የትውልድ ቦታው አሶሳ አከባቢ የሆነ የፌዴራል ፖሊስ አባል ሌሎች ሶስት የፌዴራል ፖሊስ አባላትን እና አንድ ቻይናዊን በምዕራብ ሀረርጌ ሚኤሶ ወረዳ ልዩ ስሙ ቦርደዴ በተባለ ቦታ
በጥይት ተኩሶ ከገደላቸዉ በሃላ መሰወሩን የአካባቢው ምንጮች ገልጸዋል::
የፌደራል ፖሊሶችና የኦሮምያ ፖሊስ ገዳዩን ለመያዝ በጭሮ፣ ሚኤሶ፣ በዴሳ፣ ገለምሶና አዋሽ ከተሞች ቤት ለቤት እየገቡ ፍተሻ በማካሄድ ላይ ናቸው።
ፖሊሶቹ ለሰበተ-ሚኤሶ ባቡር ስራ ቻይናዎችን እንዲጠብቁ የተመደቡ ናቸው። ቻይናዊው ሰራተኛና ሶስቱ ፖሊሶች ህዝቡን በተለይም የቀን ሰራተኞችን ያለ ክፍያ የሚያሰሩ እንዲሁም ለባቡሩ ካሳ ያልተከፈለበት እርሻን አስገድደዉ መንገድ እንዲሰራ እንደሚያደርጉ ነዋሪዎች ይናገራሉ። ገዳዩ ፖሊስ ድርጊቱን ሲቃወም በመቆየቱ በአካባቢው ህዝብ ዘንድ ተወዳጅ መሆኑንና ያለመያዙም ሚስጢር ከህዝብ መጠለያ በማግኘቱ መሆኑን ነዋሪዎች ገልጸዋል።
ድርጊቱ ከተፈጸመ በሁዋላ የባቡር ስራው መቆሙን ምንጮች ገልጸዋል። ኢሳት ቻይናውያን ሰራተኞች ስለሚፈጽሙት በደል ተደጋጋሚ አቤቱታዎች ሲደርሱት ቆይቷል። በጉዳዩ ዙሪያ የመንግስትን አስተያየት ለማካተት የተደረገው ጥረት አልተሳካም። የቻይናዊውን ግድያ በተመለከተም መንግስት እስካሁን የሰጠው ይፋዊ መግለጫ የለም።