Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Saturday, February 14, 2015

ድንገተኛና ደማቅ የፊኛ መልቀቅ ተቃውሞ በአንዋር መስጊድ ተካሄደ






‹‹ሲፈልግ ሾማቸው ሲፈልግ ሻራቸው!!››
አርብ የካቲት 6/2007
ድምጻችን ይሰማ እንደዘገበው:-

የመንግስት እጆች ዛሬም በመጅሊስ ውስጥ እንደተዘፈቁ ያረጋገጠውን በቅርቡ የተካሄደውን ህገወጥ የመጅሊስ ሹማምንት ሹም ሽር በመቃወም ደማቅ ድንገተኛ ተቃውሞ በአዲስ አበባ በታላቁ አንዋር መስጊድ ተካሄደ፡፡ ተቃውሞው ‹‹ሲፈልግ ሾማቸው ሲፈልግ ሻራቸው!›› በሚል መሪ ቃል የተካሄደ ነበር፡፡ ህብረተሰቡ የተለያዩ ቀለማት ያላቸው ፊኛዎችን እና መፈክሮችን በመጠቀም መሪ ቃሉን በደማቅ ሁኔታ አንፀባርቋል፡፡ ተቃውሞው በወኪሎቻችን አማካኝነት ለመንግስት ያቀረብነው የ‹‹ነፃ መጅሊስ›› ጥያቄ ዛሬም ህያው የማታገያ አጀንዳ እንደሆነና ከወኪሎቻችን ጋርም እስከ ድል አብረን እንደምንቀጥል ትልቅ መልዕክት ያስተላለፈ ነው፡፡


በከፍተኛ መስዋእትነት በወታደራዊው ደርግ ዘመን ያገኘነው ተቋማዊ መብታችንን (መጅሊስን) በኢህአዴግ መንግስት ከተነጠቅን ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ በይበልጥም የሃይማኖት መሪዎችን ምርጫ ‹‹በቀበሌዬ ካልሆነ አይሞከርም›› በሚል አይን ያወጣ ጣልቃ ገብነት ካድሬዎችን የሾመበት አጋጣሚ ‹‹መንግስት በመጅሊስ ውስጥ ጣልቃ ገባ›› የሚያስብል ከመሆንም አልፎ ህዝብ ትንሽም ቢሆን በተቋሙ ጉዳይ ጣልቃ እንዳይገባ በሩን የዘጋበት ታሪካዊ ሁነት ነበር፡፡ በቅርቡ ደግሞ ሲፈልግ ከያሉበት ጠርቶ በፖለቲካዊ ስሌት የሾማቸውን የመጅሊስ ህገወጥ ሹማምንት አንድ የቀበሌ አስተዳዳሪ ከመቀየር ባልከበደ ሁኔታ ሲሽራቸው ከርሟል፡፡ የሹም ሽሩ ድራማ በደም የተገኘውን መጅሊሳችንን ክብር ያጎደፈ፣ መንግስት ዛሬም ከመጅሊስ ለመውጣት ትንሽም ፍላጎት እንደሌለው ያሳየ፣ በመንግስት ጉያ ተሸሽገው ከህዝብ ተቃራኒ የቆሙ ወገኖች የነገ እጣ ፈንታቸው ምን ሊሆን እንደሚችል በተግባር ያሳየ፣ እንዲሁም በመጅሊስ እና በሌሎች የመንግስት የፖለቲካ መዋቅሮች ውስጥ የሚካሄዱ ሹምሽሮች ከተመሳሳይ ቦታ በተመሳሳይ ‹‹ህግ›› የሚከናወኑ መሆኑን ከምንግዜውም በላይ በተግባር ያሳየ ነበር፡፡

ህዝበ ሙስሊሙ ተቋሙን ዛሬ ላይ እጁን ተጠምዝዞ ተቀምቶ ህገ ወጦች እንዲፈራረቁበት ቢደረግም በተቋሙ ላይ ያለው የባለቤትነት ስሜት ግን አሁንም ህያው ነው፡፡ የጀመረውን ሰላማዊ ትግል ዳር ሲያደርስ መጅሊስን እውነተኛ የህዝብ ተቋም እንዲሆን አድርጎ ነፃ ማውጣትም ትልቁ ግቡ ነው፡፡ መንግስት እያካሄደ ያለው ሹምሽር ህገ ወጦችን በህገ ወጦች መተካት በመሆኑ በራሱ ህገወጥነት ነው፡፡ ህዝቡም ተግባራዊ ምላሽ መስጠትን ጨምሮ ጉዳዩን በዝምታ እንደማያልፈው መግለፁ ይታወሳል፡፡ የዚህ ህዝባዊ ምላሽ አንድ አካል የሆነው የዛሬው የጁሙዓ መርሃ ግብር በተሳካ መልኩ ተከናውኗል፤ አልሐምዱሊላህ!!!

ትግላችን እስከድል ደጃፎች በአላህ ፈቃድ ይቀጥላል!
ድምጻችን ይሰማ!

No comments:

Post a Comment

wanted officials