የአሸባሪ ሚስት ድሮም አሸባሪ ናት ሂጃብ አውልቂ ከተባለች ለምን አታወልቅም አይደለም ሂጃብ ይቅርና ካስፈለገን ቀሚሳቸውን አሶልቀን እናያቸዋለን (አቶ አምባዬ የማረሚያ ቤቱ ሃላፊ)
አቡ ዳውድ ኡስማን
በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ታስረው የሚገኙት ኮሚቴዎቻችን እና ኡስታዞቻችን የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በዚህ ሳምንት የጀመረውን ሙስሊም ሴቶችን ሂጃባችሁን አውልቃችሁ ሳንፈትሻቹ አትገቡም የሚለውን ክልከላ አስመልክቶ ለማረሚያ ቤቱ አስተዳደር ሃላፊ ላቀረቡት አቤቱታ በማረሚያ ቤቱ ሃላፊ በአቶ አምባዬ ከፍተኛ ስድብ እና ዛቻ ተፈፅሞባቸው ከቢሮ በፖሊስ ተገፍትረው እንዲወጡ መደረጋቸውን ምንጮች አስታወቁ፡፡
የኮሚቴዎቻችን እና ወንድሞቻችን ባለቤቶች እና ሴት ቤተሰቦች ሂጃባችሁን አውልቃችሁ ሳንፈትሻችሁ አትገቡም በሚል ማረሚያ ቤቱ በዚህ ሳምንት ተግባራዊ ማድረግ በጀመረው ጸረ ህገ መንግስታዊ የሆነ የመብት ክልከላ ላይ ለማረሚያ ቤቱ አስተዳደር ጥያቄያቸውን ለማቅረብ ወደ ሃላፊው ቢሮ ያመሩት ኡስታዝ አህመዲን ጀበል፣፣ኡስታዝ ያሲን ኑሩ፣ ኡስታዝ ሰኢድ አሊ እና ኡስታዝ ባህሩ ኡመር በማረሚያ ቤቱ ሃላፊ መሰደባቸው እና ተገፍትረው ከቢሮ በፖሊስ ሃይል እንዲወጡ መደረጋቸው ታውቋል፡፡
ኡስታዝ አህመዲን ጀበል፣፣ኡስታዝ ያሲን ኑሩ፣ ኡስታዝ ሰኢድ አሊ እና ኡስታዝ ባህሩ ኡመር ወደ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ሃላፊው አቶ አምባዬ ቢሮ ያመሩ ሲሆን ሃላፊውም በስርአቱ ተቀብሎ ማናገር ከጀመረ ቡሃላ የመጡበትን ጉዳይ በማስረዳት በማረሚያ ቤቱ ፖሊሶች በሙስሊም ሴቶች ላይ እየተፈፀመ ያለውን ህገ ወጥ ክልከላ አስመልክቶ ጥያቄያቸውን እና ስሞታቸውን ማሰማት ሲጀምሩ ሃላፊው አቶ አንባዬ በመበሳጨት እጅግ አሳፋሪ ንግግር እና ስድቦችን አዝንቦባቸዋል፡፡
አቶ አንባዬ በንግግሩ እንዳለው የአሸባሪ ሚስት ድሮም አሸባሪ ናት አውልቂ ከተባለች ለምን አታወልቅም አሸባሪ ስለሆነች ነው እንጂ ይሄ ከገረማቹ ገና አስወልቀን ቪዲዬ እንቀርፃቸዋለን። እሱም ከገረማቹ ስታወሩ በካሜራ እየቀረፅን የምታወሩትን እናዳምጣለን። ይሄም ደግሞ የሚገርማችሁ ከሆነ ገና ቀሚሳቸውን አስወልቀን እናያቸዋለን በማለት አስነዋሪ እና አሳፋሪ ንግግሮችን እና ስድቦችን እንደተናገራቸው ታውቋል፡፡
ህግ እና ስርአት ጠብቀው በቢሮ በመገኘት ላቀረቡት ህጋዊ ጥያቄ ድንበር በማለፍ በከፍተኛ ቁጣ ሃላፊው አቶ አንባዬ ስድብ እና የዛቻ መአት ሲያወርድባቸው ኡስታዝ ባህሩ ኡመር የሃላፊውን ስድብ በማስቆም ለጠየቅነው ጥያቄ መልስ እንጂ ዛቻ አያስፈልግም፡፡ የመጣነው ስርአት ባለው መልኩ ምላሽ ለማግኘት እንጂ ልንሰደብ እና ሊዛትብን አይደለም በማለት ምላሹን ሰጥቷል፡፡
ኡስታዝ አህመዲን ጀበል እና ኡስታዝ ሰኢድ አሊ ሃላፊው ለተናገረው ስርአት አልባ ንግግር የጠየቁት ተገቢ ጥያቄ መሆኑን በማስታወስ በዚህ ሁኔታ ሊያናግራቸው እንደማይገባ በማሳሰባቸው የማረሚያ ቤቱ ፖሊሶች ወደ ቢሮ እንዲገቡ ተደርጎ ኡስታዝ አህመዲን ጀበልን በመገፍተር እና በማመናጨቅ ሁላቸውንም ከቢሮ እንዲወጡ መደረጋቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
ኮሚቴዎቻችን እና ኡስታዞቻችን ከማዕከላዊ ከወጡ ቡሃላ በማረሚያ ቤቶች የማመናጨቅ እና የማንገላታት ቢኖርም የዚህ መሰሉ ከፍ ያለ ስድብ፣ማመናጨቅ ፣ ዛቻ እና ግፍተራ ለመጀመሪያ ጊዜ የሙሰሊም እህቶች ሂጃብ ለምን አውልቁ ይባላል በሚል ጥያቄ በማቅረባቸው በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ሃለፊዎች እና ፖሊሶች እንደተፈፀመባቸው ተዘግቧል፡፡
በማረሚያ ቤቱ ሃላፊዎች እጅግ አሳፋሪ የሆነ የህግ ጥሰት እየተፈፀመ ሲሆን ከአንድ ሃላፊ የማይጠበቅ አስነዋሪ ንግግሮች እና ስድቦችን በመናገር የኮሚቴዎቻችንን እና የወንድሞቻችንን ሞራል ለመስበር ጥረት እየተደረገ ይገኛል፡፡
በተያያዘም የኮሚቴው አባል የሆኑት ሼህ መከተ ሞሄም በዞን 3 ውስጥ ክፍል እንዲቀየርላቸው ላቀረቡት አቤቱታ ምላሸ እንዲሆን ቤተሰብ እንዳይጠይቃቸው እና የላይብረሪ አግልግሎትም እንዳይጠቀሙ ማዕቀብ እንደተጣለባቸው ታውቋል፡፡
posted by Aseged Tamene