅሎ ከሀገር ያሳደዳቸውን ከ50ሺህ በላይ የሚሆኑ ወገኖቻችን ያሉበትን ሁኔታ ስናስብ እጅግ በጣም መሪር ሀዘን ይሰማናል። ስለሆነም ይህንን የዘር አጥፊውን የወያኔን አረመኔያዊ ተግባር በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስምና ሥልጣን በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ የሚመራው ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ በማውገዝ ከዚህ የሚከተለውን የማጽናኛ መልእክት ያስተላልፋል።
1. በሞያሌ ከተማና በአካባቢው በሚገኙ ሰላማውያን ኗሪዎች ላይ በዘር አጥፊው በግፍ ለተገደሉት ወገኖቻችን በየአቢያተ ክርርስቲያናቱ ጸሎተ ፍትሃት እንዲደረግላቸውና ለተጎዱ ወገኖችም አስፈላጊው እርዳታ እንዲደረግላቸ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪ ያቀርባል፤
2. ቤተ ሰቦቻቸው ለተገደሉባቸውና ከከሀዲው የወያኔ ሠራዊት የጅምላ ጭፍጨፋ አምልጠውና ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው ከከባድ ሀዘን ጋር በስደት ለሚንገላቱ ወገኖቻችን መሪር ኀዘን የተሰማን መሆኑን እየገለጽን በኬንያ መንግሥት፤ ዓለም አቀፍ በቀይ መስቀል ማኅበርና በተለያዩ በጎ አድራጎት ድርጅቶች አስፈላጊው የነፍስ አድን እርዳታ እንዲደረግላቸ ቅዱስ ሲኖዶስ ይጠይቃል።
3. በሞያሌ በተፈጸመው አሰቃቂ የዘር ማጥፋት ግድያ የተነሳ ወደ ኬንያ ለተሰደዱ በብዙ ሺህ ለሚቆጠሩ ወገኖቻችን የኬንያ መንግሥት ለአደረገው መልካም ትብብር ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶ ከልብ እያመሰገነ ለወደፊቱም እንዲህ አይነቱ መልካም ትብብር እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል።
4. በሐገር ውስጥና በመላው ዓለም ለምትገኙ ኢትዮጵያውያን ወገኖች የቀረበ ጥሪ እንደሚታወቀው ሁሉ ዘር አጥፊው ወያኔ ዓላማው የኢትዮጵያን ሕዝብ ተራ በተራ መጨረስ ነው። ስለዚህ በተባበሩት መንግሥታት ሰብአዊ መብት ጥበቃ በዘር አጥፊነት ወንጀል በዓለም አቀፍ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በአስቸኳይ ክስ እንዲመሠረት በያላችሁበት አስፈላጊውን ጥረት እንድታደርጉ በየቀኑ በሚገደሉ ንጹሀን ወገኖቻችን ስም ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ ይጠይቃል።
5. ለኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን የተከበርከው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ ዓለምን ንቀው፤ ከሰው ተለይተው፤በጾምና በጸሎት ተወስነው፤ በሕይወት ዘመናቸው ስለኢትዮጵያና ስለኢትዮጵያ ሕዝብ ሌሊትና ቀን ከእግዚአብሔር ጋር የሚነጋገሩ ገዳማውያን የዋልድባ መነኮሳትን የምንኩስና ልብሳቸውን ለማስወለቅ በማስገደድና መሬት ለመሬት በመጎተት እንዲሰቃዩ በማድረግ የሚፈጸመውን ኢሰባዊ ግፍ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥብቅ እያወገዘ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በአስቸኳይ እንዲፈቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ይጠይቃል።
6. በብዙ ሽህ የሚቆጠሩ ንጹሀን ዜጎችን በሚታወቁና በማይታወቁ የጨለማ እስር ቤቶች አፍኖ በቃላት ሊገለጽ በማይቻል ልዩ ልዩ ጸዋትዎ መከራ በማብዛት አረመኔው ወያኔ የሚፈጸመው ግፍ አልበቃ ብሎ ንጹሀን ዜጎች በግፍ ከጨፈጨፈ በኋላ በተሳሳተ ምረጃ ነው ባማለት መተኪያ በሌለው የሰው ሕይወት ላይ የሚቀልደውን ብሎም የጭቆና አገዛዝ ቀምበርን ለማራዘምና የዘር ማጥፋት ዘመቻውን ለማፋጠን የሚችልበትን አሻንጉሊት የስም ጠቅላይ ሚንሥተር ለማስቀመት በዝግጅት ላይ የሚገኘውንና ሲጀመር ጀምሮ በዘር ማጥፋት ላይ የተመሠረተውን የዘር አጥፊውን የወያኔን የአገዛዝ ቀምበር የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚሸከምበት ትከሻና አቅም ከአሁን በኋላ እንደማይኖረው የሚመለከተው ሁሉ እንዲያውቀው ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪ ያቀርባል።
ስለሆነም የተከበርከው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ! በዘር፤ በፖለቲካ፤ በቋንቋ፤ በሐይማኖትና በተለያዩ ጥቃቅን ነገሮች ሳትከፋፈል የቀደሙ አባቶችህ ያስረከቡህን ታሪክና ጀግንነት መሣሪያ በማድረግና አንድነትህን በማጠናከር የጀመርከውን የነጻነት ትግል ከፍጻሜ እንድታደርስ ቅዱስ ሲኖዶስ የአንድነት ጥሪውን እያስተላለፈ ይህን የመከራ ዘመን እግዚአብሔር እንደጥላ እንዲያሳልፈው ዘወትር በጸሎት እግዚአብሔርን ይለምናል።
“እግዚአብሔር አምላክ የሀገራችንን አንድነትና ሰላም ይተብቅልን”

No comments:

Post a Comment

wanted officials