Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, March 17, 2016

እየሰመጠ ካለ መርከብ ራስን የማዳኛ ጊዜ አሁን ነው! (ከአርበኞች ግንቦት 7 ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ)

እየሰመጠ ካለ መርከብ ራስን የማዳኛ ጊዜ አሁን ነው! (ከአርበኞች ግንቦት 7 ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ)

pg7-logo-1| ዛሬ መጋቢት 8 ቀን 2008 ዓ.ም የአርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ መደበኛ ስብሰባ አድርጎ በምክር ቤቱ የመጀመሪያ ጉባኤ የተላለፉትን ውሳኔዎች አፈፃፀም ገምግሞ፤ በሚቀጥሉት ሦስት ወራት ተግባራዊ ሊደረጉ የሚገባቸው ተግባራት ላይ ተነጋግሮ ውሳኔ አስተላልፏል።
በሥራ አስፈፃሚው ግምገማ መሠረት፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ የህወሓት አገዛዝ በሚያደርስበት በደል በቃኝ ካለ ቆይቷል፤ በዚህም ምክንያት ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ በሥርዓቱ ላይ እያመፀ ነው። በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በጋምቤላ፣ በደቡብ፣ በአፋር፣ በጠቅላላው በሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች ሕዝባዊ እምቢተኝነት እየተቀጣጠለ ነው። የአዲስ አበባ የታክሲ ሾፌሮችና ባለንብረቶች እንዲሁም የረዥም ርቀት አውቶቡሶች አሽከርካሪዎች ያደረጉት የሥራ ማቆም አድማ ትግሉ ከፍ ያለ ደረጃ ላይ መድረሱን የሚያረጋግጡ ናቸው።
አርበኞች ግንቦት 7፣ የህወሓት አምባገናዊ አገዛዝ በትጥቅ ትግልና በሕዝባዊ እምቢተኝነት መወገድ እና በምትኩ የኢትዮጵያ ሕዝብ በነፃነት የመረጠው መንግሥት መተካት አለበት ብሎ ያምናል። በዚህም መሠረት በትጥቅ ትግሉ ዘርፍ የሚያደርገው ተጋድሎ ከዚህ በፊት ከነበረው በተሻለ አደረጃጀት ተጠናክሮ እንዲቀጥል፤ በየቦታው እየፈነዳዳ ያለው ሕዝባዊ እምቢተኝነት ተቀናጅቶ አገራዊ እንቅስቃሴ ሆኖ እንዲወጣ የትግል አቅጣጫ ነድፎ ተግባራዊ እንዲሆን ወስኗል።
የአርበኞች ግንቦት 7 ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በስብሰባዉ መጨረሻ የሚከተሉትን ጥሪዎች አድርጓል።
1. ለአርበኞች ግንቦት 7 አባላትና ደጋፊዎች
ወሳኝ በሆነ የትግል ወቅት ላይ እንገኛለን፤ በዚህ ወቅት በትጥቅ ትግሉ በቀጥታ ተሰልፈው ያሉት አባሎቻችን፣ በአገር ውስጥ በሕዝባዊ እምቢተኝነት በመሳተፍ ላይ ያሉ አባሎቻችንና ደጋፊዎቻችን እና በውጭ አገራት የሚገኙ አባሎቻችንና ደጋፊዎቻችን ሁሉ በአንድ ልብና መንፈስ ህወሓትን ከስልጣን የማስወገድ ሥራ ላይ እንዲረባረቡ ሥራ አስፈፃሚው ጥሪ ያደርጋል።
2. ለአገር መከላከያ ሠራዊት፣ ለፓሊስና የደህንነት አባላት
ነገ ከሚወድቅ ሥርዓት ጎን ቆማችሁ ወገኖቻችሁን ማጥቃት ተው! የመሳሪያዎቻችሁ አፈሙዝ የሁላችንም ጠላት ወደሆነው አገዛዝ ይዙር! ከወያኔ በኋላ በሚመጣው ሥርዓት የመከላከያ ሠራዊትና ፓሊስ መበተን የለባቸውም ብለን እናምናለን፤ ይህ እንዲሆን ግን ዛሬ ከአምባገነን ሥርዓት ጎን ሳይሆን ከሕዝብ ጎን ቁሙ።
3. ለህወሓት፣ ብአዴን፣ ኦህዴድ፣ ደህዴግ እና የኢህአዴግ አጋር ድርጅቶች አባላት
እየሰመጠ ካለ መርከብ ራሳችሁን አውጡ! አባል የሆናችሁባቸው ድርጅቶች ለአገራችን ብቻ ሳይሆን ለእናንተም በግል የሚበጁ አይደሉም። ቢቻል በግልጽ፤ ካልተቻለም በስውር ድርጅቶቻችሁን በማዳከም የኢትዮጵያ ሕዝብ ትግልን አግዙ።
4. በኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲፈጠር ለሚታገሉ የፓለቲካና ሲቪክ ማኅበራት
በጋራ የምንቆምበት ወቅት አሁን ነው። ዛሬ የምናደርጋቸው ትብብሮች የረዥም ጊዜ ውጤት ያላቸው መሆኑን ተገንዝበን ኃይላችንን እንድናስተባብር ጥሪ እናደርጋለን።
5. ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ
ጥያቄዎቻችን አካባቢ ተኮር ሊሆኑ ይችላሉ፤ ግባችን ግን የጋራ ነው። ከህወሓት አምባገነን አገዛዝ ነፃ የወጣች ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ እንድትኖረን ሁላችንም በአንድነት እንድንቆም የአርበኞች ግንቦት 7 ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ጥሪ ያደርጋል።
አንድነት ኃይል ነው!

No comments:

Post a Comment

wanted officials