Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Wednesday, August 31, 2016

በኢትዮጵያ መንግስት እየተፈጸመ ያለውን የሰብዓዊ መብት ወንጀል ገለልተኛ አለም አቀፍ ቡድን እንዲመረምረው ተጠየቀ

በኢትዮጵያ መንግስት እየተፈጸመ ያለውን የሰብዓዊ መብት ወንጀል ገለልተኛ አለም አቀፍ ቡድን እንዲመረምረው ተጠየቀ
ኢሳት (ነሃሴ 24 ፥ 2008)በኢትዮጵያ ውስጥ በሁሉም ክልሎች በመንግስት ጸጥታ ሃይሎች እየተደረገ ያለውን ግድያና፣ ሰቆቃ፣ እና እስራትን የሚመረምር አለም አቀፍ ገለልተኛ ቡድን እንዲቋቋም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የሲቪክ ማህበራት ባወጡት መግለጫ ጠየቁ።
የምስራቅ አፍሪካ የሰብዓዊ መብት ተከላካይ ድርጅት (ዲፌንድ ዲፌንደርስ)፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ፕሮጄክት፣ Front Line Defenders, እና የሰብዓዊ መብት አለም አቀፍ ፌዴሬሽን (FIDH) በጋራ ባወጡት መግለጫ፣ በኢትዮጵያ ውስጥ በሰላማዊ ሰዎችና በሲቪል ማህበረሰብ አባላት ላይ እየደረሰ ያለው ግድያ ወከባና እስራት በአስቸኳይ እንዲቆም ጠይቀዋል።
የኢትዮጵያ መንግስት ካለፈው ነሃሴ ወር ለምርምር የተሰማሩ 4 የሰብዓዊ መብት ድርጅት አባላት በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ማሰሩ ታውቋል ። በዚሁ በነሃሴ ወር የሰብዓዊ መብት ምክርቤት አባላትና በምርምር ስራ ላይ የተሰማሩት እቶ ተስፋ ቡራዩ፣ አቶ ቡልቲ ተሰማና አቶ አበበ ዋከኔ፣ በኦሮሚያ ሲታሰሩ፣ አቶ ተስፋዬ ታከለ ደግሞ በአማራ ክልል መታሰራቸው ታውቋል።
እነዚህ በምርመራ ስራ ላይ እያሉ የታሰሩት የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አባላት ክስ ሳይመሰረትባቸውና ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ እስካሁን ድረስ በወህኒ ቤት ታስረው እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል።
የዕስሩ ምክንያት በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች እየደረሱ ያሉትን ግድያዎች፣ ሰቆቃና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች በመመዝገብ ላይ መሰማራታቸውና ይህም መንግስት እያደረሰ ያለው የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዳይጋለጥ ሆን ተብሎ የተደረገ ድርጊት አምነስቲ እንደሆነ በድረገጹ የተሰራጨው መግለጫ አትቷል።
በሰብዓዊ መብት ላይ ገለልተኛና ግልጽ ምርመራ ለማካሄድ ፍላጎት የሌለው የኢትዮጵያ መንግስት፣ በዜጎች ላይ ለደረሰው የሰብዓዊ ጥሰት ትክክለኛ፣ መረጃ ያወጣል ብለን አናስብም ሲል በአምነስቲ ኢንተርናሽናል ድረገጽ ላይ የተበተነው መግለጫ ያስረዳል። የኢትዮጵያ መንግስት የሰብዓዊ መብት ጥሰት የፈጸሙትን አጣርቶ ከማሰር ይልቅ፣ የሰብዓዊ መብት ድርጅት የምርምር ሰራተኞችን እያሰረ እንደሚገኝ ባወጣው መግለጫ አክሎ ገልጿል።
በሁለት ቀናት በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች ከ100 በላይ ሰላማዊ ሰልፈኞች በመንግስት ሃይሎች መገደላቸውን ተከትሎ የታሰሩት የሰብዓዊ መብት ሰራተኞች፣ የመንግስት ሃይሎች ያሰሯቸው ምክንያትም መረጃ የመሰብሰብ ሂደት ለማስተጓጎል በማሰብ እንደሆነ በድረገጽ ላይ የተሰራጨው መግለጫ ያስረዳል።
ከዚህ በተጨማሪ በዚሁ በነሃሴ ወር ሶስት የውጭ ጋዜጠኞች ለ24 ሰዓታት በሻሸማኔ ከተማ ታስረው እንደተፈቱ የገለጸው የአምነስቲ ኢንተርናሽናል ሪፖርት፣ ከታሳሪዎች ውስጥ ለአፍሪካ ኒውስ ኤጀንሲ የምትሰራዋ ሃዳር አህመድ፣ የፒ ቢ ኤስ ሪፖርተሮች ፍሬድ ላዛሮ እና ቶማስ አዳኤር እንደሚገኙበት ዘርዝሯል።
ዲፌንድ ዲፌንደርስ፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ፣ ፍሮንድ ላይን ዲፌንደርስ፣ እና የሰብዓዊ መብት አለም አቀፍ ፌዴሬሽን የተባሉት የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች በጋራ ባወጡት መግለጫ፣ የኢትዮጵያ መንግስት የታሰሩትን የሲቪል ማህበረሰብ አባላት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈታ፣ በኦሮሚያ እና በአማራ ክልሎች እየተካሄዱ ያሉ ግድያዎችንና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች በአለም አቀፍ መርማሪ ቡድን ምርመራ ማካሄድ እንዲቻል ፈቃድ እንዲሰጥ ጠይቀዋል።



No comments:

Post a Comment

wanted officials