ብስራት አማረ ከቤተመንግስት ዘርፎ የወሰደው የጃንሆይ ወርቅ ከአገር ያወጣው አቶ መለስ ዜናዊ በተሳፈሩበት አውሮፕላን እንደነበረ አንድ ከፍተኛ የደህንነት ምንጭ አጋለጠ። በአሜሪካ ኦሀይ ግዛት የሚኖረው የቀድሞ የሕወሐት አባልና የደህንነት ሹም ብስራት አማረ ከቤተመንግስት ከዘረፈው የጃንሆይ ወርቅ ጋር በተያያዘ እንዲታሰር መደረጉን ያስታወሰው ምንጩ ይህን ውሳኔ ያስተላለፉት ጥቂት የፓርቲው አመራሮች መሆናቸውን ጠቁሟል። ብስራት በሆለታ እስር ቤት እንዲታሰር ቢደረግም ወርቁን ግን አሳልፎ እንዳልሰጠና ግልፅ ባልሆነ ሁኔታ ከእስር ተፈቶ ወደ አሜሪካ ማምራቱን ያመለከተው ምንጩ በሚሊዮን የሚገመት ዶላር የሚያወጣው ታሪካዊ ወርቅ አቶ መለስ ዜናዊ በተሳፈሩበት አውሮፕላን ተጭኖ አሜሪካ መግባቱንና ብስራት አማረ እንደተረከበ ጉዳዩን በቅርብ የሚያውቀው ምንጭ አጋልጧል። ብስራት አማረ በዚህ ወርቅ እራሱንና ቤተሰቡን ሚሊየነር ያደረገ ከመሆኑም ባሻገር የደህንነት አባል የነበረው ታናሽ ወንድሙ ጠስሚ (ቅቤ ማለት ነው ትርጉሙ) በአገር ውስጥ ከፍተኛ ንግድ ከሚያንቀሳቅሱ ሃብታሞች አንዱ መሆን እንደቻለ ሲታወቅ ብስራት በአሜሪካ ለምትኖር አንዲት ኢትዮጵያዊ እንድትሸጥለት የሰጣትን 1ኪሎ ወርቅ ወስዳ እንደካደችው ከዚህ ቀደም መገለፁ ይታወሳል። ባለፈው አመት ከቦሌ አየር ማረፊያ እንዲመለስ የተደረገው ብስራት ለቪ.ኦ.ኤ ሲናገር « መለስ በመሞቱ እንዲህ አይነት ችግር ተፈጠረብኝ» ማለቱ ይታወሳል። ሕወሐት በረሃ እያለ የፈፀማቸው ግድያዎችና አሰቃቂ ግፎች በዋነኛነት ይመራና ይፈፅም የነበረው ብስራት አማረ ሲሆን በተለይ ወረኢ በተባለ ቦታ በነበረው ባዶ 6 የማሰቃያ እስር ቤት ውስጥ የኢህአፓ አመራር አባላት የነበሩት እነፀጋዬ ገ/መድህንና ሌሎቹ በብስራት እንደተጨፈጨፉ ከመረጋገጡ ባሻገር ይህን የሚያውቁ የፓርቲው ሰዎች በወንጀለኛው ላይ ለመመስከር ፈቃደኛ መሆናቸውን በመጥቀስ መረጃውን ከዚህ ቀደም ይፋ እንደተደረገ ይታወሳል። ሆኖም ወንጀለኛውን ለመፋረድ የሞከረ አካል የለም።
እየሩሳሌም አርአያ