Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Saturday, January 21, 2017

የ24 ዓመቷ ወጣት ንግስት ይርጋ ከአርበኞች ግንቦት 7 ተልእኮ ትቀበል ነበር የሚል ክስ ተመሰረተባት | የክሱን ቻርጅ በPDF ይዘናል



እነ ንግስት ይርጋ የቀረበባቸው ክስ ተነበበላቸው
እነ ንግስት ይርጋ ( ስድስት ሰዎች) በማእከላዊ ለአራት ወራት ጊዜ ከቆዩ በኋላ አቃቤ ህግ ክስ ታህሳስ 28 ቀን 2009 የሽብር ክስ መስርቶባቸዋል። የዛሬ ቀጠሮ የነበረው ክሱ በችሎት እንዲነበብላቸው ሲሆን የቀረበባቸው 18 ገፅ ክስ ተነቦላቸዋል። በሁሉም ተከሳሾች ላይ የቀረበው ክስ አንድ ሲሆን፤ በ1996 ዓም የወጣውን የወንጀል ህግ አንቀፅ 32[1] (ሀ) እና (ለ)፣ አንቀፅ 38 እና በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀፅ 3 (4) እና (6) ስር የተመለከተውን በመተላለፍ የተመሰረተ ክስ ነው። አርበኞች ግንቦት ሰባት ከተባለ ሽብርተኛ ቡድን ተልእኮ በመቀበል እና የሽብር ቡድኑ አባል በመሆን ሃገር ውስጥ ካሉ አባሎች እና አመራሮች እንዲሁም ውጪ ሃገር ከሚገኙ አባል እና አመራሮች ጋር በመፍጠር በስልክ እና በድህረ ገፅ ግንኙነት በመፍጠር በአማራ ክልል በተለያዩ ዞኖች እና ከተሞች አመፅ በመምራት፤ በአዲስ አበባ የሽብር ጥቃቶች እንዲፈፀሙ ሲንቀሳቀሱ እንደነበር ክሱ ይገልፃል።
በተጨማሪም ተከሳሾቹ መተማ ዙሪያ ባስነሱት አመፅ በመኖሪያ ቤት፣ በድርጅት፣ በመንግስትና በግለሰብ ተሽከርካሪዎች ላይ ጉዳት በማድረስ ከ95,986,433 (ዘጠና አምስት ሚሊዮን ዘጠኝ መቶ ሰማኒያ ስድስት ሺህ አራት መቶ ሰላሳ ሶስት) ብር በላይ ንብረት ላይ ጉዳት እንዲደርስ፣ በጎንደር ከተማ በሚገኙ ቀበሌዎች በመንግስት እና በህዝብ ተቋም ተሽከርካሪዎች ላይ ከ10,679,945 (አስር ሚሊዮን ስድስት መቶ ሰባ ዘጠኝ ሺህ ዘጠኝ መቶ አርባምስት) ብር በላይ ንብረት ላይ ጉዳት እንዲደርስ እንዲሁም በምእራብ ጎጃም በሚገኙ ከተሞች ከ95, 345, 363 (ዘጠና አምስት ሚሊዮን ሶስት መቶ አርባ አምስት ሺህ ሶስት መቶ ስልሳ ሶስት) ብር በላይ የሚገመት ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዲደርስ ማድረጋቸው በክሱ ተካቷል።
ክሱ ከተነበበላቸው በኋላ ተከሳሾች መቃወሚያ እንዳላቸው ተጠይቀው ፤ የ1ኛ ተከሳሽ ጠበቃ (አቶ ሄኖክ አክሊሉ) እና የ4ኛ ተከሳሽ ጠበቃ እንዳላቸው የክስ መቃወሚያ እንዳላቸው ተናግረዋል። የተቀሩት ተከሳሾችም ጠበቃቸው በዛሬው እለት ባይገኙም በክሱ ላይ ተቃውሞ እንዳላቸው እራሳቸው ተናግረዋል። ጠበቃቸው በዛሬው እለት ያልተገኙ ተከሳሾች ጠበቃቸው የሚመቻቸው ጥር 23 እንደሆነ እና ቀጠሮው በዛ ቀን እንዲሆንላቸው ዳኞችን ጠይቀዋል።
ተከሳሾቹ የቀረበባቸውን ክስ በአግባቡ መከራከር እንደሚፈልጉ ገልፀው ይህን ለማድረግ ግን ህገ መንግስቱ፣ ወንጀለ መቅጫ፣ ፀረ ሽብር አዋጅ እና ሌሎች አዋጆች ማረሚያ ቤት እንዲገቡላቸው እንዲፈቀድላቸው ጠይቀዋል። ዳኞችም ህጎቹን እና አዋጆቹን ማረሚያ ቤቱን እንዲጠይቁ ነግረዋቸዋል። ተከሳሾቹም ማረሚያ ቤቱ ከወረቀት እና ከእስክብሪቶ አቅም እንኳን ማግኘት እንደሚከለከሉ በመናገራቸው፤ በሚቀጥለው ቀጠሮ ከጠበቃዎቻቸው ጋር ተነጋግረው ይህን አቤቱታቸውን በፅሁፍ እንዲያቀርቡ ተነግሯቸዋል።
በክሱ ላይ ያላቸውን መቃወሚያ በፅሁፍ ለመቀበል ለጥር 23, 2009 ቀጠሮ ተሰጥቷል።
በእነ ንግስት ይርጋ መዝገብ ክስ የተመሰረተባቸው ተከሳሾች የሚከተሉት ናቸው።
1ኛ ንግስት ይርጋ ተፈራ ( እድሜ 24, ሰሜን ጎንደር)
2ኛ አለምነህ ዋሴ ገ/ማርያም ( እድሜ 57, ሰሜን ጎንደር)
3ኛ ቴዎድሮስ ተላይ ቆሜ ( እድሜ 18, ሰሜን ጎንደር)
4ኛ አወቀ አባተ ገበየሁ ( እድሜ 31, አዲስ አበባ)
5ኛ በላይነህ አለምነህ አበጀ ( እድሜ 29, ባህር ዳር)
6ኛ ያሬድ ግርማ ሃይሌ ( እድሜ 46, አዲስ አበባ)
የክሱ ዝርዝር የሚከተለውን ሊንክ በመጫን ማግኘት ይቻላል፡፡ የክሱ ቻርጅ በPDF

ምንጭ: የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ፕሮጀክት

No comments:

Post a Comment

wanted officials