የጎንደር ሕዝባዊ ትግል ኢትዮጵያን የማዳን ትግል ነው!! – የኢትዮጵያ ሕዝብ የጋራ ትግል ሸንጎ (ሸንጎ)
ሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ. ም August 1, 2016

ይህን ሕዝባዊ ትግል ከዳር ለማድረስና ግቡን እንዲመታ በተለያዩ ቦታዎች የሚካሄደው ትግል መቀናጀት ይኖርበታል።ለዚህ በአገር ውስጥ የሚገኙት የፖለቲካ ድርጅቶች ከፍርሃትና እርስ በርስ ከመናቆር ድባብ ወጥተው እጅ ለእጅ ተያይዘውና ግንባር ፈጥረው አመራር ሊሰጡት ይገባል።የሕዝቡ ትግል በአንድ ቦታ ላይ ብቻ አተኩሮ ለአገዛዙ መቺ ሃይል አመቺ እንዳይሆንና ትግሉ በሃይል እንዳይዳፈን በተለያዩ ያገሪቱ ክፍሎች መቀጣጠል፣ አገር አቀፍ መሆን ይኖርበታል።
ገዢው ቡድን ጊዜ ለመግዛትና ለማዘናጋት ድርድር ልቅረብ ቢል ካለምንም ቅድመ ሁኔታ መቀበል ለጥፋት እጅን መስጠት ከመሆኑም በላይ ህልውናውን ማወቅ ነው።ስለሆነም ፖለቲካ እስረኞች ሳይፈቱ፣የመጻፍና የመሰብሰብ መብት ሳይረጋገጥ፣ለሽግግር መንግሥት ምስረታ የሚያበቃ ውል ሳይፈረም፣ለቁጥጥርና ለጭቆና የሚውሉ ሕጎች መሰረዛቸው ሳይረጋገጥ፣ በይሆናል ተስፋ ትግሉን ማብረድና አደባባይ የወጣው ተመልሶ እቤቱ እንዲገባ ማድረግ ለቀጣዩ አደጋና ጥቃት እራስን አጋልጦ መስጠት ይሆናል።ስለሆነም ከእራሳችን ተመክሮ ከ97ቱ ተለምዶ መማር የግድ ይላል።መሪና በቂ ዝግጅት የሌለው የሕዝብ ሰላማዊ ትግል ቀርቶ ታንክና መድፍ፣አይሮፕላንና መሳሪያ ያነገተ አያሌ ወታደር አሰልፎ ባልተቀናጀ አመራር ተዝረክርኮ የተካሄደው መፈንቅለ መንግሥት ሳይሳካ ቡጢ በጨበጠ የመንግሥት ደጋፊ ወገን መረታቱን ከቅርቡ የቱርክ ሁኔታ መረዳት እንችላለን። ይህን ስንጠቅስ የቱርክን መፈንቅለ መንግሥት በመደገፍ ሳይሆን ያልተደራጀና አመራር የሌለው ተቃውሞና ትግል ግቡን እንደማይመታ ለማሳየት ነው።
አሁን ሕዝብ ከመንግሥት ነኝ ባይ አገር አጥፊ ቡድን ጋር ደም ተቃብቷል፤ሕዝብና አገዛዙ ሆድና ጀርባ ሆኗል፤በባለሥልጣኖቹ መካከል ድንጋጤ የፈጠረው ውዝግብና ትርምስ እየጎላ መጥቷል፡፤ትናንትና ሽንጣቸውን ገትረው ይከራከሩለት የነበሩት ባለሥልጣኖች ዛሬ አደባባይ ወጥተው ስርዓቱን በመኮነን ላይ ናቸው።ሌሎቹም ወደውጭ አገር ንብረትና ቤተሰባቸውን በማሸሽ ላይ ናቸው።ይህ ሁሉ ስርዓቱ መዳከሙን ያሳያል።አሁን ሕዝብና አገዛዙ(ስርዓቱ) ከማይታረቅ ቅራኔ ውስጥ ገብቷል።ጠግኖ መቀጠል አይቻልም። እርቅና ሰላም የሚወርደው ይህ እኩይ መንግሥት ከስልጣን ሲወርድ ብቻ ነው።ከስልጣን መውረዱም ብቻ ሳይሆን ሕዝቡን የሚወክል፣በሕግ የበላይነት የሚያምን፣የአገሪቱን የግዛት አንድነት በሚያረጋግጥ፣የዜጎችን እኩልነትና መብት የሚያከብርና የሚያስከብር የሽግግር ብሎም ቋሚ መንግሥት ሲተካ ብቻ ነው። በግርግር የታጠቀ ወይም በውጭ ሃይሎች የሚረዳና ለውጭ ሃይሎች ጥቅም የቆመ ሃይል የሕዝቡን ድል ነጥቆ እንዳይወስድና ተመሳሳይ የመከራ አገዛዝ እንዳይሰፍን ነቅቶ መጠበቅ ያስፈልጋል።ከግብጽና ከሌሎቹም የሕዝብ ትግል ተነስቶ ከከሰመባቸው አገሮች የቅርብ ጊዜ ልምድ መማር ይጠቅማል።
የኢትዮጵያ ሕዝብ የጋራ ትግል ሸንጎ ይህ ሕዝባዊ ትግል የተሳካ እንዲሆን፣በአመራር በኩል ያለውን ክፍተት ለመሙላት ከሌሎቹ አገር ወዳድ ሃይሎች፣ የማህበረሰብ ተቋማትና የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር በመተባበር የሚቻለውን ሁሉ ለማድረግ ቃል ይገባል፤አመሰራረቱም ለዚያው ዓላማ ነው።አሁንም በአገር ቤት ካሉት የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር የቅርብ ግንኙነት አድርጎ ትግሉን በድፍረት እንዲመሩት የተቻለውን በማድረግ ላይ ይገኛል።
የኢትዮጵያ አገራችን የወደፊት ዕድልና የሕዝቡ ሁኔታ ሸንጎን እጅግ ያሳስበዋል፣ያስጨንቀዋልም።ለአገርና ለወገን የምታስቡ የፖለቲካ ድርጅቶች፣የሲቪክ ማህበራት፣የማህበረሰብ ስብስቦች ሁሉ፣በየምክንያቱ ተነጣጥለን የምናካሂደው ትግል ዋጋ ቢስና ጊዜው ያለፈበት መሆኑን አውቀን ከሕዝቡ ጎን ቆመን ትግሉን መሳተፍ እንደሚኖርብን ማወቅ ይገባናል።እንደተለመደው እንቀጥላለን ማለት የገዢውን መደብ ዕድሜ ማርዘም ነው። እንዳለፈው ጊዜ ለትብብር የሚደረገውን ጥሪ ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎ በየፊናው መባከን አሁን መስዋዕትነት እየከፈለ ያለውን ሕዝብ አውራ የሌለው መንጋ አድርጎ ለበለጠ አደጋ ማጋለጥ መሆኑን ልንረዳው ይገባል።
የሃይማኖት መሪዎችም በአገራችሁና በወገናችሁ ላይ የሚደርሰውን ግፍና በደል አውግዙ።እንደ ኢየሱስ ክርስቶስና ነብዩ ሞሃመድ ለሰው ልጆች ነጻነትና እኩልነት፣ክብር፣ለፈሪሃ እግዚአብሔር ታገሉ።ለአገር አንድነትና ነጻነትም እንደአቡነ ጴጥሮስና እንደ ደጃዝማች ዑመር ሰመተር፣እንደ ቢትወደድ አሊሚራህ እምቢ በሉ።ታቦት ተሸክመው በጦር ሜዳ ተሰልፈው ያገሪቱን ነጻነት እንዳስከበሩት የትናንቱ አባቶች እናንተም ያገራችሁን አንድነት ዛሬ አስከብሩ።የራቀውን ምዕመናን በስነምግባራችሁ፣በአገርና ሕዝብ ወዳድነታችሁ አሳምናችሁ ሳቡት።ለአገርና ለሕዝብ ጥቅም መታገልና መቆም ማለት አምላክን መራቅና መካድ አይደለም።አምላክን መካድ ማለት ክፉ ከሚሰሩት ጋር መወገን፣ግድያን፣ዘረፋንና፣ጭቆናን እያዩ በዝምታ መቀበል ነው።
የኢትዮጵያ መለዮ ለባሽም ወልዶና አሳድጎ ለዚህ ሙያ ያበቃህ ደሃ ሕዝብ መብቱ ሲገፈፍና ሲጨቆን ፣በአምባገነኖች ሲረገጥ መሣሪያ ሆነህ አታገልግል።ደመወዝህ ፣ስንቅና ትጥቅህ ከደሃው ሕዝብ ጉሮሮ እየተነጠቀ ከሚሰበሰብ ግብር ነውና በራስህ ላይ አትዝመትበት፣በጉሮርህ ላይም አጥንት አትቀርቅርበት።ገዢው ቡድን በመለዮ ከፋፍሎ ሊያጫርስህ፣የአገርህን አንድነት አፍርሶ ሙያ ቢስ ሊያደርግህ ታጥቆ የተነሳ መሆኑን ተገንዝበህ ከወገንህ፣ከአባትህ፣ከእናትህ፣ከወንድምና ከእህትህ ጎን ተሰልፈህ የጋራ መብትህን አስከብር።በወገኖችህ ደም መታጠብ ይብቃህ።በገዳይነት ከምትወነጀል ይልቅ በአገር አዳኝነት መመስገኑ እንደሚጠቅምህና እንደሚያኮራህ እወቅ።
የኢትዮጵያ ሕዝብ የጋራ ትግል ሸንጎ(ሸንጎ)በትግል መስኩ ላይ ወጥቶ ድምጹን ከሚያሰማውና ደሙን ከሚያፈሰው፣የአማራ፣ የኦሮሞ፣የኦጋዴን፣የቤንሻንጉል፣የትግራይ፣የጋምቤላ፣የአፋር ማህበረሰብ ጋር መቆሙንና፣በአገር ውስጥና ውጭ አገር በሚችለው መንገድ ድጋፍና ተሳትፎ እንደሚያደርግ ሊያረጋግጥ ይወዳል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ
Tel.: 44 7937600756 , +1 9168486790 E-mail : shengo.derbiaber@gmail.com
No comments:
Post a Comment