Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Wednesday, January 6, 2016

በኦሮሚያ የተጀመረው ተቃውሞ መቀጠሉ የመንግስት ባለስልጣናትን ግራ አጋብቷል

በኦሮሚያ የተጀመረው ተቃውሞ መቀጠሉ የመንግስት ባለስልጣናትን ግራ አጋብቷል
ታኀሳስ ፳፯ (ሃያ ሰባት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-
በአገር ቤት የሚገኙ የተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች በመንግስት የክትትል መረብ ውስጥ መግባታቸውን ተከትሎ የጎላ ተሳትፎ በማያደርጉበት ሁኔታ፣ ህዝቡ ራሱን እያደራጀ ተቃውሞውን መቀጠሉ መንግስት ለሚወስደው ጭካኔ የተሞላበት እርምጃ ሰበብ እንዲያጣ እንዳደረገውና በኢህአዴግ ውስጥ ቅራኔ እየፈጠረ መምጣቱን ምንጮች ገልጸዋል።
ከአሁን ቀደም ተቃውሞውን ጸረ-ሰላም ሃይሎች እንዳዘጋጁት ተደርጎ ይነገር የነበረው ዜና፣ በህዝቡ ዘንድ ተቀባይነት አለማግኘቱና ተቃውሞውም መቀጠሉ ያሳሰባቸው ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ለካድሬዎች የሚሰጡት አርኪ መልስ ማጣታቸው ስብሰባዎች ያለውጤት እየተበተኑ ነው። በዚህም የተነሳ በድርጅቶች ውስጥ ያለው ቅሬኔ እየሰፋ ነው። በርካታ የኦህዴድ ካድሬዎች፣ “ህዝቡን ልናሳምን ቀርቶ እኛንም አላሳመናችሁንም” እያሉ ሲሆን፣ በኦህዴድ ካድሬዎችና በተወሰኑ የህወሃት መሪዎች መካከል ጥርጣሬው እየሰፋ መሄዱ ፣ድርጅቱ አጠቃላይ ግምገማ እንዲያደርግ ሳይገደድ እንደማይቀር ምንጮች ጠቁመዋል።
“ኢህአዴግ እንደ አንድ ድርጅት መናበብ ተስኖታል” የሚሉት ምንጮች፣ የአሁኑ ልዩነት በተራው ካድሬ፣ በመካከለኛ አመራሩና በከፍተኛ አመራሩ መካከል መሆኑን ገልጸዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ዛሬ በሂርና ከተማ ተቃውሞ ሲካሄድ ውሎአል። ነዋሪዎች ተቃውሞአቸውን ድንጋይ በመዝጋት ጭምር ገልጸዋል። የመንግስት ወታደሮች በወሰዱት እርምጃ ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ነዋሪዎች ተጎድተዋል።
በወለጋ ዩኒቨርስቲ ደግሞ የ4ና አመት የዩኒቨርስቲ ተማሪ የሆነው በንቲ ኢራነ የተባለ የምግብ ሳይንስ ተማሪ ከሶስት ቀናት በፊት በወታደሮች ተይዞ ከተወሰደ በሁዋላ ተገድሎ ውሃ ውስጥ ተጥሎ ተገኝቷል።
ሌላው አሰቃቂ ድርጊት የተፈጸመው ባለፈው ሳምንት ታህሳስ 24፣ 2008 ዓም ጉድሮ ላይ ሲሆን፣ አንድ የአንደኛ ክፍል ተማሪ በአሰቃቂ ሁኔታ ተገድሏል። ተመሳሳይ ግድያዎች በአምቦ እና ጅማ መፈጸማቸውንም ለኢሳት የሚደረሱት መረጃዎች አመልክተዋል።
ሶስት ታዋቂ የሆኑ የኦሮምኛ ዘፋኞች ሃዊ ተዘራ፣ ጅሪንያ ሽፈራ እንዲሁም ብሊሱማ ዲንቃም መታሰራቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

No comments:

Post a Comment

wanted officials