Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, August 16, 2018

“የወልቃይትን ጉዳይ ብንሸሸው፣ ብንሸፋፍነው ሊተወን አልቻለም” ሲሉ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ተናገሩ።


“የወልቃይትን ጉዳይ ብንሸሸው፣ ብንሸፋፍነው ሊተወን አልቻለም” ሲሉ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ተናገሩ።
( ኢሳት ዜና ነሐሴ 07 ቀን 2010 ዓ/ም ) የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ይህን ያሉት፤ ከአማራ ክልል ምሁራን ጋር በባህር ዳር ከተማ እያደረጉት ባለው ውይይት ላይ ጉዳዩን አስመልክቶ ለተሰነዘረባቸው ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡ ነው።
ከተሳታፊ ምሁራኑ መካከል አንዱ “የወልቃይት ሕዝብ የአማራ ማንነታችን ይከበር በማለት ፌዴራል መንግስት ድረስ እየሄደ ጥያቄ ሲያቀርብ ከላይ የሚሰጠው ምላሽ ግን ‘’ህወሓትን ጠይቁ” የሚል ነው። በወልቃይት ጉዳይ የብአዴን አቋም ምንድነው?” በማለት ነው ጥያቄ የሰነዘሩት።
ርዕሰ መስተዳድሩ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ለጥያቄው በሰጡት ምላሽ በወልቃይት ጉዳይ ብአዴን እስካሁን ዋነኛ ጠያቂ እንዳልነበረም አምነዋል።
“ይሁንና የወልቃይትን ነገር ብንሸሸው፣ብንሸፋፍነው፣ ምን ብንለው መሄጃ የለንም” ያሉት አቶ ገዱ “መፍትሔው ያ ህዝብ የፈለገውን ማንነት እንዲመርጥና እንዲከበርለት ነጻነት መስጠት ነው” ብለዋል።
“የወልቃይት የማንነት ትያቄ ከአማራ ህዝብ ጥያቄ በላይ የሌላም ሆኗል” ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ ሕዝቡ በነጻነት እንዲወስን ከማድረግ የተሻለ መፍትሔ እንደሌለ አስረድተዋል። ወልቃይት የትግራይ ክልል ግዛት ነው የሚል አቋም የሚያራምደው ህወሃት፣ ከአሁን በኋላ በወልቃይት ጉዳይ ምንም አይነት ጥያቄ መነሳት የለበትም በማለት ደጋግሞ እያስጠነቀቀ ይገኛል።
አንዳንድ የድርጅቱ አባላትና ካድሬዎች ሳይቀሩ “ከእንግዲህ ወልቃይትን የሚነካ ካለ ለጦርነት ዝግጁ ነን” እያሉ በማህበራዊ ሚዲያው መቀስቀስ ጀምረዋል። በማንነት ጥያቄ ምክንያት በርካቶች መስዋዕት የከፈሉበት የወልቃይት ጉዳይ ባለፊት ዓመታት በአማራ ክልል ለተቀጣጠለው ሕዝባዊ ትግል ዋና መነሻ መሆኑ ይታወቃል።
ጉዳዩ በወቅቱ ለነበረው የአቶ ኃይለማርያም አስተዳደር ጭምር ራስ ምታት በመሆኑ በጥያቄው ዙሪያ ብአዴን እና ህወሓት እንዲወስኑ የሚል መመሪያ ከማውረድ አልፎ ውሳኔ ማሳለፍ ሳይችል ቀርቷል።
ከዚያም በቀድሞው የትግራይ ክልል ርዕሰ መስተዳደር በአቶ ዓባይ ወልዱ ጫና ወልቃይት የትግራይ እንደሆነ መወሰኑ ቢገለጽም ጉዳዩ ሲብላላ ቆይቶ ወደ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ወደ ዶክተር አብይ ተላልፏል።
ዶክተር አብይ በመቀሌው እና በጎንደሩ ጉብኝታቸው ከገጠሟቸው ፈታኝ ጥያቄዎች መካከል አንዱ ይኸው የወልቃይ ጉዳይ መሆኑ ይታወሳል። መቋጫው ምን ይሆን? የሚለው፣ ዛሬም የብዙዎችን ቀልብ ሰቅዞ እንደያዘ ነው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በደቡብ ክልል የተፈጠረ አለመረጋጋትን ተከትሎ በክልሎች መካከል ግልጽ ወሰን እንደሌለ በማውሳት እና አሁን ያለው አከላለል አገሪቱን ‘’ጠቅሟታል?’’ ወይስ ‘’ጎድቷታል?’’ የሚለውን ጉዳይ የሚያጠና ኮሚቴ ተቋቁሞ አወቃቀሩ ጉዳት ካለው እንደሚከለስ በመግለጽ ሕዝቡ አገራዊ አንድነቱ ላይ ትኩረት እንዲያደርግ ቢያሣስቡም፣ ቀደም ባለው ጊዜ በክልሎች መካከል የተፈጠሩ ግጭቶች እልባት ሊያገኙ አልቻሉም።
ይልቁንም የነጻነት ጸሀይ ብልጭ ማለቷን ተከትሎ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ አገራዊ ጥሪና መልዕክት በተጓዳኝ ዜጎችን በማፈናቀል፣ ድንበር በማስመርና ካርታ በመንደፍ በብሔሮችና በክልሎች መካከል የሚደረጉ ፉክክሮችና ሽኩቻዎች እዚህም፣ እዚያም እየተስተዋሉ ነው።

No comments:

Post a Comment

wanted officials