Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Saturday, January 10, 2015

"ፕሬዘዳንት የመምረጥ መብት የአንድነት የጠቅላላ ጉባኤ አባላት ሆኖ እያለ የምርጫ ቦርድ እኔ ፕሬዘዳንት ካልመረጥኩላችሁ እያለ ነው"(ከአንድነት የተሰጠ መግለጫ)

ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ መግለጫ
***********************************************************************

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ትግሉን በቁርጠንነት በመምራት የሚያደርገውን ጠንካራ እንቅስቃሴ ተከትሎ ፓርቲውን ከፖለቲካው ምህዳር የማጥፋት ዘመቻው ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ፓርቲያችንን ወደ ኋላ ለመመለስ ከህግ አግባብ ውጭ የተሰጠውን ስልጣን ካላግባብ በመጠቀምና ለገዥው ፓርቲ በመወገን እየሰራ ያለው ምርጫ ቦርድ መሆኑ ደግሞ እንደ ፓርቲ ብቻ ሳይሆን እንደዜጋ እንድንሸማቀቅ አድርጎናል፡፡
በ2007 ዓ.ም የሚካሄደውን ሀገር አቀፍ ምርጫ ተከትሎ ጠንካራ ፓርቲዎችን ከውድድር የማስወጣት ሃላፊነት ወስዶ እየተንቀሳቀሰ ያለው ይሄው የምርጫ ቦርድ አሁንም በታሪክና በህዝብ ዘንድ የሚያስጠይቀውን ተግባር አይኑን ጨፍኖ እየተገበረ ይገኛል፡፡ በተለይም በፓርቲያችን ላይ የያዘው የማፍረስ አቋም የቦርዱን ለህወሃት/ኢህአዴግ አሸርጋጅነትና አንጋሽነት ያጋለጠ ሆኖ አግንተነዋል፡፡
ቦርዱን እንደተቋም ቆጥረን ባደረግናቸው የደብዳቤ ልውውጦች አማካኝነት የጉባኤ ኮረም ቁጥር እንዲሟላ በመጠየቁ ታህሳስ ሦስትና አራት ቀን 2007 ዓ.ም የቦርዱ ተወካይ በተገኘበት የደመቀና ህጉን የጠበቀ ጉባኤ ማድረጋችን ይታወቃል፡፡ ሆኖም ግን አንድነት ወደ ምርጫ እንዳይገባ የፖለቲካ ውሳኔ በመወሰኑና ቦርዱም እጁ የተጠመዘዘ ተቋም በመሆኑ ጉባኤውን ውድቅ የሚያደርግበት ሰበብ ፈልጎ ታህሳስ 28 ቀን 2007 ዓ.ም በፃፈው ደብዳቤ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባዔ እንዲጠራ ጠየቀ፡፡ የሚገርመው መጠየቅ ብቻ ሳይሆን በ4 ቀን ውስጥ እንዲካሄድ ማለቱ ነው፡፡
የአንድነት አባላት በቦርዱ አድሎአዊ አሰራር በመቆጣታቸው ለዳግም ጉባኤው እንደሚገኙ በማረጋገጣቸው ለእሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም ዝግጅት እየተደረገ ይገኛል፡፡ ነገር ግን ቦርዱ የፈለገው አንድነት በሚስጥር ድምፅ አሰጣጥ ፕሬዘዳንት መምረጡን አይደለም፡፡ ቦርዱ የፈለገው አሳፋሪ በሆነ መንገድ ፕሬዘዳንት የመምረጥ መብት የአንድነት የጠቅላላ ጉባኤ አባላት ሆኖ እያለ ቦርዱ እኔ ፕሬዘዳንት ካልመረጥኩላችሁ እያለ ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር በጎንዮሽ አሻንጉሊት የሆነ አንድነት በመፍጠር ገዥው ፓርቲ ለብቻው የሚሮጥበት ሜዳ ማበጀት ነው፡፡
ይሄው ቦርድ አስቸኳይ ጉባዔ እንድንጠራ አዝዞ እያለ በጎን ከተለጠፊና አንድነት ከማያውቃቸው ግለሰቦች ጋር በመሞዳሞድ ተወካይ አልክም የሚል ድፍረት ላይ መድረሱ አሁንም የውንብድና ስራ እየሰራ መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡ በተጨማሪም የቦርዱ ም/ሰብሳቢ የሆነው አቶ አዲሱ ገ/እግዚአብሄር የተባለው ግለሰብ በሬድዮ ፋና በመቅረብ ታዛቢ እንዲልኩ በደብዳቤ ጠይቀናቸውና ፈርመው ተቀብለው እያለ ይህንን በመካድ ምንም አይነት ጥያቄ አልደረሰንም የሚለው ቅጥፈታቸው በታሪክም በህግም ተጠያቂ ያደርጋቸዋል፡፡
አሁንም ፓርቲያችን የተጠመዘዘው የምርጫ ቦርድ ሃላፊነቱን ይወጣል የሚል እምነት ባይኖረውም ቢያንስ ከአፍራሽነት ሚናው እንዲታቀብ እንመክራለን፡፡ ፓርቲያችንን ከሰላማዊ ትግል መንገድ ለማስወጣት እያደረገ ያለውን ሃላፊነት የማይሰማው አሳፋሪ ተግባር አቁሞ ሃላፊነቱን ለመወጣት ትንሽ እንዲሞክር እንጠይቃለን፡፡ ፓርቲያችን ህገወጥነትን ከህዝቡ ጋር በመሆን አምርሮ እንደሚታገለውና አሸናፊም እንደሚሆን ለህዝባችን ቃል እንገባለን፡፡
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
ድል የሕዝብ ነው
ጥር 2 ቀን 2ዐዐ7 ዓም
አዲስ አበባ


10153833_587630041337455_4078181881316786241_n

No comments:

Post a Comment

wanted officials