ኢንጂነግር ግዛቸው በሕዝብ ዘንድ በጉጉት የሚጠበቀዉን፣ ለአገዛዙ ራስ ምታት የሆነው፣ የመኢአድ እና አንድነት ዉህደት አመቻች ኮሚቴን አፈረሱ። በአባላትና ደጋፊዎች ዘንድም ትልቅ ድንጋጤ ተፈጥሩዋል። በአገዛዙም ዘንድ ደስታው ጨምሩዋል።
– በዉጭ አገር ያሉ የአንድነት ደጋፊዎች በኢንጂነር ገዛቸው ላይ ከፍተኛ ተቃዉሞ እያሰሙ ናቸው።
የመኢአድ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊ ፣ አቶ ተስፋሁን አለምነህ፣ ለሕብር ራዲዮ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ የአንድነት እና መኢአድ ዉህደት የሕዝብ ጥያቄ እንደሆነ ገልጾ፣ ገዢው ፓርቲ ምርጫ ቦርድን ተጠቅሞ የሚያስቀምጣቸው መሰናክሎችን አጥብቀው እንደሚያወግዙ ገልጸዋል። ድርጅታቸው አቶ አበባው መሐሪን ጠቅላላ ጉባኤ ጠርቶ ሲመርጥ፣ የምርጫ ቢርድ ሃላፊዎች በተገኙበት የተደረገ እንደሆነ የገለጹት አቶ ተስፋሁን፣ አገዛዙ ዉህድቱ እንዳይሳካና ተቃዋሚዎች ተከፋፍለው እንደለመደው የ2007 ምርጫን አጭበርብሮ ለማሸነፍ ሲል፣ ሆን ብሎ እያደርገ ነው ሲሉም ከሰዋል።
መኢአድ ሰላማዊ ሰልፎችን፣ የሥራና የትምህርት ማቆም አድማዎችን እንደሚጠራ የገለጹት ቶ ተስፋሁን፣ ትግሉ የሚጠይቀው ማናቸዉን መስወአትነት ለመክፈል አመራሩ እንደተዘጋጀም አስረድተዋል።
የመኢአድ እና የምርጫ ቦርድ ፍጥጫ በዚህ ሁኔታ እንዳለ ፣ ከመኢአድ ጎን በመቆም አጋርነት ይገልጻሉ፣ ምርጫ ቦርድ ላይ በጋራ ጫና ለማድረግ ድርጅታቸው ያሰልፋሉ ተብለው የሚጠበቁት፣ ኢንጂነር ግዛቸው፣ ከአንድ ሳምንት በፊት አገር ዉስጥ ላሉ ጋዜጦች የሰጡትን አስተያየት በመቀልበስ፣ የዉህደት አመቻች ኮሚቴዉን ያፈረሱ ሲሆን፣ ለውህደት በሚደረገዉ ከፍተኛ ትንቅን ላይ ቀዝቃዛ ዉሃ ከልብሰዉበታል።
«ኢንጂነር ግዛቸው በአሁኑ ወቅት ከመኢአድ ጋር በመሆን፣ በጋር የሚሊዮኖች ንቅናቄን በማጡዋጣፍ ፣ ሕዝባዊ እንቅስቃሴዎችን በማድረግ፣ በምርጫ ቦርድና አገዛዙ ላይ ጫና ማሳደር ሲገባቸው፣ የዉህደት አመቻች ኮሚቴውን ማፍረሳቸው ሰላማዊ ታጋዮች አንገት የሚያስደፋ ነው» ያሉት በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው የፖለቲካ ተንታኝ የኢንጂነሩን ዉሳኔ የሚረዳዉና የሚጠቅመው አገዛዙን ብቻ እንደሆነም ይናገራሉ።
ከኢንጂነር ገዛቸው አመራር ጋር በተገናኝም በዉጭ አገር የሚኖሩ የአንድነት ደጋፊዎች በኢንጂነር ግዛቸው አመራር ላይ ያላቸውም ከፍተኛ ተቃዉሞ እየገለጹ መሆናቸውን ለመረዳት ችለናል።