Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Wednesday, April 22, 2015

“በወገኖቼ ላይ የተፈፀመዉ ድርጊት አሳዝኖኛል አስቆጥቶኛልም” – ቴዲ አፍሮ


“በወገኖቼ ላይ የተፈፀመዉ ድርጊት አሳዝኖኛል አስቆጥቶኛልም” – ቴዲ አፍሮ



ከቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) የተላከ መልዕክት

ሰሞኑን በደቡብ አፍሪካ እንዲሁም በተለያዮ ሀገራት በሚገኙ ኢትዮጵያዉያን ወገኖቻችን ላይ እና የሌላ ሀገር ተወላጅነት ባላቸዉ ንፁሀን ዜጉች ላይ በተፈፀመዉ አሰቃቄ የግድያ ወንጀል አዝነን ሳናበቃ ፦ በሊቢያ በሚገኙ ኢትዮጵያዉያን ወገኖቻችን ላይ የተፈፀመዉን እጅግ አሳዛኝ ፤ አረመኔያዊ ተግባር ሳይና ስሰማ የተሰማኝን ሐዘን ለመግለፅ ቃላትም ሆነ ቋንቋ ያጥረኛል።

እንኳን የኔ በሚሉት የራስ ወገን ይቅርና ክቡር በሆነዉ የትኛዉም የሰዉ ልጅ ፍጡር ላይ እንዲህ አይነቱ ፍፁም ርሕራሔ የሌለዉ ኢሰብአዊ ተግባር ሲፈፀም ማየትም ሆነ መስማት የሚፈጥረዉን ጥልቅና መሪር የሀዘን ስሜት ለመረዳት ወገን ሆኖ መገኘት ብቻ ሳይሆን ሰዉ ሆኖ መፈጠር ይበቃል።

እንደ ሰዉ ሰዉ በመሆኔ ብቻ ሳይሆን በተለይ እንደ ኢትዮጵያዊነቴ በወገኖቼ ላይ የተፈፀመዉ ድርጊት አሳዝኖኛል አስቆጥቶኛልም።
ከመቼዉም ጊዜ በበለጠም እኛ ኢትዮጵያዊያን ማንኛዉም አይነት ልዮነት ሳይወስነን በግፍ ለተጠቁት ወጉኖቻችን በአንድነት ቆመን ወገናዊነታችንን የምናሳይበት ወቅት አሁን ነዉ።

የኛ አለመግባባትና አንድ አለመሆን እንዴህ ላለ መጠቃት አሳልፎ ሲሰጠን ዛሬ አዲስ ባይሆንም መደጋገሙ እና ተጠናክሮ መቀጠሉ ግን እዚህጋ ይበቃል ልንል ይገባል።

ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊያንን መንካት የእሳት ዘንግ መጨበጥ እንደሆነ የሁለተኛዉ የዓለም ጦርነትን ጨምሮ በዘመናት የቀደመ ታሪክ የታየና ወደፊትም የሚቀጥል የመሆኑ ሐቅ ከአለት የፀና ነዉ። ይህም ቃል ኪዳን በልኡል እግዚአብሔር የታተመ የማይቀየር ቃል ነዉ።

ላስተዋለዉ የምስራቹ ደጅ ላይ ሲደረስ ይህ የጣሩ ድምጽ ጅማሬ ስለሆነ የኢትዮጵያ ብርሀን ዓለምን ሊሞላ የተጣሏትም፤ ያዋረዷትም ፈፅመዉ ሊከደኑ እጅግ ጊዜዉ ቀርቧልና አይዟቹሁ ፅኑ ። ከመቼዉም ጊዜ በበለጠ አንድነታችን ሊጠናከር የሚገባበትም ጊዜ አሁን ነዉ።

በመጨረሻም በግፍ የተገደሉትን ንፁሀን ኢትዮጵያዊ ወገኖቻችንን ነፍስ እግዛአብሔር በቀኝ መንግስቱ እንዲያሳርፍ እየተማፀንኩ ለሟች ቤተሰቦችና ለመላዉ ኢትዮጵያን ወገኖች መፅናናትን እመኛለዉ።

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር
ፍቅር ያሸንፋል
ቴዎድሮስ ካሳሁን
(ቴዲ አፍሮ)

No comments:

Post a Comment

wanted officials