Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Tuesday, August 19, 2014

የሕዳሴ አብዮት ለፖለቲካው ( አስራት አብርሃም)

ወዳጄ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ የህዳሴው አብዮት አይቀሬ እርግጠኛ ሆኗል፤ እኔም ያለኝ ግምት ተመሳሳይ ነው። በመሆኑም የዛሬው ፅሁፌ የሚያተኩረው የህዳሴው አብዮት እንዴትና የት ይጀምር? በሚለው ርዕሰ ጉዳይ ላይ ይሆናል። በእኔ እምነት የህዳሴው አብዮት መጀመር ያለበት ከራሱ ከተቃውሞ ጎራ ነው የሚል ነው። ምክንያቱም የለውጡን ሀይል የሚመራው ይሄ የተቃውሞ ጎራ ስለሚሆን በመጀመርያ ውስጡን ማጥራትና ማጠናከር ስላለበት ነው። ስለዚህ፣ ከሁሉም ነገር በፊት የተቃውሞ ጎራው በትክክልና በተገቢው ሁኔታ እንዲታደስና እንዲለውጥ ማድረግ ያስፈልጋል ማለት ነው። ስለፖለቲካው መታደስና መለወጥ ሲታሰብ ደግሞ እንዴት ነው የሚታደሰው? እንዴት ነው የሚለወጠው? የሚሉትን ጥያቄዎች ማንሳት ተገቢ ይሆናል። የመጀመርያው ነገር፣ እስካሁን ከተጓዝንበት ኋላቀርና ውጤት አልባ የትግል ስልት የሚያወጣን፣ የተለየ ያካሄድ ለውጥና የሰላማዊ ትግል እንቅስቃሴ ለማደረግ የሚያስችለን ብቁ የሆነ ፖለቲካዊ አመራር ወደፊት እንዲመጣ ማድረግ ነው። በተለይ ደግሞ ፖለቲካዊ ትግሉ በአስራር፣ በአደረጃጀት፣ በዴሞክራሲያዊ ባህልና በበሳል አመራር ማጠናከርና ማነፅ ቀዳሚው ተግባር ነው የሚሆነው።
በቅርቡ ሊካሄድ ታስቦ የነበረውና በኋላ በምርጫ ቦርድ ምክንያት ለጊዜው የተቋረጠው የአንድነትና የመኢአድ ውህድ ፓርቲ ፕሬዝደንት የሚሆን ሰው ለመምረጥ በአንድነት ውስጥ የታየው እጅግ ማራኪና አስተማሪ የሆነ ዴሞክራሲያዊ ውድድር፣ የሰለጠነ የእጩዎቹ ደጋፊዎች ቅስቃሳ የዚሁ የህዳሴው አብዮት ጅማሮ አድርጌ ነው የምወስደው። ይሄ ዴሞክራሲዊ የሆነ ውድድር በማህበራዊ ሚዲያዎች፣ በጋዜጦችና በመፅሔቶች በጉልህ ይታይ ስለነበር የተቃውሞ ጎራ አባላት፤ ህዝቡ፣ የገዥው ፓርቲ ሰዎችም ጭምር በአንክሮ እንዲከታተሉት ምክንያት ሆኗል። ይህ እንቅስቃሴ አንድነትን ወደ ተሻለ ከፍታ የሚወስደው ከሆኑም ባሻገር ልክ እንደ ዐረቡ አብዮት ወደ ሁሉም የተቃውሞ ጎራ የሚዛመት አዲስ መንፈስ ነው ብዬ ነው የማስበው። ምንም እንኳ በተወሰነ መልኩ በዴሞክራሲያዊ ውድድርና በውስጣዊ መከፋፋል መካከል ያለውን ልዩነቱ በትክክል ያልገባቸው ወይም እንዲገባቸው ያልፈለጉ አንዳንድ ሰዎች የሚፈጥሩት ችግር የነበረ ቢሆንም በአጠቃላዩ እንቅስቃሴ ሲታይ ግን በኢትዮጵያ የፓርቲዎች ታሪክ ውስጥ በአዲስነቱ፣ በፈር ቀዳጅነቱና በአንፀባራቂነቱ ሊታወስ የሚችል ነው። ከዚህ ልምድ በመውሰድ የአንድነት አባላት ዴሞክራሲያዊ በሆነና በሰለጠነ መንገድ መሪዎቻቸውን መምረጥ የሚችሉበት ሁኔታ ከፈጠሩ፤ የሌሎች ፓርቲ አመራር አባላትም በተመሳሳይ መንገድ መሄድ የማይችሉበት ምንም ዓይነት ምክንያት የለም። ስለዚህ በአንድነት ፓርቲ ውስጥ የተሳካ የተሀድሶ አብዮት ማካሄድ ከቻልን ቀጥሎ በመኢአድ፣ በመድረክ፣ በአረና፣ በኦፌኮ፣ በደቡብ ህብረት፣ በኢዴፓና በአጠቃላይ በተቃውሞ ጎራ ባሉ ኃይሎች ሁሉ ይሄ የለውጥ እንቅስቃሴ እንዲቀጣጠል እድል የሚፈጥር ነው የሚሆነው። በመሆኑም ውህደቱ ለጊዜው ቢጨናገፍም በአንድነት አባላትና ደጋፊዎች ዘንድ የተጀመረውን የትግል መነሳሳት መቀዝቀዝ የለበትም። ይሄ መነሳሳት ፓርቲውን በአዲስ መንፈስና በአዲስ ፖለቲካዊ አካሄድ ለማስኬድ በሚያስችል መልኩ ልንጠቀምበት እንችላለን። ባለበንት እንድንረግጥ ከሚያደርገን ያረጀና ያፈጀ ፖለቲካዊ አሰራር ፖለቲካው ይላቀቅ ዘንድ የለውጥ ኃይሉ በአንድነት ውስጥ የፓርቲው ህግና ስርዓት በሚፈቅደው መሰረት የተሀድሶ እና የለውጥ እንቅስቃሴ ማካሄድ መቻል አለበት። ይሄ የለውጥ እንቅስቃሴ የፓርቲውን አንድነትና ጥንካሬ አስጠብቆ አሸናፊ ሆኖ የሚወጣ ከሆነ በሁሉም የተቃውሞ ጎራ ውስጥ የሚቀጣጠል፤ በእንቅልፍና በድንዛዜ ውስጥ ያሉት ፓርቲዎች ሁሉ የለውጥና የፀደይ አብዮት ውስጥ የሚገቡበት ሁኔታ እንዲፈጠር ምክንያት የሚሆን ነው።
ይሄ ብቻ አይደለም፤ እውነተኛ የተቃውሞ ኃይሉ ወደ አንድ ጠንካራ ዴሞክራሲያዊ አውራ ፓርቲነት የሚለወጥበት ሁኔታ እንዲፈጠርም ምክንያት ይሆናል። በሁሉም ፓርቲዎች ያለው የየራስ ፓርቲ ጥግ አስይዞ ፖለቲካውን ባለበት እንዲረግጥ እያረገ ያለው ፖለቲካዊ አሰራርና ኋላቀር አካሄድ መለወጥና ከስሩ መንቀል ከተቻለ፤ የአንድ አውራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ውልደት እውን የሚሆንበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም። ከዚያ በኋላ አንድነት፣ መኢአድ፣ ሰማያዊ፣ ኦፌኮ፣ አረና ወዘተ የሚል ሳይሆን አንድ የተጠናከረ የተቃውሞ ጎራ መንፈስ ብቻ ነው የሚኖረው። ትግሉም በአምባገነኑ ገዥው ፓርቲ እና በዴሞክራሲያዊው አውራ ፓርቲ መካከል ብቻ ስለሚሆን በሰላማዊ ትግል ህዝባዊ ማዕበልና ንቅናቄ ለመፍጠር የተመቻቸ ነው የሚሆነው። የህዳሴው አብዮት በተቃውሞ ጎራ መካሄድ አለበት ሲባል፤ የተቃውሞ ጎራው በውህደትም ይሁን በሌላ መንገድ (ከየፓርቲው እየፈረሰ የተሻለ ወደ ሚለው ፓርቲ በመግባት) ወደ አንድ የለውጥ ኃይልነት ይሰባሰባል፤ ይደራጃል። ከዚያ ኋላ በጠቅላላ በሀገሪቱ የህዳሴ አብዮት እንዲካሄድና እውን እንዲሆን ማደርግ የሚከብድ አይሆንም። እንዲህ በተበታተነ ሁኔታ ከተገባ ግን መጨረሻው ያው እንደተለመደው ውድቀት ነው የሚሆነው ነው።
የተቃውሞ ፖለቲካ የለውጥ እና የመነሳሳት ሰፈር፣ የአዲስ ፖለቲካዊ አስተሳሰብ መንፈስ ጎራ መሆን አለበት እንጂ በተለያዩ ጊዜያትና ሁኔታዎች የከሰሩና የከሸፉ ፖለቲከኞች ማጠራቀሚያና መደበቂያ ዋሻ መሆን የለበትም። በራስ ውስጥ የህዳሴ አብዮት ማካሄድ ወሳኝ ቅድመ ሁነት የሚሆነው፣ በፖለቲካው ጎራ እየተስተዋለ ያለው አባታዊነት፣ ቡድናዊነትና ራዕይ አልባነት ይቀየር ዘንድ ነው። ለዚህ ደግሞ በመጀመርያ የፓርቲ አባላት በፓርቲያቸው ውስጥ ያላቸው መብት እኩል መሆኑ፤ ከየትኛውም የፓርቲያቸው አባልና አመራር ጋር የሚኖራቸው ማንኛውም ዓይነት ግንኙነትም በእኩልነትና በነፃነት መርህ ላይ የተመሰረተ መሆኑ ታውቆና ተረጋግጦ ኋላቀርና ፊውዳላዊ ከሆነው የጌታና የሎሌ ዓይነት ግንኙነት ነፃ መውጣት አለባቸው። ከዚህም ባሻገር ፖለቲካ ማለት የአንድን ግለሰብ ወይም የተወሰነ ቡድን ምንዝር ሆኖ መኖር አድርገው የሚያስቡ አባላት ካሉ በተገቢው ሁኔታ ማሰልጠንና ማስተማር ያስፈልጋል። በተቋውሞ ፖለቲካ ውስጥ ያለው ትልቁ ችግር የዴሞክራሲ እና የሌበራሊዝም ባህል ጠንቅቆ ያለማወቅ፤ በአጠቃላይ ደግሞ የፖለቲካ እውቀት ማነስ ነው። ስለዚህ ይሄ ሁኔታ መቀየር አለበት፤ ይሄ የሚቀየረው ደግሞ ለአባላትና ለደጋፊዎች ተደጋጋሚ የሆነ ስልጠና መስጠት፤ የክርክርና የውይይት መድረኮች በማዘጋጀች ተመሳሳይና ተቀራራቢ የሆነ ፖለቲካዊ አቅምና ራዕይ መፍጠር ሲቻል ነው። ከዚህም በተጨማሪ በተቻለ አቅም የጥናትና የንባብ ማዕከላት በማቋቋም በፅንሰ ሀሳብ እና በፖለቲካዊ እውቀት የታነፁ ጠንካራ አባላትና ደጋፊዎች እንዲኖሩ በማድረግ ፖለቲካዊ ትግሉ በብቃትና በጥበብ ለመምራት የሚያስችል አቅምና ሁኔታ መፍጠር ይቻላል።
አሁን ባለው የሀገራችን ነባራዊ ሁኔታ የፓርቲ ፖለቲካ ብቻውን ብዙም አዋጪ አይደለም፤ ትግሉ ወደ ህዝባዊ ማዕበልና ንቅናቄ መቀየር ካለበት ሰፋ ያለ መዋቅር መፍጠር ያስፈልጋል። ይሄ ህዝባዊ ማዕበልና ንቅናቄ ደግሞ አሁን ባሉት ድኩማን ፓርቲዎች ሊመራ የሚችል ነገር አይደለም። ሲጀመር በየፓርቲዎቹ ያሉት መሪዎች ከፍተኛ የግል የስልጣን ጥም ያለባቸውና በደመነ ነፍስ ፖለቲካውን መምራት የሚፈልጉ፤ ራዕይ አልባ መሪዎች ናቸው። በመሆኑም አሁን ልናካሄደው እያሰብነው ያለውን ፍፁም ሰላማዊ የሆነ፣ ዘመናዊ የለውጥና የህዳሴ እንቅስቃሴ ለመምራት አቅም አላቸው ተብሎ የሚታሰብ አይደለም። እኔ በበኩሌ በፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ፣ በዶ/ር መራራ ጉዲና፣ በኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው እና በመሳሰሉት የስልሳው ትውልድ ቅሪቶች ትግሉ ተመርቶ ለውጥ ይመጣል ብዬ አላስብም። ሰላማዊ ትግሉ ለውጥ እንዲያመጣ ከፈለግን ፖለቲካው ላለንበት ዘመን በሚመጥኑ ጠንካራና ቆራጥ ሰዎች መመራት አለበት። የአንዷለም አራጌ፣ የናትናኤል መኮነን፣ የሀብታሙ አያሌው፤ የዳንኤል ሽበሺ ፓርቲ ከፖለቲካዊ እስር ይቅርታ ጠይቆ በተፈታ ሰው ሊመራ የሚችለው እንዴት ነው! አንዷለም አራጌ ከስርዓቱ ጋር ተደራድሮ፣ ይቅርታ ጠይቆ መውጣት፣ ከዚያም ሊቀመንበር መሆን አቅቶት እኮ አይደለም! ዳገቱ ላይ የሚቆም ሰው በመጥፋቱ እኔ እስኪ መስዋዕት ሆኜ ምሳሌ ልሆን ብሎ ነው፤ በእስር ቤት መከራና ግፍ እየተቀበለ ያለው። ለእነዚህ ጀግኖች እያስተላለፍነው ያለው መልዕክት እኮ ትክክል አይደለም። በግፍ ያሰራቸውን ሰርዓት ይቅርታ ጠይቀው እንዲወጡ የሚያደርግ ነው። ለዚህ ነው ለመታሰርና ለመሞት የተዘጋጁ አባላት በተመሳሳይ ሁኔታ ለመታሰርና ለመሞት በተዘጋጀ መሪ መመራት አለባቸው የምለው።
እኔ ለኢንጂነር ግዛቸው እንደመሪዬም፣ እንደ አንድ የሀገሬ አንጋፋ ፖለቲከኛም ትልቅ አክብሮት ነው ያለኝ፤ ለፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ እና ለዶ/ር መራራ ጉዲናም እንዲሁ ተመሳሳይ የሆነ አክብሮት አለኝ። በጊዚያቸው ያደረጉት ተጋድሎም ቢሆን እጅግ የሚመሰገን ነው። በተለይ ዶ/ር መራራ ጉዲና በኦሮሞ ህዝብ ፖለቲካዊ ትግል ላይ የራሳቸው አሻራ ያኖሩና በዓይነቱ የተለየ የትግል መንገድ ያሳዩ ትልቅ ሰው ናቸው። ለዚህ አበርክቷቸው ትልቅ ምስጋና ሊሰጣቸው የሚገባ ነው። ነገር ግን እነዚህ አንጋፋ የፖለቲካ መሪዎች ባለፉት ሀያ አመታት ትግሉን መርተው የሚፈለገው ያህል አመርቂ ለውጥ አላመጡም በሚለው መሰረታዊ ነገር ላይ ማትኮር ያሻል።
ስለዚህ ከእኛ ወዲያ ላሰር ከሚል የግል ስሜትና ፍላጎት ወጥተው እስኪ ደግሞ ከታች ያሉት አዳዲስ ትውልዶች ይምሩትና እንየው፤ እኛ ደግሞ አጠገባቸው ሆነን ምክርና ድጋፍ እንስጥ ወደሚል በጎ ሀሳብ መምጣት መቻለ አለባቸው። በእውነቱ እንነጋገር ከተባለ፣ ኢንጂነር ግዛቸው በጣም ትልቅ ሥራ ሰሩ የሚባለው ተመልሰው ወደ መሪነት ሲመጡ ካቢኒያቸው ብቃት ባላቸው ታጋዮችና ምሁራን እንዲዋቀር ማድረጋቸው ነው። ተክሌ በቀለ፣ በላይ ፍቃዱ፣ ስዩም መንገሻ፣ ዳንኤል ተፈራ፣ ኢንጂነር ዘለቀ ረዲ፣ ሰሎሞን ስዩም፣ ሀብታሙ አያሌው፣ ዳዊት አስራደ፣ ዘካርያስ የማነ ብርሃን፣ አለነ ማህፀንቱንና ሌሎችም ያየን እንደሆነ ሥራቸውን ለማመስገን እንገደዳለን። በእድሜም ቢሆን በወጣትነት እድሜ ላይ ካሉት ጀምሮ እስከ ጎልማሳ እድሜ ድረስ ያሉ ናቸው። ይሄ በራሱ ፈር ቀዳች የሚባል ዓይነት ነው። ችግሩ ግን እንዲህ ዓይነቱ ጠንካራ ስብስብ የያዘ ካቢኔ ለራሳቸው ለኢንጂነሩም ቢሆን ፈታኝ የመሆኑ ነገር ነው። እንዲህ ያለ በልምድ፣ በትምህርትና በእውቀት የተጠናከረ ካቤኔ መሪ መሆን ባንድ በእኩል መታደል ሲሆን፣ በሌላ በእኩል የግል ስሜትና የክብር ጉዳይ የሚቀድም ከሆነ ደግሞ የዚያው ያህል ስራዎች እንዲበላሹ፣ አብሮ የመስራትና የመተጋገዙ መንፈስ እንዲዳከም ምክንያት ይሆናል።
በመሰረቱ ለውጥ የምንፈልገው በፖለቲካው ዘገምተኝነት እጅግ በጣም ስለተሰላቸን ነው። ለውጥ እንፈልጋለን፤ ፖለቲካው ከገባበት የአዙሪት ሽንፈት የሚላቀቅበት መንገድ እንፈልጋለን፤ ስለዚህ እነዚህ አንጋፋ ፖለቲከኞች እንቅፋት መሆን የለባቸውም፤ ወይም ራሳቸውን ለመለወጥና በተገቢው ሁኔታ ትግሉን ለመምራት ቆርጠው መነሳት አለባቸው፤ ወይም አቅሙ ላላቸው ማስተላለፍ መቻል አለባቸው። ካሁን በፊት እንዳልኩት የፖለቲካ ብቃት በእድሜ ማነስም ሆነ መብዛት የሚገናኝ አይደለም። ችግሩ ያለው የቀደመው ትውልድ ትንታጉና ብቃት የነበረው ሁሉ በልዩ ልዩ መንገድ ማለቁ ነው። አሁን የዚያ ትውልድ አመዱ ብቻ ነው የቀረው ማለት ይቻላል፤ ያሉትም ቢሆኑ በእድሜ መግፋት፣ በኑሮ ጫና እንዲሁም በዴሞክራሲያዊ ባህል እጥረት ምክንያት አሁን ያለውን ትግል ለመምራት ይቸገራሉ የሚል እምነት ነው ያለኝ። ስለዚህ ፖለቲካዊ ፍላጎትና መሪ የመሆን ምኞት ካላቸው፤ ቢያንስ በዴሞክራሲያዊና በሰለጠነ መንገድ የምናደርገውን የለውጥ ትግል እነርሱም በተመሳሳይ ሁኔታ በሰለጠነ መንገድ መታገልና መወዳደር ይችላሉ፤ በፖለቲካው መስክ እስካሉ ድረስ መብታቸውም ነው። ነገር ግን ኋላ ቀር ከሆነው የጠልፎ መጣል ሴራ እና የፍረጃ ፖለቲካ መውጣት መቻል አለባቸው።
ከሁሉም ነገር በፊት ለሀገርና ለህዝብ ነው መታሰብ ያለበት። በፖለቲካው ትግል መስክ ያገናኘንም ዋነኛው ምክንያት ይሄ የሀገር እና ህዝብ ጉዳይ ነው። የህዳሴው አብዮት ማካሄድ አስፈላጊ የሚሆነው የተወሰነ ቡድን ፖለቲካዊ ፍላጎት ለማርካት ሳይሆን በጠቅላላ ሀገርና ህዝብ ለመለወጥ፤ የህግ የበላይነት የሰፈነበት የተደላደለ ህገመንግስታዊ ስርዓት ለማምጣት ነው።
በሌላ መልኩ ካየነው ደግሞ፣ የተቃውሞ ጎራው የተሳካ ተሀድሶ ማካሄድ ከቻለ፣ በገዥው ፓርቲ ቤት ውስጥም ተመሳሳይ ሁኔታ እንዲፈጠር ምክንያት ሊሆን የሚችል ነው። ከዚህም ባሻገር ትልቅ የሆነ የአስተሳሰብና የአተያይ ለውጥ እንዲመጣ የሚያደርግ ነው። ከድል በኋላ ግንባሩን የተቀላቃሉ ወጣቶችና ምሁራን “እኛስ ከማን እናንሳለን? ለምን እውነተኛ የሆነ የተሀድሶና ለውጥ እንቅስቃሴ አናደርግም?” ብለው እንዲያስቡና እንዲነሳሱ ሊያደርጋቸው ይችላል። ይሄ ከሆነ ደግሞ ብዙ ነገር ተቃለለ ማለት ነው። ታንክና መድፍ እያንጋጋ ከመጣው አሮጌ አመራር ይልቅ በብዙ መልኩ እኛ የሚመስሉትን አዲሶቹ የኢህአዴግ ትውልዶች ጋር መነጋገርና መግባባት የሚቻል ነው የሚመስለኝ። ሲጀመር እነርሱ ስልጣን ቢያጡም እንዲህ እንሆናለን፣ እንታሰራለን፣ ይበቀሉናል የሚሉበት ሁኔታ የለም። ስልጣን ቢያጡ እንኳ ሰርተው ወይም ነግደው የሚኖሩበት ሁኔታ ነው የሚኖረው። እንዲያውም በስርዓቱ አማካይነት የተሻለ ኢኮኖሚያዊ አቅምና የትምህርት እድል እንዲኖራቸው የተደረገ በመሆኑ እውነተኛና ዴሞክራሲያዊ የሆነ የነፃ ገበያ ስርዓት ሲሰፍን በተሻለ ሁኔታ ተጠቃሚ ለመሆን ከሌላው የተሻለና የተደራጀ አቅም ያላቸው ይሆናሉ።
ከፖለቲካዊ ተፅዕኖ ገለልተኛ የሆኑ ተቅዋማትና የህግ የበላይነት የሰፈነበት የተደላደለ ስርዓት እስካለ ድረስ ሰዎች በነበራቸው ፖለቲካዊ አመለካከት የሚጠቁበት ሁኔታ ፈፅሞ አይኖርም። ለዚህ ነው፤ እኔ የተሻለ አስተሳሰብና ፖለቲካዊ ባሀል በማምጣት በገዥው ፓርቲ ጥላ ስር ያሉትን ዜጎች ሳይቀር አዎንታዊ ተፅዕኖ በመፍጠር የዚህ የህዳሴው አብዮት አካል እንዲሆኑ ማድረግ እንችላለን የምለው። በመሆኑም ይሄ የለውጥ ፕሮጀክትና የተሀድሶ እንቅስቃሴ እንዲሁ በቀላሉ የሚታይና የሚታለፍ መሆን የለበትም። በዚህች ሀገር ያለው ፖለቲካዊ ባህል እንዲለውጥ የምንፈልግ ሁሉ ሀሳቡ ማስፋት ማጠናከር ብሎም ወደ መሬት በማውረድ ለተግባራዊነቱ ቆርጠን መነሳት፣ በተገቢው ሁኔታም መንቀሳቀስ መቻል አለብን። በዚህ መንገድ ከታገልን ለሁላችንም የምትበቃ፤ የተሻለችና ሁሉም ዜጎቿ ያለልዩነት የሚኮሩባት ሀገር እንድትኖረን ማድረግ እንችላለን። ስለዚህ የህዳሴው አብዮት በዚህ ሁኔታና እይታ ነው መቃኘት ያለበት የሚል እምነት ነው ያለኝ።

No comments:

Post a Comment

wanted officials