Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, October 15, 2015

የአውሮፓ ሕብረት አባሎች ወደ 160 ሽህ ስደተኞችን በአባል ሀገሮች ለማስፈር ተስማሙ


የአውሮፓ ሕብረት አባሎች ወደ 160 ሽህ ስደተኞችን በአባል ሀገሮች ለማስፈር ተስማሙ



የአውሮፓ ሕብረት 28 አባሎች ወደ 160 ሽህ የሚጠጉ ስደተኞችን ወደ ሌሎች አባል ሀገሮች ለማስፈር ተስማሙ። በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት ከግሪክና ጣሊያን የስደተኞችና የፍልሰተኞች ማቆያ ስፍራዎች፤ ወደ ሌሎች የአውሮፓ ሀገሮች የሚሰፍሩት፤ ጉዳያቸው ተቀባይነት ያገኘ የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂዎችና ስደተኞች ይሆናሉ።

ሜዲትራንያን ባህር ዳርቻ የሚገኙ የአውሮፓ ሀገሮች፤ በተለይ ጣሊያንና ግሪክ፤ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ በርካታ ሰዎች የሚፈናቀሉበትና የሚፈልሱበት ዓለም አቀፍ ቀውስ ቀዳሚ ተቀባይ ሀገሮች ሆነዋል።

ከነዚህ የባህር ዳርቻ ሀገሮች የፍልሰተኞችና ስደተኞች ወደ ሌሎች ሐገሮች እንዲሰፍሩ፤ የአውሮፓ ህብረት አባላ ሀገሮችም ጉዳዩን በጋራ ሃላፊነት እንዲወጡት ተግባራዊ ጥረት ተጀምሯል። የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ድርጅት (UNHCR) የደቡብ አውሮፓ ቃል አቀባይ ካርላታ ሳሚ (Carlotta Sami) ስደተኞችና ፍልሰተኞችን የማስፉር እቅድ በቅርብ ወራት ስምምነት ያገኘ እንደሆነ ገልጸዋል።

“በርካታ አባል ሀገሮች የተወሰኑ ስደተኞችን ተቀብለው ለማስፈር ተስማምተዋል። ሰፈራው የሜዲትራንያን ባህርን አቋርጠው ወደ ጣሊያንና ግሪክ የሚገቡትን ስደተኞች ይመለከታል” ካርላታ ሳሚ ብለዋል።
የተወሰነው160 ሽህ ስደተኞችን ለማስፈር ነው። ሆኖም ቁጥሩ አባይን በጭልፋ አይነት፤ ችግሩን የማይቀርፍ ነው።
የደቡብ አውሮፓ ቃል አቀባይ ካርላታ ሳሚ

ግሪካና ጣሊያን እንዲሁም ሌሎች የስደተኞችና ፍልሰተኞች ቀዳሚ መዳረሻ የአውሮፓ ሀገሮች፤ የህብረቱ አባላት እንዲያግዟቸው ጥሪ ሲያሳልፉ ቆይተዋል። ሆኖም የተቀናጀ የስደተኞችና ፍልሰተኞች አቀባበል ስልት እንዲሁም ስምምነት ስላልነበረ፤ አፈጻጸሙ ተጓቶ ሰንብቷል።

ባለፈው ሚያዝያ ወር የአውሮፓ ህብረት ሀገሮች አስቸኳይ ጉባዔ ጠርተው የስደትና ፍልሰትን ጉዳይ በ28ቱ አባል ሀገሮች መሪዎች ውይይት ተደርጎበት ባለ 10 ነጥብ የስምምነት ሰንድ ቀርቦ ነበር።

ከነዚህም መካከል አንዱ በባህር ላይ ፈልጎ የማዳን አቅምን ማጠናከር ሲሆን፣ ትሪተን (Triton) እና ፖሲዶን (Poseidon) ለሚባሉት በሜዲትራንያን ባህር ሰዎችን ፈልጎ የማዳን መርሃ ግብሮች፤ ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት በጀታቸው በእጥፍ እንዲያድግ ተወስኗል።

ሌላኛው ጉዳይ የህገወጥ የሰው አዘዋዋሪዎችን ንብረቶች፤ በተለይ ጀልባዎችን በመቀማት፤ ከጥቅም ውጭ እንዲሁኑ ማድረግ የሚል ነው። የብርታንያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካምሮን፤ በጉባዔው በር ላይ ባደረጉት ንግግር የዛሬው ስብሰባ አትኩሮት ህይወት ማዳን ሊሆን ይገባዋል ካሉ በኋላ ያደረጉት ንግግር ቀጥተኛ ነበር።
ህይወት ማዳን ማለት እነዚህን ችግረኞች መታደግ ነው። ከዚያም በተጨማሪ ወሮበላ አዘዋዋሪዎችን መደቆስና የአካባቢው ሃገሮች እንዲረጋጉ ማድረግ ነው።
የብርታንያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካምሮን

ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካምሮን በወቅቱ ኤች ኤም ኤስ ቡልዋርክ (HMS Bulwark) የተባለች የብርታንያ የጦር መርከብን በሜዲትራንያን ባህር እንደሚያሰማሩ ተናግረው ነበር። ሁለት ሄሊኮፐሮች፡ 67 መኪኖች፣ ሶስት አውቶማቲክ ማሳሪያዎችና ከ400 በላይ ወታደሮች የመጫን አቅም አላት ኤች ኤም ኤስ ቡልዋርክ (HMS Bulwark)።

አርብለት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት በብርታንያ የቀረበውን ረቂቅ ውሳኔ አጽድቋል። በዚህም መሰረት የአውሮፓ የባህር ሀይል የህገወጥ አዘዋዋሪ ጀልባዎችና መርከቦች ላይ ወታደራዊ እርምጃ እንዲወስዱ ስልጣን ሰጥቷል። መርከቦችን በዓለም አቀፍ የውሃ ክሎች መያዝ፣ መፈተሽና አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ማስወገድን ያካትታል።

ሆኖም በሊቢያ የባህር ክልል እንዲሁም የባህር ዳርቻዎች የሚገኙ ጀልባዎችን ለማውደም በብርታንያና በአውሮፓ ህብረት የቀረበውን ሃሳብ፤ የመንግስታቱ ድርጅት አላጸደቀውም።

የአውሮፓ ህብረት በዓለም አቀፍ የባህር ክልሎች የሚንቀሳቀሱ ህገወጥ አዘዋዋሪ ጀልባዎችን የሚቆጣጠር የባህር ሃይል አሰማርቷል። የአውሮፓ ህብረት ባለፈው ሮብ “ዘመቻ ሶፍያ” የተባለ ሶስት የአፈጻጸም እቅድ ያለው ወታደራዊ ትብብር ለማድረግ ከሊብያ ጋር ተስማምቷል። አላማውም ህይወትን ማዳን፣ ህገወጥ የሰዎች ዝውውርንና የወሮበሎችን ስራ ማስቆም ነው።

ከተሰነይ ኤርትራ ተሰዶ ወደ አውሮፓ የገባ መሆኑን የገለጸው የ20 ዓመት ወጣት በጣሊያን ለአሜሪካ ድምጽ ሬድዮ ዘጋቢዎች የተሰደደበትን ምክንያት ሲያስረዳ “የኤርትራ መንግስት በአሁኑ ወቅት ወጣቶችን በመጨቆን በውትድርና ስለሚያሰልፍ” ከሀገሩ ለመውጣት መወሰኑን ገልጿል።

ባለፈው 10 ወራት ብቻ፤ 3,092 ሰዎች ለህይወት አደገኛ በሆነው የጀልባ ጉዞ በሜዲትራንያን ባህር ላይ ሰምጠው ሞተዋል። ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ደግሞ ወደ አውሮፓ ለመሻገር በቅተዋል። የሚበዙት በግሪክና ጣሊያን ሰፍረው እንደሚገኙ የዓለም አቀፍ የፍልሰተኞች ድርጅት (IOM) ገልጿል። የአውሮፓ ህብረት የሰዎች ፈልጎ ማዳን መርሃ ግብርም ከ100ሽህ በላይ ሰዎችን ህይወት እንዳተረፈ ተመዝግቧል።

ባለፈው አርብ የጸጥታው ጥበቃ ምክር ቤት በስደተኞችና ፍልሰተኞች ጉዳይ ላይ ያሳለፈው ውሳኔ ላይ ቬኔዙዌላ ተአቅቦ ስታድርግ ሌሎቹ 14 አባላት በሙሉ ድምጽ አጽድቀውታል።

ሳሌም ሰለሞንና ሄኖክ ሰማእግዜር አቀናብረው ያዘጋጁትን ሙሉ ዝርዝር የተያያዘውን የድምጽ ፋይል በመጫን ያዳምጡ።
የአውሮፓ ሕብረት አባሎች ወደ 160 ሽህ ስደተኞችን በአባል ሀገሮች ለማስፈር ተስማሙ/ርዝመት – 6ደ54ሰ/

- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/47364#sthash.vIJosbiQ.dpuf

No comments:

Post a Comment

wanted officials