Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Sunday, August 9, 2015

መድረክ በህልውናው ላይ ሊወስን ነው –የተቃውሞ እንቅስቃሴ ወንጀል ሆኗል አለ

መድረክ በህልውናው ላይ ሊወስን ነው

Medrek
–የተቃውሞ እንቅስቃሴ ወንጀል ሆኗል አለ
ተቀዳሚው ተቃዋሚ ፓርቲ መድረክ ከምርጫ 2007 ጋር በተያያዘ በሺዎች የሚቆጠሩ አባሎቹ ለእስር፣ ለእንግልት፣ ለንብረት መውደም፣ እንዲሁም ለሞት እየተዳረጉ በመሆናቸው በህልውናው ላይ ለመነጋገር ልዩና አስቸኳይ ጉባዔ ጠርቶ
በመወያየት ላይ ነው፡፡ የኢትዮጵያ የሕግ ሥርዓት ለሰላማዊ ትግል ጥበቃ የሚያደርግ ቢሆንም፣ በተግባር የተቃውሞ እንቅስቃሴ እንደ ወንጀል ተቆጥሮ እያስቀጣ ነው ብሏል፡፡
ከነሐሴ 2 ቀን 2007 እስከ ነሐሴ 3 ቀን 2007 ዓ.ም. በሚቆየው ጉባዔ በአራቱም የመድረክ አባል ድርጅቶች የሚወከሉ 80 ጉባዔተኞች እንደሚካፈሉ እንደሚጠበቅ መድረክ ለሪፖርተር የላከው ጋዜጣዊ መግለጫ ይጠቁማል፡፡ ጉባዔው በ2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ምርጫ ሒደትና ከምርጫው ጋር በተያያዘ በአባላቱ፣ በደጋፊዎቹና በታዛቢዎቹ ላይ እየደረሰ ባለው የማዋከብና የማሰቃየት ተግባራት ላይ ውሳኔ እንደሚያሳልፍና ስለቀጣዩ ድርጅታዊ እንቅስቃሴ አመራር እንደሚሰጥ እንደሚጠበቅም ያክላል፡፡
የመድረክ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጥላሁን እንደሻው፣ ‹‹የጉባዔው ውሳኔ ምን እንደሚሆን መገመት አይቻልም፡፡ ሰላማዊ ትግል ማድረግ እንደምንችል ሕገ መንግሥቱን ጨምሮ የተለያዩ ሕጎች ይፈቅዳሉ፡፡ በተግባር ግን የተቃውሞ እንቅስቃሴያችን እንደ ወንጀል ተቆጥሮ እያስቀጣ ነው፡፡ በምርጫው መድረክን ምረጡ ብለው የቀሰቀሱ አባላት ሁሉ እየተቀጡ ነው፡፡ ስለዚህ መድረክ እንዴት ነው የሚቀጥለው በሚለው ላይ ጉባዔው ይመክራል፡፡ የፖለቲካ ምኅዳሩ ተዘግቷል ወይስ አለ የሚለውን ይገመግማል፡፡ አሠራሩን ለመቀየር ወይም ከነጭራሹ ይቅርብን ብሎ ሊወስንም ይችላል፤›› በማለት ጉባዔው በህልውናው ላይ ጭምር የሚወስን ቁልፍ ክስተት እንደሚሆን አስታውቀዋል፡፡
የመድረክ ጋዜጣዊ መግለጫ 1,065 ገበሬዎች ማዳበሪያ አልገዛችሁም ተብለው ከመሬታቸው መፈናቀላቸውን፣ 5,807 ነዋሪዎች ሕገወጥ ቤት ገንብታችኋል በመባል በክረምቱ ከቤት መፈናቀላቸውን ይገልጻል፡፡ አቶ ጥላሁን እነዚህ ምክንያቶች አሳማኝ እንዳልሆኑና ግለሰቦቹ ለመድረክ ከሰጡዋቸው የተለያዩ ድጋፎች በመነሳት ተጎጂ እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡ በተለያዩ ተዋረዶች ለሚገኙ የአስተዳደርና የፍትሕ አካላት ያቀረቡት አቤቱታ ምንም ዓይነት ውጤት እንዳላስገኘም አመልክተዋል፡፡
14 ወጣት የመድረክ ደጋፊዎችን በስም በመጥቀስ ለተለያዩ መንግሥታዊ መሥሪያ ቤቶች በተጻፈ ደብዳቤ ምንም ዓይነት የመንግሥት አገልግሎት እንዳያገኙና የሚያቀርቡትም ክስ ተቀባይነት እንዳይኖረው፣ በኦሮሚያ ክልል የሜታ ሮቢ ወረዳ የዋራቦ ቀበሌ አስተዳደርና ማኅበራዊ ፍርድ ቤት እንደወሰነባቸውም መግለጫው አካቷል፡፡ ሌሎች 20 የፓርቲው ደጋፊዎችም በፖለቲካ አመለካከታቸው የተነሳ ለእስርና ለገንዘብ ቅጣት መዳረጋቸውንም መግለጫው ያክላል፡፡
መድረክ ከምርጫው በኋላ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች አምስት አባላቱ መገደላቸውን ማስታወቁ አይዘነጋም፡፡ መግለጫው እነዚህን ወንጀሎች የፈጸሙ አካላት እስካሁን ለሕግ እንዳልቀረቡ ይጠቁማል፡፡ መድረክ በጉዳዩ ላይ መግለጫ ከማውጣትና ደብዳቤ ከመጻፍ ባሻገር ለሚመለከተው አካል ምርመራ እንዲደረግና ክስ እንዲመሠረት ምን እንዳደረገ ሪፖርተር ጥያቄ ያቀረበላቸው አቶ ጥላሁን፣ ‹‹የመንግሥት አካላት ጉዳዩን እየተከታተልነው ነው የሚል ምላሽ ሰጥተውናል፡፡ ዕርምጃ ተወስዶ ጥፋተኞቹ ሲያዙ አላየንም፡፡ ነገር ግን እኛም ሆንን የተጎጂዎቹ ቤተሰቦች ለተገቢው አካል አቤቱታቸውን አቅርበዋል፤›› ብለዋል፡፡ ሪፖርተር በመድረክ ውንጀላ ላይ መንግሥት አስተያየት እንዲሰጥ ለማድረግ ያደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡
መድረክ በአራት ፓርቲዎች በ2000 ዓ.ም. የተቋቋመ ሲሆን፣ በ2002 እና በ2007 ዓ.ም. በተካሄዱት ሁለት ጠቅላላ ምርጫዎች ከገዢው ፓርቲ በመቀጠል በርካታ ቁጥር ያላቸውን ዕጩዎች አቅርቧል፡፡ ባገኘውም ውጤት ከሌሎች የተቃዋሚ ፓርቲዎች ቀዳሚ ሆኖ ነበር፡፡ በዘንድሮው ምርጫ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 270፣ ለክልል ምክር ቤቶች 883 ዕጩዎችን በማቅረብ ዋናው ተወዳዳሪ ሆኖ ቀርቦ ነበር፡፡ ባለፈው ምርጫ ብቸኛው የተቃዋሚ ፓርቲ የፓርላማ አሸናፊ አቶ ግርማ ሰይፉ መድረክን ወክለው መወዳደራቸው ይታወሳል፡፡ በዘንድሮው ምርጫ ምንም ዓይነት ወንበር ባያሸንፍም፣ መድረክ ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ከተሰጠው ድምፅ ውስጥ 64.3 በመቶ የሚሆነውን አግኝቷል፡፡ መድረክ በቅርፅ ደረጃ ከኢሕአዴግ ጋር ተቀራራቢ ሲሆን ብሔር ተኮር የሆኑ ክልላዊ ፓርቲዎችን ያቀፈና ብሔር ተኮር የፌዴራል ሥርዓቱንም የማይቃወም ፓርቲ ነው፡፡
መድረክ አራት አባል ፓርቲዎች ያሉት ሲሆን እነዚህም ኦፌኮ፣ ኢሶዴ-ማዴኢአፓ፣ አረና እና ሲአን ናቸው፡፡
Source:: Ethiopian Reporter

No comments:

Post a Comment

wanted officials