ግምገማው የተመራው በአዳማ ከተማ ከንቲባ ሲሆን፣ ከንቲባው ቀደም ብለው ያዘጋጁዋቸው አባላት በምክትሉ ከንቲባ በአቶ አህመድ የሱፍና በድርጅት ጉዳይ ሃላፊው በአቶ ፍቅሩ ጂረኛ  ላይ የስድብ ናዳ በማውረድ ገምግመዋቸዋል። ምክትል ከንቲባው ከዚህ ቀደም ወደ አሜሪካ ለመሄድ ወደ ቦሌ ሲያቀኑ፣ በደህንነት ሃይሎች እንዲመለሱ ከተደረጉ በሁዋላ፣ በከንቲባውና በምክትሉ መካከል ያለው አለመግባባት እየሰፋ ሄዶ፣ ጸብ ደረጃ ደርሷል። ከንቲባውና በዙሪያቸው አሰለፉዋቸው ሰዎች ምክትሉን ከእስላም አክራሪነትና ከኦነግ ጋር በመፈረጅ እንዲገመገሙ ሲያደርጉ፣ አቶ ፍቅሩን ደግሞ አንባገነን ናቸው በሚል አስገምግመዋቸዋል። ከንቲባው በስልጣን መባለግ እንዲገመገሙ ሃሳብ ቢቀርብም፣ በፌደራሉ መንግስት እንጅ በአባላት አይገመገሙም ተብለው እንዲታለፉ ተደርጓል።
አብዛኞቹ አባላት በአመራሩ ላይ ተቃውሞ በማሰማታቸው፣ ከክልል ተወክለው የመጡ ባለስልጣናት ሊያረጋጉዋቸው ሲሞክሩ ታይተዋል። መረጃዎቻቸውን በኢሳት እየወጡ ነውና አባላት ጥራት ጥያቄ ምልክት ውስጥ ነው ያሉት አስገምጋሚው፣ አባሎቹም ” ሁላችንም ራሳችንን መፈተሽ አለብን” የሚል መልስ ሰጥተዋል።
አባሎቹ አንደኛውን አመራር ሴቶችን በማማገጥ ሲከሱት ሌላውን አመራር ደግሞ ድርጅቱን በመግደል ከሰውታል። አስተያየት ሰጪዎች “ኦህዴድ እንደ ከተማዋ ሞቷል” በማለት ተናግረዋል። ግምገማው እስከቀጠና ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል።