Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Wednesday, August 12, 2015

እነ ማቲያስ መኩሪያ ለነሃሴ 18 ተቀጠረባቸው





• አቶ ማሙሸት አማረ ለነሃሴ 20 ተቀጥሮበታል
አይ ኤስ አይ ኤስ በኢትዮጵያውያን ላይ የፈፀመውን አሰቃቂ ግድያ ለመቃወም መንግስት በጠራው ሰልፍ ሰበብ የታሰሩት እነ ማቲያስ መኩሪያ ለነሃሴ 18/2007 ዓ.ም ተቀጠረባቸው፡፡ ፖሊስ በጊዜ ቀጠሮ ወቅት ‹‹የቪዲዮ ማስረጃም አለን›› በማለቱ ተከሳሾቹ ‹‹ቪዲዮው ይቅረብልን፡፡ የቪዲዮ ማስረጃው ለእኛም የመከላከያ ምስክርነት ይጠቅመናል›› ብለው ጠይቀው የነበር በመሆኑ፤ ፍርድ ቤቱ የቪዲዮ ማስረጃው መቅረብ እንዳለበትና እንደሌለበት ብይን ለመስጠጥ ለዛሬ ነሃሴ 5/2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቶ ነበር፡፡ ይሁንና የመናገሻ ፍርድ ቤት በዛሬው ዕለት የማይሰራ በመሆኑ ችሎቱ በአራዳ ፍርድ ቤት በተረኛ ዳኛ ታይቷል፡፡ የልደታ ፍርድ ቤትም ‹‹ጉዳዩ አልተመረመረም፡፡›› በሚል ብይን ለመስጠት ለነሃሴ 18/2007 ዓ. ቀጠሮ ሰጥተዋል፡፡


ፍርድ ቤቱ ቪዲዮው ላይ ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ሲሰጥ የዛሬው ለሶስተኛ ጊዜ ሲሆን ተከሳሾቹም እየተጉላሉ መሆናቸውን ለፍርድ ቤቱ ቅሬታ አቅርበዋል፡፡ አንደኛ ተከሳሽ ማቲያስ መኩሪያ ‹‹በቪዲዮው ጉዳይ ለመወሰን ለሶስተኛ ጊዜ ሲቀጠር ነው፡፡ እኛም ቤተሰቦቻችንም እየተጉላላን ነው፡፡›› ሲል ቅሬታውን አቅርቧል፡፡ በተመሳሳይ 2ኛ ተከሳሽ መሳይ ደጉሰው ‹‹ድሃ ቤተሰብ አለን፡፡ ቤተሰቦቻችን መርዳት እንዳንችል እየተጉላላን ነው፡፡›› ብሏል፡፡ በማቲያስ መኩሪያ መዝገብ የተከሰሱት 1ኛ ማቲያስ መኩሪያ፣ 2ኛ መሳይ ደጉሰው፣ 3ኛ ብሌን መስፍን፣ 4ኛ ተዋቸው ዳምጤ ሲሆኑ ከመሳይ ደጉሰው ውጭ ያሉት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ናቸው፡፡
በተመሳሳይ በአራዳ ፍርድ ቤት የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው አቶ ማሙሸት አማረም ለነሃሴ 20/2007 ዓ.ም ተቀጥሮበታል፡፡ አቶ ማሙሸት የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት በተደጋጋሚ ፍርድ ቤት የቀረበ ሲሆን በዛሬው ዕለትም ‹‹ምስክሮቹ ስላልተሟሉና ብዙ መዝገቦችም ስላሉ ምስክርነት መስማት አልቻልንም›› በሚል ምስክሮቹ ሳይሰሙ ቀርተዋል፡፡ በተጨማሪም የአንድነት አባልና የሚሊዮኖች ድምፅ ጋዜጣ አምደኛ የነበረው እስማኤል ዳውድ አራዳ ፍርድ ቤት ቀርቦ ለነሃሴ 28/2007 ዓ.ም ተቀጥሮበታል፡፡
ፍርድ ቤቱ ‹‹በክረምት ከማይሰሩ የተለያዩ ፍርድ ቤቶች መዝገቦች በመምጣታቸው ምስክር መስማት አልቻልንም፡፡ ስራ በዝቶብናል›› በሚል በበርካታ ተከሳሾች ላይ ረዘም ያለ ቀጠሮ የሰጠ ሲሆን በተለይ በሰልፉ ሰበብ የታሰሩ ተከሳሾች በተለይም ሴቶች እና ቤተሰቦቻቸው የተፋጠነ ፍርድ ልናገኝ አልቻልንም በሚል ፍርድ ቤቱ ግቢ ውስጥ ሲያለቅሱ ተስተውለዋል፡፡
ምንጭ :-ነገረ ኢትዮጵያ

No comments:

Post a Comment

wanted officials