Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, January 5, 2017

በባህርዳር ወህኒ ቤት 4 ሰዎች ሲገደሉ ሌላ አንድ ነጋዴ ደግሞ ኮማንድ ፖስት ነን ባሉ ታጣቂዎች ተገደለ


አርበኞች ግንቦት 7ትን ለመቀላቀል ወደ በረሃ ሲወርዱ ከተያዙት 6 ሰዎች መካከል 4ቱ መገደላቸውን የማረሚያ ቤቱ ምንጮች ለኢሳት ገልጸዋል።

በአዲስ ቅዳም ወረዳ በሚገኘው መሰናዶ ትምህርት ቤት ያስተምር የነበረው መምህር አሸናፊ ሸዋረጋው፣ 7 ሆነው ወደ በረሃ በመጓዝ ላይ እያሉ፣ ከመካከላቸው አንዱ የደህንነት አባል በመሆን ጠቁሞ ካስያዛቸው በሁዋላ፣ በባህርዳር እስር ቤት ለወራት ታስረው ቆይተዋል።
ይሁን እንጅ ከታሰሩት መካከል መምህር አሸናፊን ጨምሮ ሌሎች 4 እስረኞች፣ ጠዋት ላይ ቁርስ በልተው ስፖርት በመስራት ላይ እያሉ ለየብቻ እየተጠሩ መርፌ መወጋታቸውን፣ ከዚህ በሁዋላ ሁሉም ህይወታቸውን ማለፉን ምንጮች ገልጸዋል። ምን አይነት መርፌ እንደተወጉ ግን የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ተናግረዋል። በጉዳዩ ላይ የአንደኛውን ሟች አባት ለማነጋገር የሞከርን ቢሆንም፣ ሀዘን ላይ በመሆናቸው ምንም ማለት እንደማይፈልጉ በከፍተኛ የሀዘን ስሜት ውስጥ ሆነው ተናግረዋል።
4 ቱም ሟቾች በሙሉ ጤንነት ላይ የሚገኙ ጓደኛሞች ነበሩ። የሟቾች ወላጆች ተጠርተው አስከሬን እንዲወስዱ ተደርጓል።
የመምህር አሸናፊ የቀብር ስነስርዓት በአዲስ ዘመን ዛሬ ተፈጽሟል።
በሌሎች እስረኞች ላይም ተመሳሳይ የግድያ እርምጃ ይወሰዳል የሚል መረጃ መሰራጨቱን ተከትሎ እስር ቤቱ ውስጥ ከፍተኛ ጭንቀት ተፈጥሯል። በጉዳዩ ዙሪያ የወህኒ ቤቱን ሃላፊ ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።
አሁንም ከግድያ ዜና ሳንወጣ በዚሁ ከተማ ትናንት ሰኞ ከምሽቱ 4 ሰአት ላይ የኮማንድ ፖስቱ አባላት ነን ያሉ ታጣቂዎች አንድ ነጋዴ ገድለዋል።
ምንጮች እንደሚሉት “የኮማንድ ፖስቱ አባላት ነን ያሉ ታጣቂዎች በምሽት በዘይት ነጋዴነታቸው የሚታወቁት የአህመድ ወሎ ልጅ ወደ ሆነው እስማኤል አህመድ ቤት በማምራት አህመድን እንደሚፈልጉት ይገልጻሉ። አህመድ ስግደት ላይ የነበረ ሲሆን፣ እሱ ስግደቱን እስኪጨርስ የቤተሰቡ አባላት ወደ አንድ ክፍል እንዲገቡ አድርገው ቤቱን በረበሩ።
አህመድ ስግደቱን ሲጨርስ “ ለምን ፈለጋችሁን?” በማለት ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን፣ ታጣቂዎችም “ ሽፍታ ደብቀሃል” በማለት መልሰውለታል። እሱም “ያስጠጋሁት ሽፍታ የለም፣ ብር ከሆነ የምትፈልጉት ልስጣችሁ” ሲላቸው ፣ ገንዘብ አንፍልግም በማለት “ በጥይት ደብድበው ጥለውት ሄደዋል።”
የእስማኤል የቀብር ስነስርዓት ዛሬ ማክሰኞ ጠዋት ተፈጽሟል። በቀብር ስነስርዓቱ ላይ ወጣቶች ተቃውሞአቸውን ገልጸዋል።
እስማኤል ባለትዳርና የአራት ልጆች አባት ነበር።
ምንጮች እንደሚሉት ገዳዮቹ 3ቱ ፖሊሶች መደበኛ የፖሊስ ልብስ የለበሱና መልካቸው እንዳይታይ ጭምብል ያጠለቁ ናቸው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በባህር ዳር ከተማ በተለያዩ ጊዜያት እየታፈኑ በመወሰድ ስቃይ ሲደርስባቸው የነበሩ ወጣቶች እንደሚናገሩት አገዛዙ ኮማንድ ፖስት በሚለው ወታደራዊ እዙ አማካኝነት በተለያዩ ህዝባዊ ስብሰባዎችና ስፖርት ሜዳ ላይ መንግስትን የሚቃወም ንግግር አድርጋችኋል በሚል ሰበብ ወጣቶችን በየቀኑ በማፈስ ወደ ማይታወቅ ቦታ በመውሰድ ስቃይ እየፈጸመባቸው ነው።
ባሳለፍነው ዕሁድ በባህርዳር ከተማ አጼ ቴዎድሮስ ስታዲየም በተደረገው የእግር ኳስ ጨዋታ ላይ የባህር ዳር ከነማንና የአማራ ክልል ውሃ ስራዎች ቡድንን ለመደገፍ የተገኙ ወጣቶችን “ገዥውን መንግስት የሚቃወም ዘፈን ዘፍናችኋል!” በሚል ከአስር በላይ ወጣቶችን በሁለት ቀናት ውስጥ አፍነው ወስደዋል፡፡
በእግር ኳስ ጨዋታው ጊዜ በድምጽ ማጉያ ይቀርብ በነበረው የአማራ ፖሊስ ኦርኬስትራ ድምጻዊ የተቀነቀነውን “ተው አትፈትነኝ ” በሚለው ክሊፕ ሁሉም ወጣቶች የወልቃይትን ጉዳይ በማንሳት በጩኸት ሲያቀነቅኑ እንደነበር የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡የታፈሱት ወጣቶች አሁን ያሉበት ቦታም ሆነ ሁኔታ አለመታወቁ በወላጆቻቸው ላይ ትልቅ ጭንቀት ፈጥሯል፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials