Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Tuesday, November 10, 2015

የናትናኤል ያለምዘውድ ይግባኝ ክርክር ተደመጠ በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

የናትናኤል ያለምዘውድ ይግባኝ ክርክር ተደመጠ
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
የኤይ ኤስ በኢትዮጵያውያን ላይ የፈፀመውን አረመኔያዊ ድርጊት ለመቃወም መንግስት በጠራው ሰልፍ ሰበብ ታስሮ 3 አመት ከ3 ወር የተፈረደበት ናትናኤል ያለም ዘውድ የይግባኝ ክርክር ህዳር 29/2008 ዓ.ም በከፍተኛ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት ተደምጧል፡፡ አቃቤ ህግ ናትናኤል ያለም ዘውድ ላይ ‹‹በወቅቱ የተፈጠረው ረብሻ ከባድ ጉዳት ያደረሰ በመሆኑ፣ ወቅቱ ሀገራዊ ምርጫ የሚካሄድበት በመሆኑና ረብሻውም የበለጠ ችግር ያስከትል የነበር በመሆኑ፣ ሀገሪቱን ለከፋ አደጋ ያጋልጥ ስለነበር እና ያደርስ የነበረውን አደጋ ግምት ውስጥ በማስገባት›› የሚሉ የጥፋት ማክበጃዎችን ያቀረበ ሲሆን 3 አመት ከሶስት ወር ተፈርዶበት በዝዋይ እስር ቤት ይገኛል፡፡
የናትናኤል ጠበቃ በበኩላቸው ‹‹በወቅቱ ረብሻ የመፍጠር ሙከራ እንጅ ረብሻ እንዳልተፈጠረ መንግስት በመግለጫው ማመኑን፣ ተፈጠረው በተባለው ረብሻ ናትናኤል ጉዳት አደረሰበት የተባለውም ሆነ ሌላ ጉዳት የደረሰበት አካል በምስክሮች አለመቅረቡና ሀኪም ማስረጃም አለመረጋገጡ፣ መንግስት ሰልፉን ሲጠራም ምርጫውን እንዳያስተጓጉልም ተዘጋጅቶበት ሊሆን እንደሚችልና ከምርጫው ጋር ግንኙነት እንደሌለውም›› በመግለፅ ደንበኛቸው ከእስር እንዲለቀቅ ጠይቀዋል፡፡
አቃቤ ህግ በበኩሉ ‹‹ተከሳሹ ያደረሰውን ጉዳት በምስክር ወይንም በሀኪም ማስረጃ ባይረጋገጥም ህዝብ መስክሮታል፣ በህገ መንግስት የተመረጠው መንግስት በማውገዙም ከምርጫው ጋር ግንኙነት አለው፣ ሰላማዊ ሰልፍ ስለሆነ የተጎዳው ሰው በርካታ ነው›› ብሏል፡፡ ጠበቃው በበኩላቸው ‹‹ሰላማዊ ሰልፍ የሚጠራው በርካታ ህዝብ ሊገኝ ነው፡፡ ይህ ምክንያት ሊሆን አይችልም፡፡ በርካታ ወጣቶች አይ ኤስ ባደረሰው ጭካኔ በመናደዳቸው መንግስትን ማውገዛቸው ይታወቃል፡፡ ደንበኛዬን ለይቶ ብቻ ምርጫ ሊበጠብጥ ነበር ማለት ተገቢ አይደለም፡፡›› ሲሉ የእስር ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ውድቅ እንዲሆን ተከራክረዋል፡፡ የሁለቱን ክርክር ያዳመጠው ፍርድ ቤቱ መዝገቡን መርምሮ ለመወሰን ለህዳር 13/2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials