Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, February 11, 2016

አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንዲፈቱ ለመጠየቅ 130ሺ ፊርማ መሰብሰቡን ሪፕሪቭ አስታወቀ

አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንዲፈቱ ለመጠየቅ 130ሺ ፊርማ መሰብሰቡን ሪፕሪቭ አስታወቀ
ኢሳት (የካቲት 1 ፥ 2008)
የብሪታኒያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን ከአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ከእስር እንዲፈቱ ግፊትን እንዲያደርጉ የሚጠይቅ የ130ሺ ሰዎች ፊርማ መሰባሰቩን ሪፕሪቭ የተሰኘ የሃገሪቱ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋም አስታወቀ።
ታዋቂ የብሪታኒያ ዜጎች እንዲሁም የፓርላማ አባላትና የሰብዓዊ መብት ተሟጋችና ግለሰቦችን ፊርማ ያካተተው ይኸው የ130ሺ ሰዎች ፊርማ ማክሰኞ በአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ባለቤትና ልጆች በኩል ለሃገሪቱ የበላይ አካል መቅረቡን ድርጅቱ ገልጿል።
የፊታችን ቅዳሜ ለእስር ከተዳረጉ 600 ቀናት የሚሞላቸው አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፣ የህግ አገልግሎትን በሚሰጡ አካላት እንዳይጎበኙ ተደርጎ መቆየቱን የብሪታኒያው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋም አስታውቋል።
እነዚህን ቀናቶች ሙሉ አቶ አንዳርጋቸው ወደ ነጻነት ሊጠጋ አለመቻሉ እጅግ የሚረብሽ ድርጊት ነው ሲሉ በድርጅቱ ምክትል ዳይሬክተር የሆኑት ሃሪት ማክ-ኩሎች ገልጸዋል።
የብሪታኒያ መንግስት ኢትዮጵያ የወሰደችውን እርምጃ ተቀባይነት የሌለው እንደሆነ ቢገልጽም፣ አቶ አንዳርጋቸው የሚፈቱበትን ሁኔታ ማመቻቸትና ጥረት ማድረግ ይገባዋል ሲሉም ሃላፊው አሳስበዋል።
የሃገሪቱ መንግስት ግፊቱን አጠናክሮ እንዲቀጥል ለማሳሰብም የ130ሺ ያህል ሰዎች ፊርማ ተሰባስስቦ ለሚመለከተው ክፍል መቅረቡን የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ጉዳይ በልዩ ሁኔታ የሚከታተለው ሪፕሪቭ ድርጅት ባወጣው መግለጫ አመልክቷል።
የሃገሪቱ የፓርላማ አባላትን ጨምሮ ታዋቂ ግለሰቦችና የሰብዓዊ መብት ተቋማት ድርጅቶች የብሪታኒያ መንግስት በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ጉዳይ ለዘብተኛ አቋምን አሳይቷል በማለት ተደጋጋሚ ተቃውሞ ሲያቀርቡ መቆየታቸው ይታወሳል።
የፊታችን ሰኔ ወር በእስር ቆይታቸው ሁለት አመት የሚሆናቸው አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ የጤናቸው ሁኔታም አሳሳቢ መሆኑን የብሪታኒያው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋም አክሎ ገልጿል።
ከወራት በፊት የሽብርተኛ ወንጀል ክስ የተመሰረተባቸው የፓርቲ አባላት አቶ አንዳርጋቸው ምስክር ሆነው እንዲቀርቡላቸው የቀረቡትን ጥያቄ ተከትሎ የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በምስክርነት እንዲቀርቡ ተደጋጋሚ ትዕዛዝን ቢሰጥም አቶ አንዳርጋቸው ሊቀርቡ አለመቻላቸው ይታወቃል።
 
Netsanet Beqalu Mannet's photo.
 

No comments:

Post a Comment

wanted officials