Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Sunday, March 27, 2016

የታገደችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንጂ ማኅበረ ቅዱሳን አይደለም!

የታገደችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንጂ ማኅበረ ቅዱሳን አይደለም!
 
ዐውደ ርእዩ ሲታገድ ለአንዳንዶች ማኅበረ ቅዱሳን እንደ ተከለከለ ወይም ዝግጅቱን እንዳያካሂድ እንደተሠረዘበት ሊመስላቸው ይችላል፡፡ እነዚህ ሰዎች ሁለት ዓይነት ናቸው፡፡ አንደኞቹ ዝግጅቱን ለማቅረብ ደፋ ቀና ሲል የሚያውቁት ማኅበረ ቅዱሳንን ስለኾነ ዐውደ ርእዩ ሲታገድ በቀጥታ ከማኅበሩ ጋር የሚያያይዙት ናቸው፡፡ የእነዚህ ግምት እዚህ ላይ መውደቁ በቤተ ክህነቱ እና በደጅ ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ በቅርበት ካለማወቅ እንጂ ሌላ ተንኮል የለበትም፡፡ ሁለተኞቹ ደግሞ በሰበብ አስባቡ የማኅበሩን ውድቀት ከመመኘታቸው የተነሣ ሌሊት በቅዠታቸው ሲያፈርሱት የሚያድሩት ማኅበር ሲነቁ የበለጠ አድጎና ጎልምሶ እያዩት በሌት ቅዠት በቀን ፍርሃት ውስጥ ያሉት ናቸው፡፡ ክፉዎች ናቸውና ኮሽ ባለ ቁጥር ከማኅበሩ ሕልውና ጋር አያይዘው ለማደናገር ይሮጣሉ፡፡
እባብነት የተጠናወታቸውን አጽራረ ቤተ ክርስቲያን አስተሳሰብ አሽቀንጥረን ጥለን በነፃ አዕምሮ ስናስበው እውነቱ ከማኅበሩም በላይ ያድጋል፡፡ ሥራውን በዕቅድ እንደሚሠራ ዘመናዊ ትውልድ ማኅበሩ ዕቅዱን ያቀደው አምና ነበረ፡፡ በመኾኑም ቅድመ ዝግጅቱንም የጀመረው ባስቀመጠው የጊዜ ዐቅድ መሠረት በዚያው ዓመት ነው፡፡ እናም በዓመቱ መጨረሻ ጳጉሜን ፭ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም በቁጥር 4944/8613/07 ከጠቅላይ ቤተ ክህነት የፈቃድ ደብዳቤ አስጽፎ ወደ ኤግዚቢሽን እና የገበያ ማዕከል አስገብቶ ነበር፡፡ በዚህም መሠረት የጊዜ ሰሌዳውን አስከብሮ ዐውደ ርእዩን ለማቅረብ ሲሰናዳ ከረመ፡፡
ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የጻፈውን ደብዳቤ የፈረሙት የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማቴዎስ ናቸው፡፡ ደብዳቤውም እንዲህ ይላል፡፡ ". . . ከዚህ በፊት እንደተለመደው ሁሉ አስፈላጊው ትብብር እንዲደረግላቸው በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም እየጠየቅን ለሚደረግልን መልካም ትብብርም በቅድሚያ ምስጋና እናቀርባለን፡፡"
እዚህ ደብዳቤ ውስጥ ሁለት ዐበይት ጉዳዮች ሊጤኑ ይገባቸዋል፡፡
፩. ጥያቄው የቀረበው በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም መኾኑ
በመዋቅሩ ሥር ያለው ማኅበረ ቅዱሳን ባቀረበው ጥያቄ መሠረት ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ይህን ደብዳቤ መጻፉ የማኅበሩን ሕጋዊ አካሄድ ያመለክታል፡፡ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱም ጉዳዩን ተቀብሎ እና አምኖበት የማኅበሩ ጉዳይ ብቻ ሳይኾን የቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ጉዳይ ነው ብሎ ጥያቄውን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም አቅርቧል፡፡ የማኅበሩን ዐቅድ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ከማጽደቁም በላይ ይሁንታውን እና ፈቃዱን አክሎበት ለሦስተኛ ወገን ስለ ማኅበረ ቅዱሳን ተገብቶ ፈቃድ ጠያቂ ኾኖ ደብዳቤ መጻፉ ሊሠመርበት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ ጉዳዩ የአንድ ማኅበር ብቻ ሳይኾን ኩላዊት፣ ሐዋርያዊት የኾነችው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንደተደረገ ከዚህ እንረዳለን፡፡
፪. ባለቤትነቱ የጠቅላይ ቤተ ክህነት መኾኑ
በተጻፈው ደብዳቤ ውስጥ ". . . እየጠየቅን ለሚደረግልን መልካም ትብብርም በቅድሚያ ምስጋና እናቀርባለን" የሚለው አገላለጥ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ራሱን የጉዳዩ ባለቤት እንዳደረገው ያሳየናል፡፡ ምናልባትም "ለሚደረግላቸው ትብብርም" ተብሎ ተገልጦ ቢኾን ለዚህ ትርጉም ባልተመቸ፡፡ ነገር ግን ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ትብብሩ በቀጥታ እርሱን የሚመለከት መኾኑን በማያወላውል ሁኔታ አስቀምጦታል፡፡
"ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ለመላዋ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሥራ አመራር፣ የገንዘብ ንብረት አስተዳደር የበላይ ኃለፊ በጠቅላላው የቤተ ክህነት ዋና ባለሥልጣን ነው" ቃለ ዓዋዲ ፶፫፥፩። እንዲሁም ነውና ስለመላዋ አንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲን ማንነት የሚያስረዳውን ዐውደ ርእይ እሺ በጀ ብሎ መፍቀዱም ኾነ ማስፈቀዱ ይገባዋል፡፡ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በጻፈው ደብዳቤ መነሻነት ምንም ይደረግ ምን የውጤቱ ተቀባይ እና ባለቤት ጠቅላይ ቤተ ክህነት ነው፡፡ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ መላዋ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ሥራ ይመራል ተብሎ ተደንግጓልና፡፡
ከዚህ በላይ በተገለጡት አመክንዮዎች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ባለቤትነቱን ወስዳ በተገቢው መንገድ የተጓዘችለት ዐውደ ርእይ ሲታገድ ለእኔ የታገደችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ይኽንን ታሪካዊ ስህተት በእርሷ ላይ መሥራት ከጤናማነት አይቀዳም፡፡ ይህች ቤተ ክርስቲያን ለሀገሪትነ ኢትዮጵያ ሁለመናዋ ናትና፡፡ አንድ ማኅበርን ያጠቃን የመሰላቸው ሁሉ እየተጋጩ የሚገኙት ከታላቋ ከብሔራዊትም በላይ ዓለማቀፋዊት ከኾነቸው ቤተ ክርስቲያን ጋር እንደኾነ ካልተረዱት ቢረዱት መልካም ነው፡፡ እርሷን ማገድ ይቻላል ወይ?
እየተላለፈልን ያለው መልእክት ቆም ብሎ የሚያስብ እስካልመጣ ድረስ ለሀገርም ለወገንም አይጠቅምም፡፡ በሰላም ተጉዘን በሰላም ጠይቀን በሰላም ተፈቅዶልን በሰላም የመሥራት ዓላማችን ሲደናቀፍ ምን ለማለት ተፈልጎ ነው? ሰላማዊያን ሽልማታቸው እንዲህ ከኾነ አጠያያቂ ነው፡፡ ሰላማውያን ሌላ መንገድ እንዲያዩ የሚመኝ አካል አለን?
አንድ ሥራ ግን ሳያውቁት ሠርተውልናል፡፡ የዐውደ ርእዩ መሪ ቃል "የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አሰተምህሮ እንጠንቅቅ ድርሻችንንም እንወቅ" የሚል ነው፡፡ በመሪ ቃሉ ውስጥ "ድርሻችንን እንወቅ" የሚለው ለሁሉም ሕዝበ ክርስቲያን የተላለፈ ይመስለኛል፡፡ ሁሉም ስለ ድርሻው አሁን እየተነጋገረ ይመስለኛል፡፡ በአካል ባልገኝም ሁለት እና ሦስት ከዚያም በላይ ኾናችሁ በጉዳዩ ተንገብግባችሁ "እንኪያስ ድርሻችን ምን ይኾን?" ስትባባሉ ይሰማኛል፡፡ በቃ የተፈለገው እናንተን እና ሌሎችንም እዚህ ማድረስ ነበር፡፡ ድርጊቱ እዚህ አድርሶናል፡፡ ዐውደ ርእዩ ባልታሰበ መንገድ እንደተካሄደ ሳልቆጥር ማለፍ አልችልም፡፡ የእርሱ መንገዱ ብዙ ነውና፡፡
እርግጥ ነው አዳራሽ ውስጥ አልገባንም፡፡ የመግቢያም አልከፈልንም (ቀድማችሁ የመግቢያ ትኬት የገዛችሁ ከ፵ ሺህ በላይ የምትኾኑትን ሳልጨምር)፡፡ ግን ትኬት በእጃችን የገባውም ያልገባውም በአንድነት አንዱን ዐውደ ርእይ ወደ አዳራሹ ሳንሄድ ባለንበት ኾነን ዐይተነዋል፡፡ ግን ዐውደ ርእዩን ዐይተነዋል፡፡ ከእንግዲህ የሚጠብቀን በየአጥቢያችን፣ በወረዳችን፣ በሀገረ ስብከታችን እና በመንበረ ፓትርያርክ ሁሉ የሚጠበቅብንን ለማድረግ መሰለፍ ነው፡፡ ቦታችንን የያዙትን ጥቃቅን ቀበሮዎች ከመዋቅር ማስወጣት እና እኛ በስፍራው መተከል ይኖርብናል፡፡
መንግሥትም በጉዳዩ ላይ አስቦበት መክሮበት ዘክሮበት ዐውደ ርእዩ ወደ ነበረበት እንዲመለስ ለማድረግ የድርሻውን ይወጣዘንድ ይገባዋል፡፡ ለተሄደው ሁሉ ሕጋዊ መንገድ የመጨረሻው ምላሽ መሠረታዊ ነውና! መልሱ ትክክል የሚኾነው ሕጋዊ ጠያቂ ሲሸለም ብቻ ነው፡፡
ከኤግዚቢሽን ማዕከሉ (የዐውደ ርእይ ማዕከል መባል ሲገባው በባዕድ ቃል ሲጠራ መኖርን የመረጠ መኾኑ በራሱ ሌላ ጉዳይ ኾኖ) አመራሮች የወጣው ቃል "ከበላይ አካላት" ዐውደ ርእዩ መካሄድ እንደሌለበት መመሪያ ስለተላለፈ በዚህ ምክንያት ወደ መሰረዝ እንደሄዱ ይገልጣል፡፡ ያ "የበላይ አካል" ማን ነው? ሕግ ባለበት ሀገር ተሰውሮ መቅረት ለምን ተፈለገ? እኔ ነኝ ያገድሁት ለማለት ለምን ድፍረት አጣ? ጉዳዩ የሀገርን ሰላም እና ጸጥታ ከማስከበር አንጻር ታይቶም ከኾነ ጠቅላይ ቤተ ክህነትም ማኅበረ ቅዱሳንም የማይተባበሩ ኾነው ነው ወይ? የሀገርን መልካም ገጽታ ለማስተዋወቅ ብዙ የሰው ኃይልና ገንዘብ ማፍሰሳቸው እንዴት ተዘነጋ? ቤተ ክርስቲያን መቼም ቢኾን በሀገር ጉዳይ መሪ ፊታውራሪ እንጂ መመሪያ ተቀባይ ኾና አታውቅምና! በሀገር ፍቅር ቋንቋ ልጆቿ ከመትረጌስም ፊት ለመቆም የማይገዳቸው ለመኾናቸው የቅርቦቹን አቡነ ሚካኤልን እና አቡነ ጴጥሮስን ማስታወስ ይበቃል፡፡
ከሁሉም በላይ ግን ይህንን ዐውደ ርእይ እንዳይካሄድ ያገድሁት እኔ ነኝ የሚል አካል አለመኖሩ ካለም ደግሞ መደበቁ ሌላው አሳፋሪ ድርጊት ነው፡፡ ብቅ ብሎ ማስረዳት አለበት፡፡ ከተሳሳተም ደግሞ መጠየቅ አለበት፡፡ አስፈላጊውን የሕጋዊ መስመር ተከትሎ ፈቃድ ጠይቆ፣ በጠየቀም ጊዜ ማሟላት ያለበትን ማንኛውም መስፈርት ሁሉ ማሟላቱ ተረጋግጦ ውል ፈጽሞ የተገኘን ማኅበር ዓላማ እንደተደበቀ በስውር አስታጉሎ መቅረት ምንን ያመለክታል?
ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም በአግባቡ ጠይቃ ምላሽ የማግኘት ሕጋዊ መብት አላት፡፡ ስለኾነም መሄድ እስካለባት ድረስ ሄዳ ጉዳዩ እንዳይታጎል ሥራ ይጠብቃታል፡፡ በዝምታ የማይታለፈውን የመብት ጉዳይ በዝምታ ማለፍ የለባትም፡፡
ማሳሰቢያ
ሁኔታዎች ተጣርተው አስፈላጊው ሁሉ ጥረት እንዲደረግ በማሰብ ለተወሠኑ ቀናት (ከሁለት ቀን በላይ አይኾንም) ዐውደ ርእዩ የማይታይ ሲኾን አማራጮች ሁሉ ታይተው መፍትሔ የማይገኝ ከኾነም በምን መልኩ መቀጠል እንዳለበት መግለጫ እንደሚሰጥ የማኅበሩ ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡ በዚህ እና በዚያ በተለይም በማኅበሩ ጽ/ቤት ዐውደ ርእዩ ይታያል እየተባሉ ሲነገሩ የነበሩት ሀሳቦች ውሣኔ ያልተሰጠባቸው ስለኾኑ ሁኔታውን እስክናረጋግጥ ድረስ በትዕግስት መጠባበቅ ይመረጣል፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials