ኢሳት ዜና :-ወኪላችን እንዳለው በዋና ከተማዋ ጁባ አንድ ወንድና አንድ ሴት ሲገደሉ ሁለት ሴቶች ግን በጠና ቆስለው ወደ ኢትዮጵያ ተወስደዋል። የሁለቱም ሟቾች አስከሬንም በኢትዮጵያውያን እርዳታ ወደ ኢትዮጵያ መሄዱ ታውቆል:: ሰዎቹ በምን ሁኔታ እንደተገደሉና እንደቆሰሉ
እንዲሁም ጥቃቱን ያደረሱትን ወገኖች ዝርዝር ለማወቅ አልተቻለም። በደቡብ ሱዳን የሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ በኢትዮጵያውያን የሚደረገውን ግፍና እንግልት ከመከታተል ይልቅ በዶላር ጥቁር ገበያ ምንዛሪ መሰማራቱን የገለጸው ወኪላችን ፣ የቀድሞ የህወሃት ባለስልጣናት በጁባ ከተማ የሚያራምዱትን የቢዝነስ ተቋምና በጋምቤላ በኩል የሚያመጡትን የጤፍና የተለያየ ሸቀጣሽቀጥ ንግድ ጉዳይ ቅድሚያ በመስጠት አብዛኛው ኢትዮጵያውያን የሚያቀርቡትን አቤቱታ እንደማይሰማ ተናግሯል። ለህወሃት አባሎች ህጋዊ የመኖረያ ፈቃድና የንግድ ፈቃድ ለማስወጣት የጁባ ባለስልጣናትን ደጅ የሚጠናው ኢምባሲው ምርቶችን ወደ ደደቡብ ሱዳን በማስገባት በኩል ወኪል ሆኖ እየሰራ መሆኑን ጠቅሷል።