Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Monday, December 1, 2014

አስተዳደሩ የትብብሩን የ24 ሰዓት ሰላማዊ ሰልፍ እውቅና አልሰጠሁም አለ





•ትብብሩ አስተዳደሩ እውቅና ሰጭም ነፋጊም አለመሆኑን በመግለጽ ድጋሜ ደብዳቤ ጽፏል

የ9ኙ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ትብብር ህዳር 27 እና 28/2007 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ሊያደርገው ላቀደው የአዳር ሰላማዊ ሰልፍ አስፈላጊው ትብብር እንዲደረግለት፣ ህዳር 17 ቀን 2007 ዓ.ም በፃፈው ደብዳቤ መጠየቁ የሚታወስ ቢሆንም አስተዳደሩ በቁጥር አ.አ/ከፅ/10/30.4/55 ህዳር 19 ቀን 2007 ዓ.ም በፃፈው የመልስ ደብዳቤ ለሰላማዊ ሰልፉ እውቅና አለመስጠቱን አስታውቋል፡፡

ትብብሩ ለሰልፉ የመረጠው ቦታ መስቀል አደባባይ ሲሆን፣ አስተዳደሩ በበኩሉ የ24 ሰዓቱን ሰልፍ ላለማወቁ ምክንያት ነው ያለውን ሲያስቀምጥ፣ ‹‹የተጠየቀው ቦታ በልማት ምክንያት የትራፊክ መጨናነቅና ትላልቅ የመንግስት ተቋማት እና የዓለም አቀፍ ድርጅቶች ያሉበት ስለሆን ጥያቄውን ተቀብለን ለማስተናገድ የምንቸገር መሆኑን እየገለጽን፣ የአደባባይ ስብሰባውም ሆነ ሰላማዊ ሰልፉ እውቅና ያልተሰጠው መሆኑን እናስታውቃለን›› በማለት አስፍሯል፡፡

የትብብሩን ሰልፍ እያስተባበሩ ያሉት ፓርቲዎች አመራሮች ዛሬ ለአስተዳደሩ በጻፉት ደብዳቤ እንደጠቀሱት ደግሞ፣ የሰላማዊ ሰልፍና ሕዝባዊ የፖለቲካ ስብሰባ ሥርዓት አዋጅ ቁጥር 3/1983 አንቀፅ 6 ንዑስ አንቀፅ 2 “የከተማው ወይም የአውራጃው አስተዳደር ጽ/ቤት በዚህ አዋጅ አንቀፅ 6 ንዑስ አንቀፅ 1 የተመለከቱትን ሁኔታዎች በማገናዘብ ሰላማዊ ሰልፍ ወይም ሕዝባዊ የፖለቲካ ስብሰባው በሌላ ጊዜ ወይም በሌላ ሥፍራ ቢደረግ ይሻላል የሚል አስተያየት ካለው ምክንያቱን በመግለፅ ይህንኑ ጥያቄው በደረሰው በ12 ሰዓት ውስጥ በጽሁፍ ለአዘጋጁ የማሳወቅ ኃላፊነት አለበት፡፡ ሆኖም የከተማው ወይም የአውራጃው አስተዳደር ጽ/ቤት ሰላማዊ ሰልፍ ወይም ሕዝባዊ የፖለቲካ ስብሰባው ምን ጊዜም ወይም በየትኛውም ቦታ ሊካሄድ አይችልም ማለት አይችልም” በማለት አስተዳደሩ እውቅና የመንፈግ ስልጣን እንደሌለው ገልጸዋል፡፡

በመሆኑም፡-
‹‹1ኛ. እውቅና እንዲሰጥ የተጠየቀ ማንኛውም አካል ከላይ የተደነገገውን በማገናዘብ ለሌላ ጊዜና በሌላ ቦታ እንዲደረግ ሃሳብ ከማቅረብ ውጭ ሰላማዊ ሰልፉ ምን ጊዜም ወይም በየትኛውም ቦታ ሊካሄድ አይችልም ለማለት ለመስሪያ ቤታችሁ ስልጣን ያልተሰጠ በመሆኑ፤
2ኛ. ሰላማዊ ሰልፉና ሕዝባዊ የፖለቲካ ስብሰባ የሚከናወኑት በመሰረታዊነት ለትላልቅ የመንግስትና ዓለም ዓቀፍ ተቋማት ለማሳወቅ በመሆኑ በእነዚህ አካባቢ ሰልፍና ሕዝባዊ ስብሰባ ማድረግ በአዋጁ ያልተከለከለ በመሆኑ፤

ለጥያቄያችን የተሰጠን መልስ ከምክንያታዊነትና ህጋዊነት ውጭ ሰልፉ እንዳይካሄድ ለመከልከል ስለሆነ እንዲህ ዓይነቱን ኢ-ህጋዊ የሆነ ውሳኔና አሰራር ፈፅሞ የማንቀበል በመሆኑ አስቀድመን ባሳወቅነው መሰረት ሰላማዊ ሰልፉን በተጠቀሰው ቀን፣ ሰዓትና ቦታ የምናካሂድ መሆኑን እያሳወቅን በጽ/ቤታችሁ በኩል አስፈላጊው ትብብር እንዲደረግልን በድጋሚ እናስታውቃለን›› ብሏል ትብብሩ ዛሬ ለአስተዳደሩ በጻፈው ደብዳቤ፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials