አቶ ተስፋዬ ብሩ (ኋላ ዶ/ር) የደረሰባቸው ግፍና ስቃይ እጅግ አሳዛኝ ነው። ጉዳዩ እንዲህ ነው፤ ተስፋዬ የቴሌ ስራ አስኪያጅ ሆነው የተመደቡት በ1995ዓ.ም ነበር። አንድ በቴሌ የሚሰራ ኢንጂነር ወዳጄ በወቅቱ « ተስፋዬ ብሩ እውቀትና ብቃት አለው። ግን አያሰሩትም» ያለኝን በኢትኦጵ ጋዜጣ በወቅቱ አስፍሬው ነበር። እርሳቸው ከመሾማቸው በፊት ቴሌን በአዜብ መስፍን “አዝማችነት” ኢያሱ በርሄን ጨምሮ 38 ግልሰቦች ለ7 አመት በደንብ አድርገው ገሽልጠውታል። በቁጥጥር ስር ቢውሉም ወዲያው አዜብ አስፈታቻቸው። የቴሌ አመራሮችም በቦሌ ተሸኙ። ድርጅቱን የተረከቡት ተስፋዬ ብሩ በአግባቡ ማስተዳደር ቀጠሉ። በ1998 ዓ.ም “ሪፖርተር” ጋዜጣ 20ኛ አመቱን ለማክበር ሲል ቴሌን የ250ሺህ ብር ስፖንሰር እንዲሆነው ይጠይቃል። ሃላፊውም “አይሆንም” ሲሉ ይመልሳሉ። አማረ አረጋዊ በተስፋዬ ብሩ ላይ አከታትሎ ዘመቻ ይከፍታል። በዛው አመት ከስልጣን ተነስተው የጠ/ሚ/ሩ አማካሪ ተደርገው ይሾማሉ። ከዚያም ወደ ውጭ ለትምህርት ይሄዳሉ። አማረ መፃፉን አላቆመም። ተስፋዬ ክስ ሲመሰረትባቸው ውጭ አገር ነበሩ። ትምህርታቸውን በማቋረጥ « እኔ የሰራሁት ወንጀል ስለሌ እሄዳለሁ» በማለት መጡ። ከቦሌ ተይዘው እስር ቤት ተወረወሩ። የሚገርመው ረቡዕ የወጣ ሪፖርተር ጋዜጣ በፊት ገፁ የተስፋዬን ፎቶ በማስፈር ሙሉ ሽፋን ሰጥቶ «ደስታውን» ገለፀ። በክሱ ላይ «ተስፋዬ ሳንቲም ሰርቀው ወሰዱ፣ ይህን ያክል ሃብት አፈሩ» የሚል ነገር በጭራሽ አልቀረበም። እነሆ ከ7 አመት ግፍና ስቃይ በኋላ ባለፈው ሳምንት ተፈቱ። እንደተስፋዬ ሁሉ የቀድሞ የፕራይቬታይዜሽን ስራ አስኪያጅ በሻህ አዝምቴ፣ የወንጂ ስኳር ብርሃኑ ጃጆ፣ አሰፋ አብርሃ፣ ኢ/ር ግዛቸው ተ/ማርያም፣ ጉልላት ጥላሁን ያለሃጢያታቸው በግፍ የተሰቃዩ ናቸው። (ስለነዚህ እመለስበታለሁ)…የሪፖርተሩ አማረ በሙስና ዙሪያ የፃፈው « ጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊ በሙስና ይጠየቁ» ሲል ስለ2 ቢሊዮን ያጋለጠበትና የግርማ ብሩ ይጠቀሳሉ። ከዛ ውጭ አባይ ፀሐዬ፣ ስብሃት ነጋ፣ አዜብና በረከት እንዲሁም የጄኔራሎችን ሙስና በተመለከተ አንስቶ አያውቅም።

(የግፍ ሰለባው ዶ/ር ተስፋዬ ብሩ እኚህ ናቸው….) እየሩሳሌም አርአያ