Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Monday, February 29, 2016

በአዲስ አበባ የሚካሄደው የታክሲ አሽከርካሪዎች አድማ እንደቀጠለ ነው



የካቲት ፳፩ (ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- 
የፌዴራል ትራንስፖርት ባለስልጣን አሽከርካሪዎች ጥፋት ሲያጠፉ ፈቃዳቸውን እስከመሰረዝ የሚያደርሰውን ከበድ ያለ ቅጣት የያዘውን ህገደንብ በመቃወም በአ/አ ከተማ የተጀመረው የታክሲ ማቆም አድማ የቀጠለ ሲሆን ፣ በተለያዩ አካባቢዎች ታክሲ በመጠበቅ ላይ የነበረው ህዝብ ሆን ብሎ መንገዶችን በመዝጋት፣ ሌሎች የግል፣የንግድና የመንግስት ተሸከርካሪዎች እንቅስቃሴ እንዲታወክ በማድረግ ተቃውሞውን ተቀላቅሏል።
ተቃውሞውን ተከትሎ የመንገድና ትራንስፖርት ባለስልጣን ደንቡ አሁን ተፈጻሚ እንደማይሆንና ከሶስት ወራት በሁዋላ ተግባራዊ እንደሚሆን ቢገልጽም፣ አሽከርካሪዎች መግለጫውን ባለመቀበል ተቃውሞአቸውን ቀጥለዋል።
የታክሲ እጥረቱን ተከትሎ የመንግስት መስሪያ ቤት መኪኖች በትእዛዝ የትራንስፖርት አገልግሎት እንዲሰጡ ተደርጓል።ይህም ሆኖ በርካታ የመንግስትና የግል ድርጅት ሰራተኞች በስራ ገበታቸው ላይ መገኘት ሳይችሉ ቀርተዋል።
በሜክሲኮ፣ በቄራና አየር ጤና አካባቢዎች ህዝቡ መንገድ በመዝጋት ጭምር ተቃውሞውን አሳይቶአል።በአውቶቡስ ተራ፣ አድማውን ወደ ጎን በማለት ሲንቀሳቀሱ የነበሩ መኪኖች ተሰባብረዋል።በአየር ጤና የሚገኙ ተማሪዎች ደግሞ ተቃውሞ ለማሰማት ሲንቀሳቀሱ በፖሊሶች ተበትነዋል።ተመሳሳይ ተቃውሞ በአውቶቡስ ተራ አካባቢ በሚገኝ አንድ ትምህርት ቤት ተጀምሮ፣ ፖሊሶች በአካባቢው ደርሰው ተቆጣጥረውታል። የታክሲ አሽከርካሪዎች አድማ ሌሎች ዜጎችንም አካትቶ ወደ አጠቃላይ የመብት ጥያቄ እንዲሸጋገር የሚጠይቁ ጽሁፎች በብዛት እየተበተኑ ነው።
የታክሲ ባለንብረቶችና አሽከርካሪዎች እንዲሁም አድማውን የሚመራው አስተባባሪ ኮሚቴ የተጀመረው የስራ ማቆም አድማ በመጀመሪያው ቀን ውጤታማ ሆኗል ብለዋል ። በአሽከርካሪዎችና በህዝቡ መካከል ያለውን የመንፈስ አንድነትም አድንቀዋል።
ደህንነቶችና ትራፊክ ፖሊሶች በጋራ በመሆን መንገድ ላይ ያገኙዋቸውን ታክሲዎች ታርጋ ሲፈቱ አርፍደዋል። በአዲስ አበባ አጎራባች ቀበሌዎች የሚሰሩ ” ኦሮ” የሚል ታርጋ የተለጠፈባቸው በኦሮምያ ክልል ብቻ እንዲሰሩ የተፈቀደላቸው ታክሲዎች፣ ችግሩን ለመቅረፍ በሚል ወደ መሃል አዲስ አበባ ገብተው እንዲሰሩ ቢፈቀድላቸውም፣ ከህዝቡ የሚወሰድባቸውን እርምጃ በመፍራት እና አድማውንም በመደገፍ ብዙዎቹ ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል።
የአዲስ አበባ ታክሲ ሾፌሮች መብት አስከባሪ ኮሚቴ ከሰዓት በሁዋላ ባወጣው መግለጫ ” መንግስት ታርጋ እንፈታለን፣ ሾፌሮችን እና ባለንብረቶችን እናስራለን” በማለት የሚያሰማው ዛቻ እና ማስፈራሪያ መፍትሄ ሊሆን የማይችል መሆኑን ገልጿል። ህጉን ለሶስት ወራት እናዘገያለን የሚለው ማታለያ ተቀባይነት እንደሌለውና መንግስት በአስቸኳይ ህጉን ሙሉ በሙሉ በአዋጅ ካልሻረና ያለአገባብ ንሮ የሚገኘውን የነዳጅ ዋጋ ከአለም ገበያ ዋጋ ጋር ካለስተካከለ ፣ የስራ ማቆም አድማው ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲል አስጠንቅቋል። በአገሪቱ ያሉ ሹፌሮች አድማውን እንደሚቀላቀሉ ፣ መንግስት ፍትሃዊ ጥያቄውን በሃይል ለማፈን ከሞከረ ከስራ ማቆም አድማ አልፈው በመኪኖቻቸው መንገዶችን በመዝጋት ማንኛውንም የተሽከርከሪዎች እንቅስቃሴ ለማገት መዘጋጀታቸውንም በመግለጫቸው ጠቅሰዋል።
ካለፉት ሁለት ወራት ጀምሮ በመላው አገሪቱ የሚደረጉ ተቃውሞዎች በአይነትና በስፋት እየጨመሩ ሲሆን፣ በኦሮምያ፣ በአማራና አሁን ደግሞ በአዲስ አበባ በመካሄድ ላይ ያሉት ተቃውሞዎች፣ የህዝቡን አጠቃላይ የለውጥ ፍላጎት እንደሚያመለክቱ አስተያየቶች እየተሰጡ ነው። በኦሮምያ የሚካሄደውን ተቃውሞ ተከትሎ መንግስት የተቃውሞው አንድ ምክንያት ነው የተባለውን የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን እንደሰረዘው ሁሉ፣ አሽከርካሪዎችና ባለንብረቶች ተቃውሞአቸውን ከቀጠሉ መንግስት ይህንን ደንብም ሊሰርዘው ይችላል የሚሉ አስተያየቶች እየተሰጡ ነው።
በተመሳሳይ ዜና በአዲስ አበባ የሚታየው የነዳጅ እጥረት አሳሳቢ እየሆነ መምጣቱን አሽከርካሪዎች ይናገራሉ። ከዚህም በላይ ባለ ታክሲዎች የትራፊክ ፖሊሶች በሚወስዱት እርምጃ በከፍተኛ ሁኔታ ሲማረሩ መቆየታቸው ተቃውሞውን ለማስነሳት አንድ ምክንያት ሆኗል።

No comments:

Post a Comment

wanted officials