Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Tuesday, March 18, 2014

የሰማያዊ ወጣቶች በዝግ ችሎት ቀጠሯቸው ለሶስተኛ ጊዜ ተራዘመ

• ዳኛው ጉዳዩ በመደበኛ ፍርድ ቤት እንዲታይ ወስኗል 
• ወጣቶቹ እስር ቤት ውስጥ በደል እየደረሰባቸው እንደሆነ ገልጸዋል
ባለፈው አርብ መጋቢት 5/2006 ዓ.ም ለዛሬ መጋቢት 9 2006 ዓ.ም ተቀጥለው የነበሩት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ቀጠሯቸው ለሶስተኛ ጊዜ ተራዘመ፡፡ ሶስት ሰዓት ላይ ይካሄዳል ተብሎ ዘግይቶ አራት ሰዓት ላይ በጀመረው ችሎት፤ የውጭ አገር ኤምባሲ ተወካዮችን ጨምሮ ከ60-70 የሚሆን ህዝብ ችሎቱን ለመከታተል ተገኝቶ የነበር ቢሆንም ከጠበቃው ውጭ ማንም ሰው ወደ ችሎቱ እንዳይገባ ተከልክሏል፡፡ ችሎቱ ሰፋ ባለ ክፍል ይደረጋል ተብሎ ተጠብቆ የነበር ቢሆንም አራት በአራት በሆነ የዳኛ ማሞ ሞገስ ጠባብ ቢሮ ውስጥ ተካሂዷል፡፡ ከጠበቃው ውጭ ማንም ሰው እንዳይገባ ተከልክሏል፡፡
ምንም እንኳ ፖሊስ ያቀረበው አዲስ ማስረጃ ባይኖርም ዳኛው ጠበቃው ያቀረቡትን ጠበቅ ያለ መከራከሪያ ተንተርሶ ታሳሪዎቹን ከመፍታት ይልቅ ወደ መደበኛ ፍርድ ቤት እንዲያመራ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ ዳኛው ፖሊስ ነገ ክሱን በመደበኛ ፍርድ ቤት ማቅረብ ካልቻለ ታሳሪዎቹ አቤቱታ ማቅረብ እንደሚችሉ ገልጸዋል፡፡
ባለፈው ቀጠሮ በ4 ቀን ውስጥ ቀሪ መረጃና ተጨማሪ ተጠርጣሪዎችን ለመያዝ ተጨማሪ ጊዜ ያስፈልገኛል ያለው ፖሊስ አሁንም 14 ቀን ተጨማሪ ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ መርማሪው ባለፈው በተሰጠው የ4 ቀን ቀጠሮ ምንም ተጨማሪ ማስረጃም ሆነ ተባባሪ ሰው ሳይዝ ነው የቀረበው፡፡ ይሁንና አሁንም 20 ያህል ተጠርጣሪዎችን ማሰር እንደሚፈልግ፣ ተጨማሪ መረጃ ማሰባሰብ እንደሚያስፈልገውና ታሳሪዎቹ ከተፈቱ ሌላ ተጨማሪ ወንጀል ስለሚሰሩ እንዳይወጡ ጠይቋል፡፡ ፖሊስ 20 ያህል ተጠርጣሪዎች እንዳሉ ከታሳሪዎች ቃል መቀበላቸውን ቢገልጹም ተጠርጣሪዎቹ ምንም አይነት ቃል መግለጻቸውን ከጠበቃው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
ጠበቃው አቶ አለሙ ገዴቦ ፖሊስ ለሁለተኛ ጊዜ መረጃ ለማሰባሰብና ተጠርጣሪ ያላቸውን ተጨማሪ ሰዎች ለመያዝ ከበቂ በላይ ጊዜ እንዳገኘ፣ በመሆኑም ወጣቶቹ በራሳቸውም ሆነ በሌላ ቀለል ባለ ዋስ መፈታት እንዳለባቸው ተከራክረዋል፡፡ ተጨማሪ መረጃም ሆነ ሌሎቹን መያዝ ካስፈለገው ታሳሪዎች ወጥተው መፈለግና ማጣራት እንደሚችሉ ገልጸዋል፡፡ ወጣቶቹ አሁንም ቢሆን በኃላፊነት ላይ የሚገኙና በጎ ስነምግባር ያላቸው በመሆኑ ቢፈቱ ምንም አይነት ወንጀል እንደማይሰሩ ተከራክረዋል፡፡
የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ወጣት ብርሃኑ ተክለያሬድና የአደረጃጀት ኃላፊ ጌታነህ ባልቻ ባለፈው መብታቸው እየተጣሰ መሆኑን ተናግረው ምርመራ እንደሚደረግና እንደሚቀረፍ ተነገር የነበረ ቢሆንም ምንም ነገር ችግር እንዳልተቀረፈ ተናግረዋል፡፡ ይባስ ብሎም አሁንም ፖሊስ ሴቶቹን ሌሊት እየጠራ እንደሚያስፈራሩዋቸውና ሀኪም ቤት መሄድ እንዳልተፈቀደላቸው አመልክተዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ታሳሪዎቹ ምንም አይነት ወንጀል ባልሰሩበት በየወቅቱ ቀጠሮ የሚያራዝሙት ባላቸው የፖለቲካ አመለካከት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በዝጉ ጅሎት በተደረገው ክርክር እንዳይገቡ የተከለከሉት የፓርቲው ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት ሂደቱ አግባብ አለመሆኑንና ሆን ተብሎ የወጣቶቹ ስነ ልቦና ለመጉዳት ታስቦ የተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የፓርቲው የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ ወጣት ዮናታን ተስፋየ በበኩሉ ዳኛው ባለበት ጫና በራሱ መወሰን ባለመቻሉ ወደ መደበኛ ፍርድ ቤት እንዳዞረው በመግለጽ የሂደቱን ህገ ወጥነት ገልጸዋል፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials