Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Wednesday, August 24, 2016

ኢትዮጵያውያን የተለያዩ የተቃውሞ እርምጃዎችን እንዲወስዱ አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ ጠየቀ


ኢሳት (ነሃሴ 16 ፥2008)
አንጋፋ የኢትዮጵያ አትሌቶችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በሃገሪቱ የሚፈጸሙ ግድያዎችን እና እስራትን በመቃወም የተለያዩ የተቃውሞ እርምጃዎችን እንዲወስዱ እሁድ በሪዮ ኦሎምፒክ የተቃውሞ መልዕክቱን ያስተላለፈው አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ ከኢሳት ጋር ባደረገው ቃለምልልስ ጥሪውን አቀረበ።
እሁድ በአለም አቀፍ ደረጃ መነጋገሪያ ስለሆነ የተቃውሞ ድርጊቱ ከኢሳት ጋር ቆይታን ያደረገው አትሌት ሌሊሳ በተለይ አንጋፋ የኢትዮጵያ አትሌቶች የገዢው የኢህአዴግ መንግስትን ግድያ እና አፈና በመቃወም ተመሳሳይ ድርጊትን እንዲወስዱ ጠይቋል።
ካገኘሁት ሜዳሊያ ይልቅ ያስተላለፍኩት መልዕክት ደስታን ሰጥቶኛል ሲል የገለጸው አትሌቱ እጁን በማጣመር ተቃውሞን በአለም አደባባይ ማቅረቡ ሃላፊነትን የመወጣት ድርጊት እንደሆነ አስታውቋል።
“ከአሁን በኋላ ብሞትም አይቆጨኝም ሲል በወሰደው እርምጃ እጅግ ደስተኛ መሆኑን የተናገረው አትሌት ሌሊሳ፣ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ተረባርቦ ይህንን ስርዓት ማስወገድ አለበት” በማለት ከዜና ክፍላችን ጋር ባደረገው ቃለምልልስ አስረድቷል።
በመንግስት እየተፈጸመ ያለውን ኢሰብዓዊ ድርጊት ለመግለጽ ቃል ያጥረኛል ያለው ወጣቱ አትሌት የታሰሩ ዘመዶቹን ለመጠየቅ እስር ቤት በሚመላለስበት ጊዜ በሚያየው ሁኔታ ሲያዝን መቆየቱን አስታውቀዋል።
ለሪዮ ኦሎምፒክ ከመታቀፍ ጊዜ ጀምሮ በኢትዮጵያ ያለውን ግድያና እስራት በአለም አቀፍ ደረጃ ለማጋለጥ በዝግጅት ላይ እንደነበር የገለጸው ሌሊሳ በኦሮሚያና አማራ ክልሎች በርካታ ኢትዮጵያውያን እየረገፉ እንደሆነ አክሎ አስረድቷል።
ከባለፈው አመት ጀምሮ በበርሊንና ቶኪዮ ከተሞች በተካሄዱ የማራቶን ውድድሮች ድልን ተቀናጅቶ የነበረው አትሌት ሌሊሳ እሁድ በሪዮ ኦሎምፒክ በመዝጊያ ዝግጅት ወቅት በተካሄደ የማራቶን ውድድር የብር ሜዳሊያ ማግኘቱ ይታወሳል።
ይሁንና ወጣቱ አትሌት በእለቱ ያስተላለፈው ተቃውሞ ከድሉ ይልቅ በአለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ዘንድ ሰፊ ሽፋንን እንዲያገኝ ያደረገው ሲሆን፣ ሰኞ ድረስ በርካታ የአለም አቀፍ መገኛና ብዙሃን ድርጊቱን ሲዘግቡ ውለዋል።
በአሁኑ ወቅት በሪዮ ስላለው ሁኔታ የተጠየቀው አትሌቱ ከተለያዩ ሃገራት በርካታ ኢትዮጵያውያን በተለያዩ መንገዶች ያላቸውን ድጋፍ እየገለጡለት እንደሚገኝና በጥሩ ስነልቦና ውስጥ መሆኑን ከዜና ክፍላችን ጋር በነበረው ቆይታ ገልጸዋል።
ዋሽንግተን ፖስት፣ ኒው ዮርክ ታይምስ፣ ቢቢሲ፣ ሮይተርስ፣ ዎል ስትሪት ጆርናል፣ ዴይሊ ሜይልን ጨምሮ ከ20 የሚበልጡ አለም አቀፍ አቀፍ የቴሌቪዥን ጣቢያዎችና ጋዜጠኞች አትሌቱ የወሰደውን ድርጊት በማስመልከት በኢትዮጵያ ስላለው ተቃውሞ ሰፊ ዘገባን አቀርበዋል።

 2016 Rio Olympics - Athletics - Final - Men's Marathon - Sambodromo - Rio de Janeiro, Brazil - 21/08/2016. Feyisa Lilesa (ETH) of Ethiopia celebrates.   REUTERS/Athit Perawongmetha

No comments:

Post a Comment

wanted officials