Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Friday, November 20, 2015

የሰማያዊ ፓርቲ አባል ናትናኤል ያለምዘውድ ...........ከሸዋሮቢት እስር ቤት!!

ሰላምታየን አቀርባለሁ!
ከናትናኤል ያለምዘውድ ...........ከሸዋሮቢት እስር ቤት!!
ይቺን ፅሁፍ የምጽፈው ዛፍ ጥላ ስር ተወሽቄ ሙቀቱን ለመከላከል ከታጠቅኋት ቁምጣ ሱሪ ላይ ደብተሬን አስደግፌ፣ ሀሳቤን ለመሰብሰብ ስሞክር አንዱ ተፈንክቶ ደም እያዘራ ሲያልፍ፣ ሌላው ስምንት ቁጥር ታስሮ አሰቃቂ የዱላ መዓት ሲወርድበት፣ ጨለማ ቤት የታሰሩት የጣዕር ድምፅና፣ በሚዝገመገመው የድርቀት ወላፈን ክፉኛ ከሀሳቤ እያናጠበኝ የምቸገር፣ ሁለት ፍራሽ ላይ ለሰባት ተጠቅጥቄ የምተኛ፣ ለጊዜው የተለያዩ ዛቻና ማስፈራሪያዎች የሚደርሱብኝ......ሸዋ ሮቢት ‹‹ልማታዊ›› ማረሚያ ቤት ላይ በአስቸጋሪው ሁኔታ ደረቴን ነፍቼ የምታሰር የሰማያዊ ፓርቲ አባል ነኝ፡፡
መቼም መንግስታት ማረሚያ ቤት ብለው ሰይመው ሲያግዙበት ኖረዋልና ስሙ ስለወጣለት ማረሚያ ቤት ልበለው! ..ምንም በሉት ብቻ ሮቢት ውስጥ ከ350 በላይ ደባሎች ጋር እንዳድር ካስገደደኝ ግቢ ሆኜ ሰላምታዬን አቀርባለሁ፡፡
ሸዋሮቢት ላይ መታሰር እጅጉን ከባድ ቢሆንም እነ እስክንድር፣ ተመስገን፣ አንዱዓለም፣ እና ሌሎችንም ሳስብ እበረታለሁ፡፡ የእነሱ መንፈሰ ጠንካራነት ለእኔም ወኔና ጥንካሬ ይሰጠኛል፡፡ ራሴን በጠቀስኳቸው ሰዎች ቁመና እየለካሁ እንዳልሆነ ልብ ይባላልኝ፡፡ ግን እውነት እላችኋለሁ መታሰሬን የሚነግረኝ ስሜት ሞቷል! መፈታቴን የምፈልገው ለተለየ (ላቅ ላለ) ተግባር እንጂ ራዕይ፣ ቁጭቴ፣ ተስፋዬ.....ቆጠራ እየተባለ ስለ ደሙና ስለወደሙ አይደለም፡፡
በእርግጥ መጀመሪያ ተቃውሞዬን ሳሰማ ፍትህ እንዲመጣ፣ የሰብአዊ መብት ጥሰት እንዲቆም ቢሆንም መታሰር እንዳለም ግን አውቅ ነበር፡፡ እናም በዚህ ጨካኝ ስርዓት ስር ብኖርም እኔም ፓርቲዬም ወደ ኋላ ልንልበት የምንችል ምንም ምክንያት ሊኖር አይችልምና ገና አንገት ለአንገት እየተናነቅን ትግሉን እናስቀጥለዋለን፡፡ ምኑ ተጀመረና!
የትግል አላማውም፣ ግቡም፣ ስሜቱም ህዝብ ነው፡፡ ህዝብን ስናስብ ደግሞ ጎዳና ላይ የወደቀው፣ አጥንትና ደሙ ተቆጥሮ የሚጋዘውና የሚሰደደው፣ የዕለት ጉርሱ ህብስተ መና የሆነበትን ሁሉ እናስባለን፡፡ ስርዓቱ በችግርና በአፈና የተሞላ ነው፡፡ ይህ የሥርዓቱ ባህሪ ነው እልፎችን እንዲቆጡ ያደረጋቸው፡፡ የእኔ ድምፅ ከዚህ የህምታ ማዕከል የድምቢጥም ብትሆን ጭው፣ ጭው ብላለች፡፡ ቢሆንም ጥያቄየም፣ አላማየም አልተመለሰምና እንደ ሸቀጥ ከተደረደርኩበት ፍራሽ ላይ ሆኜ የብዙሃንን የእሮሮ ድምፅ ማቀናበሪያ ብልሃት ሳውጠነጥንና ስሻ አድራለሁ፡፡
አቤት ደስ ሲል! ለዓላማ እየኖርክ፣ በስርዓቱ እየተፈተንክ፣ በአግቦ እየሳክ፣ በሆድህ ጥርስ እየነከስክ፣ አብዲሳ፣ ባልቻ፣ አበበ፣ በላይ፣....የተዋደቁበትን ሰንደቅ አላማ በህሊናህ ጠፈር ቀስተ ዳመና አሰርተህ፣ የአቤ ጉበኛን፣ የበዓሉ ግርማን፣ የጀ/መንግስቱ ንዋይን፣ የአንዳርጋቸው ፅጌን፣… የምንሞትለትን ህዝብ የፍትህ ጥማት በድል ለመቋጨት ዘወትር ነቅቶ መኖር፡፡
ሰማያዊ አላማችን ከምድር አሸዋ የብዙ ከዋከብት ተረጭተውበት፣ ጨረቃዋ እያብረቀረቀች በፀሀይ ድምቀትና ሙቀት ታግዞ በቃል የማይገለፅ ምሉዕነት እንዲፈጠር፣ ጥንካሬውና ውበታችን እንዲፀና እንበረታና ዓይናችን የጋረደውን ዳመና፣ በቀስተ ዳመናው ጥለት ተቋጭቶ፣ ማለፊያ ሸማ ይሰራ፡፡ የአንድነት ሸማ፡፡ ዘር ተዘራ እንጂ ሞተ፣ በሰበሰ አይባልም፡፡ ሳሙኤል አወቀ በራዕዩ ራዕያችን በቅሎ እንዲያንሰራራ፣ በርቱ! የሺዋስና መሰል ጓዶቻችን አልታበዩም አራት ዓይናማው ገጣሚ፣
‹‹አይዞህ የእኔ ጌታ ነገርክን አትርሳ፣
አለስልሰህ ዝራ የስንዴውን ማሳ፣
የተዘራችው ዘር ፈርሳና በስብሳ፣
ትበቅላለች ነገ ሞታ ስትነሳ፡፡›› ያለው ለዚህ ነው፡፡
ከግፍ በላይ ግፍ እየሰሩ ከህሊናቸው ተኳርፈው እየኖሩ በቁም እስር ለሚማቅቁ መጥኔውን እንጅ፣ እኔና ጓደኞቼ እንደ ወይን ጠጅ እያደርን ስንዋብ ይታወቀኛል፡፡ ‹‹ዘጠኝ ሞት መጣ ቢሉት…›› የሚለው ብሂል የሞት አንድና ሁለት መኖሩን ለማመልከት ነው፡፡ መራራው ሞት ተረግጦ ኖሮ መሞት ነው፡፡ ይህኛውን ሞት ወጥቼ ግባ አልለውም፡፡ እፋለመዋለሁ እንጅ! ውድ ጓዶች ሆይ! የእኛ ትውልድ ኃላፊነት በእነዚህ ስንኞች እንደተቋጠረው፣
‹‹በዚህ ባዲሱ ቃል ባዲሱ ሩካቤ፣ ተገኝቶ የመጣ፣
ይገኝ ነበር አዲስ ሀይል ትውልድ፣
ህያው ፍች የሚሰጥ ሚስጥር የሚያወጣ፣
የቀለጠ ብረት ሳይሳሳ የሚንጣጣ፡፡››
ነውና በየቀኑ ከቆምንበት ቦታ ወደ ፊት እየተነቃነቅን ህያው ፍች፣ የሚሰጥ የነፃነትና የፍትህ አርማ እንትከል፡፡ በቀጣይ ጽሁፌ ሸዋሮቢት እስር ቤትን በጨረፍታ አስተዋውቃችኋለሁ፡፡
አምላክ ኢትዮጵያን ይባርክ!

No comments:

Post a Comment

wanted officials