በሰሜን ሸዋ ዞን በመርሃ ቤቴ ወረዳ በአለም ከተማ ከመብራት ማሰራጫ ጋር በተያያዘ በተነሳ ተቃውሞ አንድ ሰው ከፌደራል ፖሊሶች በተተኮሰ ጥይት ተመትቶ ቆስሏል።
መብራት ሃይል የከተማውን የመብራት ማሰራጫ በማንሳት ወደ ሌላ አካባቢ ለመውሰድ እንቅስቃሴ ሲጀምር የአካባቢው ህዝብ ተቃውሞ አሰምቷል። እሁድ እለት ወደ ከተማዋ የገባው የፌደራል ፖሊስ ከህዝቡ ጋር ፊት ለፊት መጋጨቱን ፣ ህዝቡ በድንጋይ ራሱን ለመከላከል ሲሞክር የፌደራል ፖሊሶች ጥይት ይተኩስ እንደነበር የከተማው ነዋሪዎች ገልጸዋል። እስካሁን የተጎዱትን ሲቪሎች ቁጥር በትክክል ለማወቅ ባይቻልም፣ አንድ ሰው ቆስሎ ሆስፒታል መግባቱን ለማረጋገጥ ተችሎአል።
ይህን ዜና እስካጠናከርንበት ጊዜ ድረስ ውጥረት እንዳለ ሲሆን ፣ የዞኑ አስተዳዳሪ ህዝቡን ሰብስበው ለማነጋገር ሙከራ እያደረጉ መሆኑ ታውቋል።
በሰሜን ጎንደር ዞን በእንፍራንዝ ከተማ ደግሞ ሀምሌ 8 ቀን 2006 ዓም ከመብራት እና ከውሃ ጋር በተያያዘ የከተማው ወጣቶች ተቃውሞዋቸውን ለማሰማት ወደ አደባባይ በመውጣት ወደተለያዩ አቅጣጫዎች የሚሄዱ መኪኖች እንዳያልፉ ከልክለዋል። ለሰአታት መኪኖችን አግተው የቆዩት ወጣቶች በሃይል እንዲበቱ የተደረገ ሲሆን፣ 4 ወጣቶች አመጹን አስተባብራችሁዋል በሚል ታስረዋል። ወጣቶቹ እስካሁን ድረስ አለመፈታታቸውም ታውቋል።
በመተማ ደግሞ በኢትዮጵያ እና ሱዳን ድንበር መካከል ባለው መሬት ላይ በተፈጠረ ውዝግብ 12 ሰዎች ታስረዋል። ለሱዳን ከተሰጠው መሬት አልፎ ወደ 42 ኪሎሜትር ወደውስጥ በመግባት አንዳንድ የሱዳን ባለሀብቶች በአካባቢው ጥበቃ ከሚያደርጉ የጸጥታ ሃይሎች ጋር በመመሳጠር እና ከፍተኛ ገንዘብ በመክፈል የኢትዮጵያ አርሶ አደሮችን በማፈናቀል መሬት እየገዙ መሆኑን የአካባቢው ነዋሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል። ድርጊቱን ለመቃወም የሞክሩ 12 ወጣቶች መታሰራቸውም ታውቋል።