ዳዊት ሰለሞን
ኢትዮጵያዊያኑ በኬንያ ፖሊስ ቁጥጥር ስር የገቡት ወደ ደቡብ አፍሪካ እንደሚያሻግሯቸው ተስፋ በሰጧቸው ደላሎች አማካኝነት እንዲያርፉባት በተደረገች ክፍል ውስጥ ተደራርበው እንደተኙ ነው፡፡
አየሩ በታፈነ ክፍል ውስጥ ታጭቀው የተያዙት ወጣቶች የሚበዙት ከደቡብ ኢትዮጵያ ተነስተው ሞያሌን አቋርጠው ናይሮቢ የደረሱ ነበሩ፡፡ቤተሰቦቻቸው የነበረቻቸውን መሬትና ከብቶቻቸውን ሸጠው፤የገሚሶቹ ተበድረው ጥቂት የማይሰኙት ደግሞ በአዲስ አበባ ጭምር ለዓመታት በጫማ ጠራጊነት ተሰማርተው ያጠራቀሟትን ገንዘብ ለደላሎች በመክፈል ደቡብ አፍሪካን በዓይነ ህሊናቸው እየሳሉ ስጋቸውን ባሳረፉበት ቅጽበት ፖሊሶች ‹‹ወደ አገራችን በህገ ወጥ መንገድ በመግባታችሁ በቁጥጥር ስር ውላችኋል አሏቸው፡፡
በኤልዶሬት አካባቢ የተያዙት 80 ኢትዮጵያዊያን በኢሲኦሎ ፍርድ ቤት ቢቀርቡም በግዜው አስተርጓሚ ባለመገኘቱ ተጨማሪ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
ከዚህ በፊት በተለያዩ የኬንያ ክፍሎች የተያዙ ኢትዩጵያዊያን በፍርድ ቤቶች በህገ ወጥ መንገድ ወደ አገር ውስጥ በመግባት የሚል ክስ እየተመሰረተባቸው ከ500-800 ዶላር የሚደርስ የገንዘብ ወይም ከ6 ወር እስከ ሁለት ዓመት የሚደርስ ቅጣት ሲበየንባቸው መቆየቱ ይታወሳል፡፡የኢትዮጵያ መንግስት በቅርቡ ሁለት ሰው አዘዋዋሪዎችን በኢንተርፖል አማካኝነት እጃቸውን ይዤ ወደ አገር አስገብቻለሁ ቢልም የወጣቶቹ ፍልሰት አለመቆሙ የሚያሳየው አሁንም የአዘዋዋሪዎቹ መረብ አለመበጠሱን ነው፡፡