Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Saturday, June 14, 2014

ውሕደታችንን በማጠናከር የቅንጅትን ሕዝባዊ መንፈስ ዳግም እንመልሳለን!!! – ከአንድነት ፓርቲ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

አንድነት ለዴሞክራና ለፍትህ ፓርቲ የሀገራችን ውስብስብ ችግር በዘላቂነት እንዲፈታና ህዝቡ ለዘመናት ዋጋ ሲከፍልበት የኖረው ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እውን እንዲሆን የፖለቲካ ፓርቲዎች ያላቸው ድርሻ ከፍተኛ እንደሆነ ይረዳል. የተቃውሞ ጎራው አንድ ጠንካራ ሃይል ለመፍጠር ከሚያስችለው ከግል ድርጅታዊ ጥንካሬና ስራ በተጨማሪ ልዩነትን አቻችሎና አጣጥሞ መሰባሰብ እንደሚገባም እንገነዘባለን. የህዝባችን ፍላጎትም የተበታተነ ተቃዋሚ ፓርቲ ሳይሆን የተጠናከረና የተሰባሰበ አንድ ፓርቲ ማየት እንደሆነ በተደጋጋሚ ሲገለፅ ቆይቷል.
አንድነት ይህንን እውነት በመገንዘብ በሀቀኛ ተቃዋሚዎች መካከል ውህደት እንዲፈፀም በስትራቴጅ ሰነዳችንም በማስቀመጥ ስንሰራ ቆይተናል. የፖለቲካ ፓርቲዎች መሰባሰብም የፓርቲያችን መሰረታዊ መርህና እምነት ነው. እንደ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ሁሉ በሰላማዊ ትግሉ ከፍተኛ ዋጋ ከከፈለውና እየከፈለ ካለው አንድነት ጋር በሁለቱ ፓርቲዎች መልካም ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የድርድር ውይይት ሲያደርግ መቆየቱም ይታወሳል.
አንድነትና መኢአድ ከጥልቅ ውይይት በኋላ ወቅታዊው የፖለቲካ ሁኔታ የሚፈልገውን በመገንዘብ; የህዝቡን ጥያቄ መመለስ የሚችል የበተባበረ የፖለቲካ ሃይል ለመፍጠርና የቅንጅትን ህዝባዊ መንፈስ ለመመለስ የሚያስችላቸው ደረጃ ላይ በመድረሳቸው ፓርቲያችን የተሰማውን ደስታ ለመግለፅ ይወዳል.
ሁለቱ ፓርቲዎች ስለ ዴሞክራሲ ሲሉ መስዋዕት የሆኑ ውድ ኢትዮጵያውያን በሚዘከሩበት ሰኔ 1 ቀን ለበርካታ ወራት በጋራ ሲሰሩበት የነበረውን የውህደት ስምምነት ከጫፍ በማድረስ የቅድመ ውህደት ስምምነት ፊርማቸውን አኑረዋል. ይህም የኢትዮጵያን ህዝብ ያስደሰተ እንደሆነ ካገኘነው የህዝብ አስተያየት ለመረዳት ችለናል. በእለቱም ውህደቱን ያልወደዱና የቅንጅት መንፈስ ዳግም እንደሚመለስ የገባቸው የስርዓቱ ምንደኞች የመጨረሻ የጣር ድምፃቸውን አሰምተዋል. የማደናቀፍ ሙከራው ግን አቅም አልባ ስለነበር የህዝቡን ጥያቄ ሊቀለብስ አልቻለም. ፓርቲያችን በከፍተኛ ውጣ ውረድ ቅድመ ውህደቱን ከጫፍ ለማድረስ የተጉ ሁለቱ ፓርቲዎች ከፍተኛ አመራሮች; የሀገር ሽማግሌዎች; አባላትና የተባበሩ ጥሪ ሲያቀርብ ለነበረው ህዝብ ከፍተኛ ምስጋና ያቀርባል. ውህደቱን ለማደናቀፍ የተላኩ ግለሰቦች የፈፀሙት የአካል ጉዳት ሳይበግራቸው ውህደቱን ባሳኩ አባሎቻችንም ኩራት ይሰማናል. ሁከት ፈጣሪዎችን ግን በሕግ እንጠይቃለን.
ከመጣነው ይልቅ የሚቀረን ብዙ እንደሆነም እንገነዘባለን. ይህንንም ከጫፍ ለማድረስ ትግላችን ተጠናክሮ ይቀጥላል. የኢትዮጵያ ህዝብም ያልተሸራረፈ ዴሞክራሲ ባለቤት እንዲሆን ውህደታችንን በማጠናከር የቅንጅትን መንፈስ ዳግም እንመልሳለን. ሌሎች ፓርቲዎችም ኢህአዴግን አሸናፊ የሚያደርገው የተናጠል ሩጫ እንደማያዋጣ ተገንዝበው አብሮ ወደ መስራቱ እንዲመጡ ሀገራዊ ጥሪ እናቀርባለን.
UDJ-SEALድል ​​የህዝብ ነው!
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
ሰኔ 5 ቀን 2006 ዓ. ም
አዲስ አበባ

No comments:

Post a Comment

wanted officials