Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, October 6, 2016

ፍሪደም ሃውስን ጨምሮ የተለያዩ የሰብዓዊ መብት ተቋማት በእሬቻ በዓል ላይ በመቶዎች ለሚቆጠሩ ሰዎች ሞት ምክንያት የሆነው አደጋ እንዲጣራ ጠየቀ




በቢሾፍቱ ከተማ በመቶዎች ለሚቆጠሩ ሰዎች ሞት ምክንያት የሆነው አደጋ የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ተቃውሞን ለመቆጣጠር ሲሉ በከፈቱት የተኩስ ዕርምጃ መሆኑን መቀመጫውን በዚህ በአሜሪካ ያደረገ አንድ አለም አቀፍ ተቋም ማክሰኞ አስታወቀ።
ፍሪደም ሃውስ የተሰኘው ይኸው የሰብዓዊ መብት ተቋም የኢትዮጵያ መንግስት ድርጊቱ በገለልተኛ አካል እንዲጣራ ፈቃደኛ መሆን ይኖርበታል ሲል ጥሪውን አቅርቧል።
የመንግስት ባለስልጣናት ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች በበዓሉ አከባበር ስፍራ ተፈጥሮ በነበረ ግፊያና መረጋገጥ እንዳለሆነ ሲገልጽ ቆይተዋል።
ይሁንና በጉዳዩ ዙሪያ መግለጫን ያወጣው ፍሪደም ሃውስ የጸጥታ ሃይሎች ለበዓሉ በታደሙ በሚሊዮን በሚቆጠሩ ሰዎች ላይ ጥይትን ጨምሮ አስለቃሽ ጢስ በመክፈታቸው ምክንያት አደጋው ሊደርስ መቻሉን ገልጿል።
በእስካሁኑ ሂደትም ከ150 በላይ ሰዎች ሞት ማረጋገጥ መቻሉን አመልክቷል።
የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች በተለያዩ ጊዜያት የተቀሰቀሱ ህዝባዊ ተቃውሞዎችን ለመቆጣጠር ሲሉ ከመጠን ያለፈ የሃይል ዕርምጃን ሲወስዱ እንደነበር የሰብዓዊ መብት ተቋሙ አክሎ ገልጿል።
ይኸው ድርጊት በእሬቻ በዓል አከባበር ወቅት መደገሙን የተናገሩት የድርጅቱ የአፍሪካ ዳይሬክተር ቡካሲን ፔትሮቺች ድርጊቱ በአስቸኳይ በገለልተኛ አካል ምርመራ መካሄድ እንዳለበት ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
ፍሪደም ሃውስን ጨምሮ የተለያዩ የሰብዓዊ መብት ተቋማት እሁድ በቢሾፍቱ (ደብረዘይት) ከተፈጠረው ግጭት ጋር በተገናኘ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች እንደሞቱ ቢገልጹም መንግስት የሟቾች ቁጥር 55 ብቻ መሆኑን አስተባብሏል።

No comments:

Post a Comment

wanted officials