Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Monday, October 27, 2014

በስልጠናው ጥያቄ ጠየቀና ስርዓቱን የተቸ የአንበሳ አውቶቡስ ድርጅት ሰራተኛ ታሰረ

በስልጠናው ጥያቄ ያነሳው ሰራተኛ ታሰረ
ገዥው ፓርቲ በሚሰጠው የ‹‹አብዮታዊ ዴሞክራሲ›› ስልጠና ላይ ጥያቄ የጠየቀና ስርዓቱን የተቸ የአንበሳ አውቶቡስ ድርጅት ሰራተኛ ታሰረ፡፡ ፋንታሁን የተባለው የአንበሳ ከተማ አውቶቡስ ሰራተኛ በስልጠናው ወቅት ጥያቄዎቹን በማንሳቱና ስርዓቱን በመተቸቱ መታሰሩን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡
በስልጠናው ወቅት ስላለፉት ስርዓቶች በተነሳበት ወቅት ‹‹ደርግንም ሆነ ምኒልክን እናውቃቸዋለን፡፡ እናንተ ስለ እነሱ መጥፎውን ከምትገልጹልን እንደ 97 እንደማትገድሉና ነጻና ፍትሃዊ ምትጫ እንደምታደርጉ ንገሩን፡፡›› ሲል አስተያየት የሰጠው ፋንታሁን ይህና ሌሎች አስተያየቶቹ መስሪያ ቤቱ ውስጥ የሚሰሩ የኢህአዴግ ካድሬዎችን እንዳስቆጣ ገልጾአል፡፡ ስብሰባው ካለቀ በኋላም ረቡዕ ጥቅምት 13/ 2007 ዓ.ም አንበሳ አውቶቡስ ድርጅት ውስጥ የሚሰሩ የኢህአዴግ አመራሮችና አባላት እንዲሁም ደህንነቶች እንደያዙት ገልጾአል፡፡
በስልጠናው ወቅት ጥያቄ በመጠየቁና ትችት በመሰንዘሩ አንበሳ አውቶቡስ ውስጥ የሚሰሩ የገዥው ፓርቲ ካድሬዎች ‹‹ግንቦት 7 ብሎ ጠረጴዛ ላይ ጽፏል፡፡›› የሚል የሀሰት ክስ እንደከፈቱት ፋንታሁን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡
ከታሰረ በኋላ ስልኩና የግል አጀንዳውን የተቀማ ሲሆን ስልኮቹን መስሪያ ቤቱ ውስጥ ያሉት ካድሬዎች እየተጠቀሙበት እንደሆነና ስልክ ሲደወልም እያነሱ እያነጋገሩ እንደሆነ መረጃ እንደደረሰው ገልጾልናል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ስለ አገሩ ወቅታዊ ሁኔታ የጻፋቸውንና ሌሎችንም ጉዳዮች ያሰፈረበትን የግል ማስታወሻው ደህንነቶች ‹‹ምን ማለት ናቸው? ከማን ጋር ነው የምትገናኘው?›› እያሉ ጫና እያሳደሩበት መሆኑን አስታውቋል፡፡
ስልኩና ማስታወሻ በካድሬዎችና በደህንነቶች እጅ በመግባቱ ‹‹የግል ማስታወሻዬና ስልኬን ደህንነቶችና የኢህአዴግ ካድሬዎች እየተጠቀሙበት በመሆኑ እኔ ግንኙነት ከሌለኝ አካል ጋር ግንኙነት እንዳለኝ አሊያም ያልጻፍኩትን የጻፍኩ በማስመሰል እንደማይከሱኝ እርግጠኛ አይደለሁም፡፡›› ሲል ፋንታሁን ስጋቱን ገልጾአል፡፡
ፋንታሁን በተለምዶ ችሎት ተብሎ በሚጠራው ቀጨኔ መዳህኒያለም አካባቢ በሚገኝ ወረዳ 9 ፖሊስ ጣቢያ ታስሮ የሚገኝ ሲሆን ነገ ማክሰኞ/ ጥቅምት 18 ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ ይጠበቃል፡፡
የ‹‹አብዮታዊ ዴሞክራሲ›› ስልጠናን ለ11 ቀናት የወሰዱት የከተማ አውቶቡስ ድርጅት ሰራተኞች ስልጠናውን በደንብ አልተከታተላችሁም በሚል ተጨማሪ 8 ቀን ቅጣት ተጥሎባቸው ስልጠናውን ዳግመኛ እንደወሰዱ ነገረ ኢትዮጵያ መዘገቧ ይታወሳል፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials