Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Sunday, November 15, 2015

እስር ቤት የሚገኙት የሰማያዊ፣ የአንድነትና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለህዝብ መልዕክት አስተላለፉ፡፡

እስር ቤት የሚገኙት የሰማያዊ፣ የአንድነትና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለህዝብ መልዕክት አስተላለፉ፡፡

እነ የሺዋስ አሰፋ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ መልዕክት አስተላለፉ
‹‹ርሃቡን ለዓለም ለማሳወቅ ከፍተኛ የህዝብ ግንኙነት ስራ መሰራት አለበት››
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
የሽብርተኝነት ክስ ተመስርቶባቸው በፌደራል ክፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ከተበየነላቸው በኋላ አቃቤ ህግ ይግባኝ ጠይቆባቸው ጉዳያቸው በጠቅላይ ፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት የሰማያዊ፣ የአንድነትና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለህዝብ መልዕክት አስተላለፉ፡፡ መልዕክቱን ያስተላለፉት በቃሊቲ እስር ቤት የሚገኙት የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታና ዳንኤል ሺበሽ ሲሆኑ በተለይ ርሃቡ ለዓለም ማህበረሰብ እንዲታወቅ የተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ ሲቪክ ማህበረሰቦች፣ ሚዲያውና ሌሎችም የቻሉትን ሁሉ እንዲያደርጉ አደራ ብለዋል፡፡
በተለይ ከመንግስት ርሃቡን የመደበቅ ባህሪ አንፃር በሌሎች ኢትዮጵያውያን በኩል ርሃቡን ለዓለም ለማሳወቅ ከፍተኛ የህዝብ ግንኙነት ስራ መሰራት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡ ‹‹በርሃቡ ምክንያት የአንድ ሰው ህይወት መጥፋት አልነበረበትም›› ያሉት የፖለቲካ አመራሮቹ መንግስት ተራበ በተባለው ህዝብ ቁጥር ጨዋታ ውስጥ ከመግባት ይልቅ ለተራቡት መድረስ እንደነበረበትም ገልፀዋል፡፡ መንግስት የተራቡትን ቁጥርና መረጃ ስለሚደብቅም ኢትዮጵያውያን ርሃቡን ለዓለም በማሳወቅ እርዳታ እንዲገኝ ከማድረግ ባሻገር እርዳታ በማሰባሰብ ሊያግዟቸው ይገባል ብለዋል፡፡
ከርሃቡ በተጨማሪ የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ጥያቄ መልስ አለማግኘቱን፣ ህገ ወጥ የእስረኛ አያያዝ፣ የፍርድ ቤቶች ገለልተኛ አለመሆንና በአጠቃላይ የፍርድ መጓደልን በስፋት ያነሱት ሲሆን እነዚህ ጉዳዮች አጀንዳ ሆነው በጠነከረ መልኩ ወደ አደባባይ መውጣት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በርካታ ችግሮችና ጭቆና ቢኖርም አጀንዳ ሆኖ መታገያ እየሆነ አይደለም ሲሉ ትዝብታቸውን ገልፀዋል፡፡ በመሆኑም በሰላማዊ ሰልፍና በሌሎችም መንገዶች አጀንዳዎቹ ለህዝብ መድረስ እንዳለባቸው መክረዋል፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials