Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Tuesday, June 7, 2016

ሰበር ዜና የጠቅ/ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ተመረጡ ፓትርያርኩ በከባዱ ተገሥጸዋል

ሰበር ዜና – ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅ/ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የጠቅ/ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ኾነው ተመረጡ፤ ፓትርያርኩ በከባዱ ተገሥጸዋል


their graces the gen sec-elect Abune sawiros and the gen mgr-elect Abune Deyoscoros
ለዋና ጸሐፊነት የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ፣ የደቡብ ምዕ. ሸዋ ወሊሶ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ(በግራ)፤ ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ ዋና ሥራ አስኪያጅነት የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ፣ የደቡብ እና ምሥራቃዊ ትግራይ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ(በቀኝ)
  • ፓትርያርኩ፣ የአስመራጭ ኮሚቴውን ዕጩዎች ካልተቀበሉ ነባሮቹን ብፁዕ ዋና ጸሐፊ እና ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጅ ለድጋሚ የሦስት ዓመታት የሥራ ዘመን እንደሚያስቀጥላቸው አሳስቧቸው ነበር፤
  • “እነርሱንስ ከምታስቀጥሉ እኔን አንሡኝ፤” ያሉት ፓትርያርኩ፣ ማሳሰቢያውን ተከትሎ በምልዓተ ጉባኤው በተሠየመው አስመራጭ ኮሚቴ የቀረቡትን ዕጩዎች በመቀበላቸው፣ በምስጢራዊ የድምፅ አሰጣጥ ሥርዓቱ መሠረት፣ የብፁዕ ዋና ጸሐፊው እና የብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ ምርጫ ተከናውኗል፤
  • ለቀጣይ ሦስት የአገልግሎት ዓመታት፣ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅነት የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ፣ ድምፅ ከሰጡት 38 የምልዓተ ጉባኤው አባላት የ22ቱን በማግኘት፤ ለቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊነት የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ድምፅ ከሰጡት 38 የምልዓተ ጉባኤው አባላት የ26ቱን በማግኘት በቅዱስ ሲኖዶሱ ተመርጠዋል፤
  • በምልዓተ ጉባኤው በአብላጫ ድምፅ የተመረጡት፣ አዲሱ ብፁዕ ዋና ጸሐፊ እና ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በሚጻፍላቸው ደብዳቤ ይሾማሉ፤
  • ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው፥ የቋሚ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊም ሲኾኑ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አጀንዳዎችን የማዘጋጀት፤ ውሳኔውንና ትእዛዙን ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና ለሚመለከታቸው ማስተላለፍና በተግባር ላይ መዋላቸውን እየተከታተሉ ስለአፈጻጸማቸው ለምልዓተ ጉባኤው ሪፖርት የማቅረብ ሓላፊነት አለባቸው፤
  • የመላዋ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሥራ አስፈጻሚ የኾኑት ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ፥ ከፍተኛ የአስተዳደር አካል የኾነው የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ባለሥልጣን እንደመኾናቸው፣ ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው የሚወስናቸውን ጉዳዮች በሕገ ቤተ ክርስቲያን መሠረት ይፈጽማሉ፤ ያስፈጽማሉ፤ መምሪያዎችንና ድርጅቶችን ኹሉ በበላይነት ይመራሉ፤ ማንኛውም ንብረት፣ የገንዘብ ገቢና ወጭ በቤተ ክርስቲያኒቱ የፋይናንስና የንብረት አስተዳደር ደንብ፣ በሕግ ፊት ተቀባይነት ባለው የሒሳብ አያያዝ ሥርዓት መከናወኑን ይከታተላሉ፤ ይቆጣጠራሉ፤ በየዓመቱ በርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤም፣ ዕቅድ ክንውናቸውን ያቀርባሉ፤ ሲፈቀድም ተግባራዊ ያደርጋሉ፤
  • ፓትርያርኩ የጥዋቱ የምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ ሲጀመር፣ ከመንበራቸው ተነሥተው፡-“አባቶቼ፣ ወንድሞቼ፥ ይቅርታ አስቀየምኋችኹ”ብለው ትላንት በምርጫው ሒደት ላይ ለፈጠሩት መስተጓጎል የተጸጸቱ መስለው ቢታዩም፣ ከጥቂት ቆይታ በኋላ ተመልሰው ደግሞ፤ “ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስንና ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስን አውጡልኝ” በማለታቸው ምልዓተ ጉባኤውን በእጅጉ አሳዝነዋል፤ ይህም ከባድ ተግሣጽም አስከትሏባቸዋል
    ?
  • ምልዓተ ጉባኤው ከስሕተታቸው የማይማሩትን ፓትርያርኩን በሚከተለው ቃል ነበር የገሠጻቸው፡- “የእርስዎ መሠረታዊ ችግር፣ ይህችን ቤተ ክርስቲያን አያውቋትም፤ ለ35 ዓመታት ውጭ ስለኖሩ የአህጉረ ስብከቱን ይኹን የቤተ ክህነቱን የየዘርፍ ሥራዎች አያውቋቸውም፤ ባልዋሉበትና ባላወቁት ሓላፊነት በመቀመጥዎ ሕግንና ሕገ ቤተ ክርስቲያንን መሠረት አድርገው መሥራት አልቻሉም፤ የሚያሳዝነው፥ በዚኽች ቤተ ክርስቲያን ላይ እጁን ያነሣ አካል አኹንም እርስዎን ሾመብን፤ አኹንም ከጀርባ ኾኖ ያበጣብጠናል፤ ወደ ሰላም፣ ወደ ልማት፣ ወደ ዕድገት እንዳትሔድ፤ ዘወትር የብጥብጥ ዐውድማ እንድትኾን እየሠራ ያለ አካል መኖሩን እኛም እናውቃለን፣ ሕዝቡም ያውቃል፡፡
  • ምልዓተ ጉባኤው ለቀጣይ ስድስት ወራት(ከግንቦት እስከ ሐምሌ እና ከነሐሴ እስከ ጥቅምት) በቋሚ ሲኖዶስ አባልነት የሚያገለግሉ የስድስት ብፁዓን አባቶች ምርጫም አካሒዷል፡፡ ከግንቦት እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም.፡- ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ሰላማ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፤ ከነሐሴ እስከ ጥቅምት 30 ቀን 2009 ዓ.ም.፡- ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል፣ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ፣ ብፁዕ አቡነ ዳንኤል እና ብፁዕ አቡነ ኄኖክ እንዲያገለግሉ በቅዱስ ሲኖዶሱ ተመርጠዋል፡፡
ለብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ እና ለብፁዕ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ፣ መልካም እና በውጤት የታጀበ የአገልግሎት ዘመን እንመኝላቸዋለን፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials