በእነ ሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ቀርቦባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት የዞን ዘጠኝ ጦማርያን እና ሶስቱ ጋዜጠኞች የቀረበባቸውን ክስ መከላከል ያስፈልጋቸዋል ወይስ በነጻ ይሰናበቱ የሚለው ላይ ብይን ለመስጠት ለሐምሌ 13/2007 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡
ዛሬ ሰኔ 8/2007 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ልደታ ምድብ የቀረቡት ጦማርያኑና ጋዜጠኞቹ ጥቁር ለብሰው ችሎት ፊት ቀርበዋል፡፡ መዝገቡ ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው አቃቤ ህግ በአንደኛ ተከሳሽ ላይ የሲ.ዲ ዶክሜንተሪ ማስረጃ ማቅረቡን ተከትሎ ፍርድ ቤቱ በጽ/ቤት አይቶ ሲ.ዲው በግልጽ ችሎት ይታይ ወይስ በዝግ የሚለውን ብይን ለመስጠት ነበር፡፡
በዚህም ፍርድ ቤቱ ሲ.ዲው በችሎት መታየቱን ተገቢ ሆኖ ስላላገኘነው በሚል ዳኞች ብቻ ተመልከተውት በማስረጃነት እንዲያዝ ተደርጓል፡፡ ይህን ተከትሎ ተከሳሾች በብይኑ ላይ አለን ያሉትን አቤቱታ በጠበቆቻቸው አማካኝነት ያሰሙ ሲሆን፣ ፍርድ ቤቱ ግን ብይን ባገኘ ጉዳይ ላይ አቤታቱውን ከመመዝገብ ውጭ ለውጥ እንደማይኖረው ገልጹዋል፡፡
በመሆኑም ፍርድ ቤቱ ሐምሌ 13/2007 ዓ.ም ተከሳሾች አቃቤ ህግ ያቀረበባቸውን ክስ ይከላከሉ ወይስ በነጻ ይሰናበቱ በሚለው ጉዳይ ላይ ብይን ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡