Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Saturday, February 14, 2015

እንዳይጎበኝ ክልከላ የተደረገበት የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ወላጅ እናት አቤቱታ አቀረቡ


የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ወላጅ እናት አቤቱታ አቀረቡ






ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ

‹‹መርማሪ ተመድቦ ጉዳዩ እየተጣራ ነው›› የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን

የፍትሕ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሆኖ ሲሠራ በጋዜጣው የተለያዩ ዕትሞች ላይ በወጡ በራሱና ከአንባብያን በተላኩ መጣጥፎች ምክንያት የወንጀል ክስ ተመሥርቶበት፣ የሦስት ዓመታት እስር የተወሰነበት ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ወላጅ እናት፣ ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን አቤቱታ አቀረቡ፡፡


ጋዜጠኛ ተመስገን ጥፋተኛ በተባለበት የወንጀል ክስ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 16ኛ ወንጀል ችሎት የሦስት ዓመት የእስር ቅጣት ውሳኔ ከተላለፈበት በኋላ፣ በፌዴራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ዝዋይ ማረሚያ ቤት በእስር ላይ ይገኛል፡፡ በመሆኑም እናቱን ጨምሮ ወንድሙ፣ ጓደኞቹና ወዳጆቹ እየጠየቁት የነበረ ቢሆንም፣ ካለፉት 30 ቀናት ወዲህ ግን ማንም እንዳይጠይቀው መከልከሉንና በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ማወቅ እንዳልቻሉ፣ እናቱ ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው ለኮሚሽኑ፣ በግልባጭም ለሚመለከታቸው የመንግሥት ተቋማትና ለውጭ ኤምባሲዎች በጻፉት ደብዳቤ አሳውቀዋል፡፡

ወ/ሮ ፋናዬ የካቲት 2 ቀን 2007 ዓ.ም. ዋናውን ለሰብዓዊ መብት ኮሚሽን፣ በግልባጭ ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት፣ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለሕግና ፍትሕ አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴና ለአፈ ጉባዔ ጽሕፈት ቤት፣ ለእንባ ጠባቂ ተቋም፣ ለአሜሪካና ለእንግሊዝ ኤምባሲዎች በጻፉት ደብዳቤ እንደገለጹት፣ ልጃቸውን ጋዜጠኛ ተመስገንን ካዩት (ድምፁን ከሰሙ) አንድ ወር አልፏቸዋል፡፡ ታናሽ ወንድሙ ታሪኩ ደሳለኝ ምግብ ይዞለት ዝዋይ ማረሚያ ቤት የሄደ ቢሆንም፣ በማረሚያ ቤቱ ጠባቂዎች ድብደባ ደርሶበትና ምግቡም ሜዳ ላይ ተደፍቶ ተመልሷል ብለዋል፡፡ ልጃቸው በቤተሰቦቹ፣ በጓደኞቹና በወዳጆቹ እንዳይጎበኝ ለምን እንደተከለከለ እንዲነገራቸውና ሰብዓዊ መብቱ ተጠብቆ እንደማንኛውም ታራሚ በነፃነት እንዲጎበኝ እንዲያደርጉላቸው፣ የሚመለከታቸውን የመንግሥት ተቋማትና የሁለቱን አገሮች አምባሳደሮች በደብዳቤያቸው ተማፅነዋል፡፡

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ለምን እንዳይጠየቅ (እንዳይጎበኝ) ክልከላ እንደተደረገበት ማብራሪያ ለማግኘት የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ኃላፊዎችን ለማግኘት ተደጋጋሚ ጥረት ቢደረግም፣ አመራሮች በሥልጠና ላይ መሆናቸውን ከመግለጽ ባለፈ ማብራሪያ የሚሰጡ ማግኘት አልተቻለም፡፡

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ስለአቤቱታው ተጠይቆ፣ የጋዜጠኛ ተመስገን እናት የጻፉት የመማፀኛ ደብዳቤ እንደደደረሰው አረጋግጧል፡፡ መርማሪ መድቦ ጉዳዩን ማጣራት እንደጀመረም የኮሚሽኑ የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ብርሃኑ አባዲ አስረድተዋል፡፡

Source:: Ethiopian Reporter

No comments:

Post a Comment

wanted officials