Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Saturday, November 28, 2015

እነ ዘላለም ወርቃገኘሁ መከላከያ ምስክሮቻቸውን አሰሙ ᎐vአንዳርጋቸው ጽጌና እስክንድር ነጋ ለምስክርነት ተጠርተዋል

እነ ዘላለም ወርቃገኘሁ መከላከያ ምስክሮቻቸውን አሰሙ
᎐አንዳርጋቸው ጽጌና እስክንድር ነጋ ለምስክርነት ተጠርተዋል
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
esknder

በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብርተኝነት ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት እየታየ የሚገኙት አምስት ተከሳሾች የመከላከያ ምስክሮቻቸውን አቅርበው አሰምተዋል፡፡ በዚህ መዝገብ የተካተቱት ተከሳሾችም ዘላለም ወርቃገኘሁ፣ ዮናታን ወልዴ፣ ባህሩ ደጉ፣ ሰለሞን ግርማ እና ተስፋዬ ተፈሪ ናቸው፡፡
ተከሳሾቹ ከሰኞ ህዳር 13/2008 ዓ.ም ጀምሮ በተከታታይ ለአራት ቀናት ምስክሮቻቸውን ያሰሙ ሲሆን፣ ዘላለም ወርቃገኘሁ 11 ምስክሮች፣ ዮናታን ወልዴ 5፣ ሰለሞን ግርማ 3፣ እና ባህሩ ደጉ እና ተስፋዬ ተፈሪ እያንዳንዳቸው 8 ምስክሮችን ጠርተዋል፡፡ ከእነዚህ መካከልም በአንደኛ ተከሳሽ ለምስክርነት የተጠሩት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እንዲቀርቡ አለመደረጋቸው ታውቋል፤ በተጨማሪም በእስር ቃሊቲ የሚገኙትና ለምስክርነት የተጠሩት አብርሃ ደስታ፣ የሺዋስ አሰፋ እና ዳንኤል ሺበሽን ማረሚያ ቤቱ ለተከታታይ ቀናት ከፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ቢተላለፍለትም ሳያቀርባቸው ቀርቷል፡፡
በዋናነት ተከሳሾች በማዕከላዊ ፌደራል ወንጀል ምርመራ በነበሩበት ወቅት የደረሰባቸውን አስከፊ የምርመራ ሁኔታና በዚሁ ምክንያት ተገድደው ስለሰጡት ቃል የሚመሰክሩ ምስክሮችን አሰምተዋል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በዚሁ በምርመራ ወቅት አብረዋቸው ታስረው የነበሩና በኋላ ላይ የአቃቤ ህግ ምስክር ሆነው ቀርበው የመሰከሩ ግለሰቦች እንዴት ተገድደው በሀሰት እንደመሰከሩባቸው ያስረዱልናል ያሏቸውን ምስክሮች አስደምጠዋል፡፡
ተከሳሾች የተከሳሽነት መከላከያ ቃላቸውን ለፍርድ ቤቱ የሰጡ ሲሆን፣ በተለይ አንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ህዳር 16/2008 ዓ.ም ለፍርድ ቤቱ በሰጠው ቃል፣ የቀረበበት ክስ ፖለቲካዊ ይዘት ያለው (politically motivated) እንደሆነና በምርመራ ወቅትም በፖሊስና ደህንነት ከተከሰሰበት ጋር በማይገናኝ መልኩ ‹‹ምርጫ 2007ን ለማደናቀፍ ቡድን አደራጅተሃል›› በሚል ሲመረመር እንደነበር አመልክቷል፡፡
ዘላለም በሰጠው ቃል የጸረ-ሽብር ህጉ አሸባሪዎችን ለመከላከልና ለመቅጣት ሳይሆን የተቃውሞ ድምጽ የሚያሰሙ ዜጎችን እና ጋዜጠኞችን ለማጥቃት እየዋለ እንደሆነም አስረድቷል፡፡ ‹‹በእኔ እምነት አሸባሪ ተብሎ የተፈረጀውና ግንኙነት አለህ በሚል የተከሰስኩበት ድርጅት አሸባሪ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ሆኖም ግን እንደ እኔ አይነቶችን ለማጥቃት መጠቀሚያ እንዲሆን ሊፈረጅ ችሏል›› ሲል ቃሉን ሰጥቷል፡፡
ለተከታታይ 41 ቀናት ቀዝቃዛና ጨለማ ክፍል በማዕከላዊ እንዳሳለፈና ለአንድ ወር ከቤተሰብ ጋር እንዳይገናኝ እንደተደረገ የተናገረው ዘላለም፣ ‹‹ለለውጥ የሚታገሉ ወጣቶች ላይ ተጽዕኖ ላለማሳደር የደረሰብኝን በደል ሁሉ እዚህ መዘርዘር አልሻም›› ሲል ገልጹዋል፡፡ በተመሳሳይ ሌሎችም ተከሳሾች በሰጡት ቃል በማዕከላዊ አስከፊ ምርመራ እንደተደረገባቸው አስረድተዋል፡፡
በዚህ መዝገብ የተካተቱት አቶ ባህሩ ደጉ እስካሁን ምስክሮቻቸውን አቅርበው ያላሰሙ ሲሆን፣ አንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ እና 6ኛ ተከሳሽ ዮናታን ወልዴ ደግሞ ቀሪ ምስክሮቻቸውን የሚያሰሙ ይሆናል፡፡ ስለሆነም ዛሬ ህዳር 17/2008 ዓ.ም ‹‹ዳኞች አልተሟሉም›› በሚል ቀሪ ምስክሮችን ማሰማት ባለመቻላቸው ለህዳር 24/2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷቸዋል፡፡
በዚሁ መዝገብ ክስ ተመስርቶባቸው የነበሩት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች የሆኑት አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ እና ዳንኤል ሺበሽ እንዲሁም መምህር አብርሃም ሰለሞን በዚሁ ችሎት ነጻ መሆናቸው ቢበየንም በአቃቤ ህግ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ተጠይቆባቸው ጉዳያቸውን በእስር ላይ ሆነው እየተከታተሉ እንዳሉ ይታወቃል፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials