Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, March 31, 2016

ወያኔ መሞቻውን፤ ­­­­እኛ መሰንበቻውን

ይገረም አለሙ
እኔ ከምኑም የለሁበት ተቀዋሚም ደጋፊም አይደለሁም  በሚል ጭንብል ተሸፍኖ የሚኖረው ክፍል ሲቀር ሌላው በሁለቱ ጎራ ይመደባል፡፡ በወያኔ ጎራ ያለው ወገን ለአባልነትም ይሁን ለደጋፊነት ያበቃው ምክንያት ምንም ይሁን ባለው አቅም  በሚችለው መንገድ የወያኔን  ዕድሜ ለማራዘም ያስችላል ብሎ ያመነበትን ይሰራል፡፡ እንደውም አንዳንዱ ያለ ወያኔ መኖር አንደማይቸል ራሱን አሳምኖ ሞቴን ከወያኔ ጋራ ያለ ነው የሚመስለው፡፡ በዚህ ጎራ የተሰለፉ ሰዎች ሆነ ብለው አቅድው ሊገኝ የሚችለውን ውጤት ናፍቀው የወያኔን እድሜ በሚያሳጥር ተግባር ላይ አይሰማሩም፡፡ የውስጥ አርበኞች ካልሆኑ በስተቀር፡፡
በአንጻሩ በተቃውሞው ጎራ ያለው ወገን ለተቀዋሚነት የበቃበት ምክንያትና አንዴትነት የመለያየቱን ያህል ተግባሩም የዛኑ ያህል የተለያየ ነው፡፡ ይህም በመሆኑ መቋሰል መጓተቱን፤መወነጃጀል ጣት መቀሳሰሩን ወደ ጎን አስቀምጦ  አንድ ወጥ በሆነ መንገድ ለወያኔ እድሜ ማጠር መስራት አልቻለም፡፡  ይህም በመሆኑ ወያኔ በጥንካሬው ሳይሆን በድክመቱ፣ በእውኑ ሳይሆን በሙቱ ሲገዛ ኖሯል፣. አሁንም እየገዛ ነው ምን አልባትም ወደፊትም! ( መበስበሳቸውን ከነገሩን በኋላ በእኛ ድክመት ህይወት ዘርተው ስንት አመት ገዙን ?)
ከወያኔ ጎራ የተሰለፉት ሥልጣን ሽተውም ይሁን በዘር ተስበው፤ስኳር ልሰውም ይሁን መሬት ብናገኝ ብለው፤አያያዙን አይተህ ወደሚያደላው ብለው መስሎ ተመሳስሎ መኖርን መርጠውም ይሁን ብቻ ባሉበት በተሰለፉበት ለወያኔ ይበጃል ያሉትን በተናጠልም ይሁን በመተባበር ሲሰሩ አኛ ለተያያዝነው ትግል ይበጃል የምንለውን ምን ሰራን ብለን ራሳችንን ከመጠየቅ ይልቅ እነሱ ማውገዙ በእጅጉ የቀለናል፡፡ ዓላማው ምንም ይሁን ምን ያንን ተግባራዊ ለማድረግ ከሚመስለው ተባብሮ በራሱም ተጠናክሮ በጽናት የሚሰራ ይደነቃል፡፡ ዓላማየ የሚለውን ያውም በቃል ሲነገር የተቀደሰ አላማ ያንን ተግባራዊ ለማድረግ የማይጣጣር  የማይተባበር መወገዝ መወቀስ ካለበት እርሱ ነው፡፡
የተቃውሞው ጎራ ዥንጉርጉርነት በራሱ አልሞ አቅዶና ታግሎ ውጤት ማምጣት አይደለም ጊዜ የሚፈጥራቸውን አጋጣሚዎች ለመጠቀም እንኳን  የማይችል አድርጎታል፡፡ በመሆኑም ወያኔ ለሥልጣኔ ማቆያ ይበጃኛል እያለ በሚፈጽመው ኢ- ሰብአዊ ኢ- ህጋዊና  ከዴሞክራሲ ጋር ሆድና ጀርባ በሆነ ተግባሩ በየግዜው ከህዝብ እየተጣላ መሞቻውን ሲያፋጥን በአንጻሩ ተቀዋሚው መሰንበቻውን ያመቻችለታል፡፡ ( የወያኔን ዕድሜ የሚያራዝም ተግባር ይፈጽማል፡፡)

እንደ ተቀዋሚ ድርጅቶቹ ብዛት  እንደ መሪዎቹ ማንነት ለታቃውሞ የተነሱበት ዓላማና ምክንያት ይለያያል፡፡ ነገር ግን በወርቃማ ቃላት የተሸፈነ ድብቅ አጀንዳ እስከሌለ ድረስ የወያኔን አንባገነናዊ አገዛዝ ከህዝብ ጫንቃ ላይ ማስወገድና ኢትዮጵያን ዴሞክራሲያዊት ሀገር ማድረግ ሁሉንም ሊያስማማ የሚችል ነው፡፡ ( በድርጅት ደረጃ ከዚህ የተለየ የተጻፈና በአደባባይ የሚናገሩት ዓላማና ግብ የነበራቸው እድሜ አስተምሮአቸው መከራ መክሮአቸው  ተመልሰዋል፡፡)

በመሆኑም አደረጃጀታቸው ቢለያይ፤ የመረጡት የትግል ስልት ሊዛመድ የማይችል ቢሆን ከላይ በተጠቀሰው ግብ ተስማምተው  ቢችሉ ተባብረው ካልሆነም ሁሉም በየራሱ የትግል ስልትና መንገድ ወደ ግቡ መጓዝ አንጂ አንዱ የሌላኛው እንቅፋት ሲብስም ጠላት ሆኖ መሰለፍ ፍቺ ያጣ አንቆቅልሽ ነው፡፡ ይህ አንቆቅልሽ የሆነ ተግባር ነው እንግዲህ ወያኔ መቃብሩን ሲቆፍር ተቀዋሚዎች እድሜ ማራዘሚያ መድሀኒት እንዲሆኑት ያደረገው፡፡እናም ወያኔ መሞቻውን እኛ መሰንበቻውን እንሰራለን ለማለት ያበቃኝ፡፤
ብዙ ሩቅ መሄድ ሳያስፈልግ  ወቅታዊውን ሁኔታ እንመልከት፡፡ ከሁለት አመት በፊት ተቃውሞ አስነስቶ የብዙ ወጣቶችን የህይወት መስዋእትነት አስከፍሎ ለብዙ ወጣቶችም እስር እንግልትና ስደት ምክንያት ሆኖ ተግባራዊነቱ የቆመውን የኦሮምያና የአዲስ አበባ አጎራባች ወረዳዎች የጋራ ማስተር ፕላን ተግባራዊ አናደርገዋለን ለማደናቀፍ የሚሞክሩትንም ልክ እናስገባቸዋለን ብሎ ለህዝብ  ያላቸውን ንቀት ባሳየ መልኩ መናገር እድሜ ማሳጠሪያ እንጂ ማራዘሚያ ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ ወያኔ ሞቱን የጠራበት የአቶ አባይ ጸሀየ ንግግር ግን ለፖለቲከኞቹ የተገለጠላቸው ህዝቡ ለተቃውሞ አደባባ ወጥቶ በጥይት መውደቅ  ከጀመረ በኋላ ነው፡፡
በኦሮምያ በአብዛኛዎቹ ዞኖች የታየው ግድያ፤ የግፍ ደብደባና የገፍ እስራት የተጠቀመበት አልተገኘም እንጂ ወያኔ መሞቻውን ያመቻቸበት ነበር፡፡ አቶ ጌታቸው ረዳ ሕዝብን ጋኔን፣ ሰይጣን ጠንቋይ በማለት የተናገሩትም ሆነ የኦሮምያ ክልል ፕሬዝዳንቱ  አቶ ሙክታር ከደር  የወያኔው ገዳይ ቡድን በኦሮምያ ክልል ተሰማርቶ የፈጸመው ኢሰብአዊ ድርጊት ሁሉ ተገቢና ትክክል እንደነበረ ገልጸው ይህን በማድረጋችሁ ትመሰገናላችሁ በማለት በመገናኛ ብዙኃን አማካኝነት ያስተላለፉት አድናቆትና ምስጋና ለወያኔ መሞቻው አንጂ መሰንበቻው ሊሆን የሚችል አልነበረም፡፡ አንዲህ አይነት ግራ ገብ ነገር ሲገጥማቸው ሟች ሞልቶ ነበር ገዳይ ጠፋ እንጂ ነው የሚሉት አበው፡፡

የሱዳኖችን መሬት ድንበር አልፈው ሄደው የያዙ ሽፍቶች በማለት የሀገሩን ዜጎች ከመወንጀል አልፎ  የኢትዮጵያን መሬት የሱዳን ነው በማለት በአደባባይ ለመመስከር የተበቃው ከማን አለብኝነት ንቀት በመነጨ ቢሆንም ይህ ሞቱን ሊያፋጥኑ ከሚችሉ በርካታ ተግባሮቹ አንዱ የሆነው ድርጊት ያደረሰበት ነገር አለመኖሩ ሲታይ በርግጥም የናቀን አይቶ ገምቶ ነው ያሰኛል፡፡ ያስናቁን ደግሞ በመግለጫ እንጂ በተግባር የማይታዮ ቁጥረ ብዙ ድርጅቶች ናቸው፡፡
በሀገሪቱ በብዙ አቅጣጫ ፈንድቶ የወጣ ቁጣ በሚታይበት ወቅት አዲስ አበባ ዝም በማለቱ ለአመታት ተግባራዊ ያላደረጉትን የመንገድ ሥነ- ሥርዓት ህግ ተግባራዊ እንደርጋለን ብለው የታክሲ ሾፌሮችን ለስራ ማቆም አድማ የዳረጉበትን ድርጊት ማንም ጤነኛ የወያኔ አባልና ደጋፊ ለእድሜ ማራዘሚያ የተደረገ ነው ሊለው አይችልም፡፡ ዝም ያለውን ለመቆስቆስና ተቃውሞውን አዲስ አበባ ላይም ለማቀጣጠል  የውስጥ አርበኞች የፈጸሙት ነው ከተባለ ሊያስማማን ይችላል፡፡ ነገር ግን በማንም ተፈጸመ በማን ከሌሎች ድርጊቶች ጋር ተደማምሮ  የወያኔን መሞቻ ሊያፋጥን የሚችል ድርጊት ነበር፡፡ በነበር ቀረ እንጂ፡፡
በሀገር ውስጥ ያሉትም ሆኑ በወጪ የሚገኙት ፖለቲከኞች እነዚህና ሌሎች በርካታ  ወያኔ ራሱ የፈጸማቸውን ሞቱን የሚያፋጥኑ ድርጊቶች  ሊያነሳሱዋቸውና ሊያስተባብሩዋቸው ቀርቶ እንደ ዓላማና አደረጃጀታቸው በየራሳቸው መንገድ    ተንቀሳቅሰው ራሱ በቆፈረው ጉድጓድ ለመቅበር ያደረጉት ነገር ባለመኖሩ እሱ ሞቱን ቢያፋጥነውም እነርሱ እስትንፋስ ሰጥተውት መሰንበት ችሏል፡፡ መሰንበቱን ሲያረጋግጥ ደግሞ  ይቅርታ የሚባል የእድሜ ማረዘሚያ መድሀኒት ራሱ ለራሱ አዞ እየወሰደ ይገኛል፡፡ ይህን ተከትሎም አንዳንዶቹ ፖለቲከኞች በእውናቸው ይሁን በህልማቸው የታያቸው ባይታወቅም ይቅርታ በተባለው እንክብል ወያኔ ሙሉ ፈውስ አግኝቶ ከደደቢት እምነቱ ይለወጣል ብለው ተስፋ እያደረጉ ነው፡፡
ወያኔ ከላይ ለአብነት የተጠቀሱትን ጨምሮ ለሀያ አምስት አመታት በቃልም በተግባርም መሞቻውን የሚያፋጥኑ ድርጊቶች ፈጽሟል፡፡በአንጻሩ ወያኔን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጫንቃ ላይ ለማንሳት ነው የምንታገለው የሚሉ ፖለቲከኞች ሀያ አምስት አመት ሙሉ ፓርቲ ሲያፈርሱ ሲገነቡ፤ አንደ አሜባ ራሳቸውን ሲያባዙ፤ርስ በርስ ሲወነጃጀሉ የጎንዮሽ ሲታገሉ ወያኔን ታግለው የሚያሸንፉ አይደለም ራሱ መቃብሩን እየቆፈረ ሞቱን ሲያፋጥን ገንዘው ሳጥን ለመክተትም ሆነ ከቀብር ስፍራ አድርሰው አፈር ለመመለስ የሚችሉ ባለመሆናቸው ወያኔ ነበረ አለ  እስከ መቼ አንደሆነ ባይታወቅም ይኖራል፡፡ አሳዛኝ አሳፋሪ!

No comments:

Post a Comment

wanted officials