Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Wednesday, December 31, 2014

የኢንተርኔት እና የተንቀሳቃሽ ስልክ መረጃዎች ላይ ጠበቅ ያለ ቁጥጥር የሚያደርግ አዋጅ ተረቀቀ

ኢሳት ዜና :-በሥራ ላይ ያለውን የብሮድካስት አዋጅ የሚሽርና ለመጀመሪያ ጊዜ በኢንተርኔት ድረገጾች እንዲሁም ተንቀሳቃሽ ስልክንበመጠቀም የሚቀርብ የብሮድካስት አገልግሎቶችን ላይ ጥብቅ ቁጥጥር የሚያደርግ የሚዲያ ረቂቅ አዋጅ ተዘጋጅቷል፡፡
የኢትዮጵያ የብሮድካስት ባለስልጣን ያዘጋጀውና በዚህ ዓመት ለፓርላማው ቀርቦ ይጸድቃል ተብሎ የሚጠበቀው ይህው የሚዲያ ረቂቅ አዋጅ አሌክትሮኒክስ መገናኛ ብዙሃን ማለትም ራዲዮ፣ቴሌቪዥን፣ የኢንተርኔት ድረገጾች እንዲሁም የሕትመት ሚዲያውን የሚመለከት ነው፡፡ በዚህ አዋጅ ለመጀመሪያ ጊዜ የአንተርኔት ድረገጾች ፈቃድ ማውጣት የግድ መሆኑን ደንግጎአል፡፡
በኢንተርኔት ፣በተንቀሳቃሽ ስልክ ወይም በመሰል የመረጃ መረብ አማካኝነት ለስርጭት የሚቀርብ ማንኛውም ፕሮግራም በአገር አንድነትና ሉአላዊነት ላይ አደጋ የሚጥል ፣በአገር ደህንነት፣ ክብርና ጥቅም ላይ ጉዳት የሚያደርስ ፣የአገር ሚስጢርን የሚገልጽ ፣ አመጽና ጦርነትን የሚቀሰቅስ፣ የሰው ልጆችን ስብዕና ፣ነጻነት ወይንም ስነምግባር የሚጻረር ፣የሌሎችን እምነት የሚያንኳስስ መሆን እንደሌለበት ደንግጎአል፡፡
በተጨማሪም ሥራዎቹ ማንኛውንም የህብረሰተብ ክፍል፣ ብሔር፣ጎሳ፣ቀለም፣ጾታ፣ዘር፣ቋንቋ፣ሃይማኖት፣ማህበራዊ አመጣጥ፣ ወይንም ሌላ መሰል አቋምንና ክብርን የሚነካ ወይም የሚያዋርድ፣ በህዝቦችና በሃይማኖቶች መካከል የእርስ በእርስ ግጭት የሚቀሰቅስ ወይንም ጥላቻ የሚያስፋፋ፣ የግለሰብን ስም የሚያጠፋ፣፣ለአካለ መጠን ያልደረሱ ልጆችን አመለካከት ስሜት የሚጎዳና ወደአልተፈለገ አቅጣጫ እንዲያዘነብሉ የሚገፋፋ፣ የህብረሰተቡን ሞራል የሚጥስ ወይንም በሕግ የተከለከለ ማንኛውንም ድርጊት የሚፈጽም መሆን የለበትም ይላል፡፡
ተጠያቂነትም በተመለከተ ረቂቅ አዋጁ እንዳሰፈረው በኢንተርኔት ፣በተንቀሳቃሽ ስልክ ወይም በመሰል መረጃ መረብ አማካይነት የቀረበ ፕሮግራም ለሚያስከትለው ማንኛውም የወንጀል ድርጊት ወይም የፍትሐብሄር ጉዳት የፕሮግራሙ ሃላፊና የብሮድካስት አገልግሎት ሰጪው በአንድነት ተጠያቂ ይሆናሉ ይላል፡፡
በኢንተርኔት ፣በተንቀሳቃሽ ስልክ ወይም በመሰል መረጃ መረብ አማካይነት የቀረበ ፕሮግራምን ቁጥጥርን በተመለከተ ከህብረተሰቡ በቅሬታ መልክ የሚቀርቡ አቤቱታዎችን የመመርመር፣ተቆጣጣሪ የመመደብ ስልጣን ወደፊት ለሚቋቋመው ባለስልጣን መ/ቤት ሃላፊነቱን ይሰጣል፡፡
ረቂቅ አዋጁ የቴሌቪዥንን ከአናሎግ ወደዲጂታል ሽግግርን ለማቀላጠፍና የግል ቴሌቪዥን ለመፍቀድ ይረዳል ተብሎአል፡፡ በዚህ ረቂቅ አዋጅ መሰረት ተጠሪነቱ ለጠ/ሚኒስትሩ የሆነ የኢትዮጵያ የሚዲያ ባለስልጣን የሚባል መ/ቤት ይቋቋማል፡፡
የብሮድካስት አግልግሎት የሚመራበትን ሥርዓት ለመደንገግ ከ15 ዓመታት በፊት የወጣው አዋጅ ቁጥር 178/1991 የግል ቴሌቬዥን ጣቢያ ፈቃድ ለግል ባለሃብቶች የፈቀደ ቢሆንም ይህ ተግባራዊ ሳይሆን አዋጁ በቁጥር 533/1999 የተሻሻለ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በተሸሻለውም አዋጅ ቢሆን የግል ቴሌቭዥን ጣቢያ የተፈቀደ ቢሆንም ኢህአዴግ መራሹ መንግስት ኢትዮጵያ ለዚህ ደረጃ ገና አልበቃችም በማለት አዋጁ እንዳይፈጸም እስካሁን ድረስ መከልከሉ የሚታወቅ ነው፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials