Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Tuesday, October 13, 2015

ረሃቡ ከገዥው ፓርቲ የፖሊሲ ውድቀት የመነጨ መሆኑን ሰማያዊ ፓርቲ ገለፀ

ረሃቡ ከገዥው ፓርቲ የፖሊሲ ውድቀት የመነጨ መሆኑን ሰማያዊ ፓርቲ ገለፀ
• ‹‹ለችግሮቻችን ምንጭ የሆነውን ስርዓት በቁጥርጠኝነት መታገል አለብን››
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
ሰማያዊ ፓርቲ ዛሬ መስከረም 27/2008 ዓ.ም በፅ/ቤቱ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ረሃቡ ከገዥው ፓርቲ የፖሊሲ ውድቀት የመነጨ ነው ብሏል፡፡ ፓርቲው ‹‹ረሃቡ የገዥው ፓርቲ የፖሊሲ ውድቀት ነው!›› በሚል በሰጠው መግለጫ ‹‹ገዥው ፓርቲ ችግር ቢከሰት እንኳ በአደጋ ጊዜ ለዜጎች የሚበቃ እርዳታ አቀርባለሁ ሲል የነበረ ቢሆንም ለወገኖቻችን ግን የሚደርስላቸው አልተገኘም፡፡›› ሲል ወቅሷል፡፡ ‹‹ለዜጎች ዓለም አቀፍ ተቋማት እንዳይደርሱላቸው የተፈጠረው ረሃብ የራሱ የፖሊሲ ውድቀት መሆኑን የሚያውቀው ስርዓቱ የዜጎቻችን ስቃይና መከራ ሲሸፋፍን እንደቆየና ከአቅሙ በላይ ሲሆን ችግሩ እንደተከሰተ ቢገልፅም ለዜጎች ተገቢውን እርዳታ በሚያስገኝ መልኩ እርምጃ እየወሰደ አይደለም›› ብሏል መግለጫው፡፡ ለተከሰተው የረሃብ አደጋ ተገቢው ትኩረት መነፈጉም ገዥው ፓርቲ እመራዋለሁ ለሚለው ህዝብ ደንታ ቢስነቱን የሚያረጋግጥ እንደሆነ አስታውቋል፡፡
ፓርቲው በመግለጫው ‹‹ረሃቡ፣ ርዛቱ፣ ድህነቱ፣ ስደቱ፣ ስራ አጥነቱ፣ የኑሮ ውድነቱ ከመቼውም ጊዜ በላይ ዜጎችን በብርቱ እየተፈታተኑ በሚገኝበት ወቅት ገዥው ፓርቲና በስሩ ያሉ ድርጅቶች ተመሰረትንበት የሚሉትን ጊዜ ለወራት በቅንጦት በማክበር በብዙ ሚሊዮን ገንዘብ ከኢትዮጵያውያን ጉሮሮ ነጥቆ ድግስ ሲደግስና አሸሸ ገዳሜ ሲል በርካታ ኢትዮጵያውያንን አሳዝኗል፡፡›› ብሏል፡፡ ለተከሰተው ረሃብ ኢህአዴግ ለይስሙላ ቆሜለታለሁ የሚለውን አርሶ አደርና አርብቶ አደርን ህይወት ለማሻሻል የረባ ስራ እንዳልሰራ አረጋግጧል ያለው መግለጫው ግብርናው ኢኮኖሚውን ይመራል ቢልም እስካሁን ግን በየአመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን የረሃብ ሰለባ እንደሆነ መቀጠሉን ገልፆአል፡፡ መሬት የመንግስት ነው በሚል ሽፋን አርሶ አደሩን ከቀየው እያፈናቀለ ለስርዓቱና ደጋፊዎችና ለባዕዳን መሬትን እየሸጠ አርሶ አደሩን ለረሃብ ተጋላጭ አድርጎታል ሲልም ለርሃቡ ምክንያት የኢህአዴግን የፖሊሱ ውድቀት እንደሆነ ገልፆአል፡፡
ገዥው ፓርቲ አፋጣኝ እርምጃ እንዲወስድ የጠየቀው ሰማያዊ ፓርቲ ስለ ችግሩ ለኢትዮጵያውያንና ለዓለም አቀፍ ማህበረሰብ የሚያስረዳ ገለልተኛ አካል ተቋቁሞ በረሃብ ለተጠቁት ዜጎች መፍትሄ እንዲፈለግም ጠይቋል፡፡ ስርዓቱ ደካማና ኃላፊነት የጎደለው እንደሆነ የገለፀው ሰማያዊ ፓርቲ በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ኢትዮጵያውያንና የዓለም ማህረሰብ ማህበረሰቡ ከተጎጅዎቹ ጎን እንዲቆሙ ጠይቋል፡፡ ‹‹የኢትዮጵያውያን መከራ የመነጨው ከገዥው ፓርቲ የተሳሳተ ፖሊሲ፣ የአፈፃፀም ብቃት ችግርና ለኢትዮጵያውያንም ባለው ግድ የለሽነት በመሆኑ ለችግሮቻችን ምንጭ የሆነ ስርዓት በቁጥርጠኝነት መታገል አለብን›› ሲልም ለህዝብ ጥሪ አቅርቧል፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials